የትምህርቱ ርዕስ | የማይከራከር

“እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል፤… የማይከራከር” 1ጢሞ. 3፡2-3
ሰው የአስተሳሰቡ ውጤት ነው ። አስተሳሰቡ የአስተዳደጉ ውጤት ነው ። አስተዳደግ መደበኛ ያልሆነ ከመደበኛው ትምህርት ቤት ግን የበለጠ የምንማርበት ነው ። አስተዳደግ ተግባራዊ ትምህርት ቤት ነው ። ክርስቶስ ሕይወታችንን ካልለወጠ ይዘን የምንዞረው አስተዳደጋችንን ነው ። አስተዳደግን በመደበኛ ትምህርት ፣ በዕድሜ መለወጥ አይቻልም ። እውቀት ያለንን ነገር የሚያዳብር እንጂ የሚለውጥ አይደለም ። ዕድሜም አስተዳደጋችንን የበለጠ የምናጠነክርበት ነው ። ሰው ሁሉ ክርስቶስን ተሸክሞ ካልዞረ አስተዳደጉን ተሸክሞ ይዞራል ። እኛን አይወዱንም በሚል ቤተሰብ ያደገ ሰው ዘረኛ ይሆናል ። ቆንጆ ነህ ተብሎ ያደገ ራሱን ለዝሙት ይሸጣል ። ሰነፍ ተብሎ ያደገ ሌሎችን ማመስገን ይቸገራል ። እኔ በሚል አስተዳደግ ያደገ ለሌሎች ስሜት ግድ የለሽ ይሆናል ። በብዙ እንክብካቤ ያደገ ጥገኛ ይሆናል ። እኛ በሚል አስተዳደግ ያደገ ከቤተሰቡ ውጭ ሌላውን መውደድ ይቸገራል ። በስድብ ያደገ ሌሎችን በማዋረድ ይረካል ። በበታችነት ስሜት ያደገ ትዕቢተኛ ይሆናል ። በመልኩ ሲሰደብ የኖረ ቆንጆ የሚባሉትን ይጠላል ። በቀለሙ ሲተች ያደገ ሌላ ቀለም ያለውን ሰው ለመግደል ይነሣሣል ። ከአመክንዮ የራቀ አስተዳደግ ያለው ያለ ምክንያት ሰው ይጠላል ። ሴት ብቻ ባለበት ቤት ውስጥ ያደገ ወንድ ብቻ ጥሩ ይመስለዋል ። ወንድ ብቻ ባለበት ቤት ውስጥ ያደገ ሴት ብቻ ጥሩ ትመስለዋለች ። በጥላቻ ያደገ ሰው ሁሉ ክፉ ይመስለዋል ። በዱላ ያደገ በቀለኛ ይሆናል ። ይቅርታን በማያስተምር ቤተሰብ ያደገ የሰውን ስህተት ማለፍ ይከብደዋል ። እኔን ብቻ አዳምጡኝ በሚል ቤተሰብ ያደገ ለፍላፊ ይሆናል ። በር ተዘግቶበት ያደገ ሰውን ሁሉ ይጠራጠራል ። በውግዘት ያደገ የሰዎችን እንከን ይፈልጋል ። በቅናት ያደገ በሌሎች በጎ ዕድል መደሰት ያቅተዋል ። ጉድለት አለብህ ተብሎ ያደገ ነጭናጫ ይሆናል ። አትችልም ተብሎ ያደገ መሞከር ይፈራል ። ሳይገራ ያደገ ክርክር ይወዳል ። የእግዚአብሔር አገልጋይ ግን የማይከራከር ሊሆን ይገባዋል ።

ክርክር ፍቅርን የሚያጠፋ ነው ። እውነትን ቢይዝም ክርክር ስህተት ነው ። ምክንያቱም እውነትን የሚናገረው ሰዎችን ለማሳወቅ ሳይሆን ለመርታት ነው ። የክርክር ዓላማው የበላይነትን ለማሳየት ነው ። የክርክር ዓላማው ሌላውን አጠልሽቶ ራስን ውብ አድርጎ ለማቅረብ ነው ። የክርክር ዓላማው ሌላውን ጥሎ ለማለፍ ነው ። ክርክር ለፖለቲካ እንጂ ለኑሮ መልካም አይደለም ። ክርክር ሌሎች እንዲሰለቹን የሚያደርግ ነው ። ክርክር የሥጋ ሥራ ነው /ገላ. 5፡20/ ። ክርክር የሥጋ ሥራ ከሆነ የሚከራከሩ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ። ክርክር የሕፃንነት ጠባይ ነው ። ደቀ መዛሙርት ማነው ትልቅ እያሉ ይከራከሩ ነበር /ማቴ. 18፡1/ ። ክርክር የሌሎችን ነጻ ፈቃድ አለማወቅና አለማክበር ነው ። ክርክር ሱስ ነው ። ክርክር ግጥሚያ ነው ። ግጥሚያነቱም የቃላት ግጥሚያ ነው ። ክርክር የነቀፋ ፣ የዘለፋና የስድብ መውጫ ነው ።
ክርክር የአሳብ ልውውጥ አይደለም ። ክርክር በአሳብ የበላይነት ሳይሆን በእኔነት የበላይነት ማመን ነው ። ክርክር የእውቀት ብርሃን የሚያስገኘው የአሳብ ፍጭት አይደለም ። ክርክር መናገር እንጂ መስማት የሌለበት ነው ። ክርክር እኔ እንጂ እኛ የማይል ነው ። ክርክር በራስ አጥር ውስጥ መዞር ነው ። ክርክር እውቀት ከመስጠት በእውቀት ስም ሌሎችን ማሳነስ ነው ።
ክርክርን የሚወልዱ ነገሮች አሉ ። እነዚህም፡-
1-  በአስተሳሰብ አለመብሰል፡- ዕድሜና እውቀት እየገፋ ሲመጣ እውቀት የሌለው መሃይም ማንም እንደሌለ እንረዳለን ። ሰዎችን ሁለት እርምጃ ወደ እኛ ለማምጣት አንድ እርምጃ ወደ እነርሱ መሄድ ተገቢ እንደሆነ እንረዳለን ።
2-  ሕፃንነት፡- ሕፃናት ቁመት ሲለካኩ ይውላሉ ። ቢረዝሙ የሚያገኙት ነገር ባይኖርም ከሌላው በመብለጣቸው ደስ ይላቸዋል ። ሌላውን መብለጥ ብቻ የሚፈልግ ትሑት መሆን አይችልምና ከእግዚአብሔር መንግሥት ይርቃል ።
3-  የቃል ሰው ብቻ መሆን፡- የምናውቀውን መኖር ቢያቅተን የምናምነውን መኖር ተገቢ ነው ። የቃል ሰዎች ግን የሚያውቁትና የሚያምኑትን መለየት ያቅታል ። ሰው በኑሮው ሲረታ እንጂ በቃል ሲረታ ጊዜያዊ ድልን ብቻ ያገኛል ።
4-  ጭብጨባን ፈላጊነት፡- መታከም ከሚገባቸው ስሜቶች አንዱ ጭብጨባ ፈላጊነት ነው ። ጭብጨባ ፈላጊዎች ስሜታዊ እንጂ እውነተኛ ወዳጅ የላቸውም ። ስሜት የሚበርድ ነውና መልሰው ይነቀፋሉ ። ክርክር ከጭብጨባ ፈላጊነት ይመነጫል ።
ሰው ከራሱ ፣ ከሰዎችና ከእግዚአብሔር ጋር ክርክር ውስጥ ይገባል ። የክርክር ጥልቅ ትርጉምም ይህ ነው ። ሰው ከራሱ ጋር ክርክር ውስጥ ሲገባ ትላንትና ላይ መቆየት ይጀምራል ። ያጣቸውን ነገሮች መቊጠርና ማዘን ይፈልጋል ። በስህተቱ ከመጠን በላይ ያዝናል ። የቀደመ ስህተቱ ዛሬን እንዲበክልበት ይፈቅዳል ። ቆሻሻ ቦታ መቆየት ለመቆሸሽ ነው ። ረጅም ሰዓት በስህተት ፊት መቆየትም ለመረበሽ ነው ። የራሱን መልካምነት በጣም እያሰበ ምላሽ አጥቻለሁ በማለት ጥያቄ ውስጥ ይገባል ። ፍቅርን ለማትረፍና ፣ ጥሩ ሰው ነው ለመባል የሄደባቸው ርቀቶች ጠላትነትን ብቻ እንዳተረፉበት ያስብና ክፉ መሆን ሳያዋጣ አይቀርም የሚል አስተሳሰብ ውስጥ ይነከራል ። ክፋትንም ሲያደርግ እንደ ክፉዎቹ አይረጋጋም ። ክፉዎቹ ቀጥተኛ ኑሮአቸው ሲሆን የእርሱ ግን መጨነቅ የወለደው ነውና ። ይህ ሰው ራሱን በክርስቶስ ካላየ አይድንም ። አንድ የእግዚአብሔር አገልጋይ እንዲህ ያለ ክርክር ውስጥ ካለ የሚያገለግለውን ሕዝብ እየጎዳ ይመጣል ። አገልግሎቱ ሁሉ መረበሽ ያለበት ፣ የዝቅተኛነት መንፈስ የሚያሰቃየው ይሆናል ። “እኔ ማን ነኝ ?” “ወላጆቼ እነማን ናቸው?” የሚል ክርክር በውስጡ ያለበት ሰው አለ ። የማይሞተውን ወላጅ ሥላሴን ይዞ የሚሞቱ ወላጆችን አጣሁ ብሎ መጨነቅ አይገባም ።
ከሰዎች ጋር ክርክር ውስጥ የገቡ ሰዎች አሉ ። እነዚህ ሰዎች በሰዎች መካከል እየተሟገቱ የሚኖሩና ብቻቸውን የሚኖሩ ሁለት መደብ ያላቸው ናቸው ። በሰዎች መካከልና ከሰዎች ርቀው የሚኖሩ በሰዎች ደረስብን የሚለውን እያሰቡ ቀኑን በሙሉ ሲከራከሩ ይውላሉ ። እነዚህ ሰዎች ይቅርታ ማድረግ በጣም የሚቸገሩ ፣ ዓለም ሁሉ ጠፍቶ ያለሁት እኔ ብቻ ነኝ የሚሉ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ምንም ነገር መስማትም ማየትም የማይፈልጉ ሲሆን ጥንቃቄአቸውን አልፎ ከሰሙና ካዩ ለሰዎች ያላቸው ጥላቻ ይበልጥ እየጨመረ ይመጣል ። ከዓመታት በፊት ሰዎች የተናገሩአቸውን እንደ አሁን ማሰብ ይጀምራሉ ። ከሰዎች ጋር ሲገናኙም የሚያወሩት ፣ ሰው ክፉ መሆኑን ነው ። ይህን አልፎ በፍቅር የሚያክማቸው ሰው ካገኙ  በጣም ጠቃሚ ሰዎች ይሆናሉ ። አሊያ ራሳቸውን የሚያክሙበት ዘዴ ይቅርታ ብቻ ነው ። ከሰው ጋር ክርክር ያላቸው ሰዎች አትኩረው የሚያዩና አጣርተው የሚሰሙ ናቸው ። ነገሮችን በመልካም ጎናቸው አይቶ ከመደሰት የችግሩን ክፍል መፈለግ ይቀናቸዋል ። አንድ አገልጋይ ከሰዎች ጋር ክርክር ካለው አገልግሎቱ የጎዱትን ሰዎች ለመንካትና ለመበቀል ይሆናል ። የንግግሩ ቃና ፣ የስብከቱ አድራሻ የጎዱት ሰዎች ይሆናሉ ።
ከእግዚአብሔር ጋር ክርክር ያላቸው ሰዎች በራሳቸው ሕይወት በደረሰባቸውና በሌሎች ሰዎች ሲደርስ ባዩት ክፉ ነገር እንዴት እግዚአብሔር ዝም አለ? ብለው ያዘኑ ናቸው ። ፍትሕ ሲጠፋ ፣ ሐሰተኛ ረታሁ ብሎ ሲጨፍር ፣ ደካማ ሲገፋ ፣ ጉልበተኛ ጣልኩኝ ብሎ ሲዘል ይህች ዓለም በእግዚአብሔር ተጥላ ያለ አስተዳዳሪ ቀርታለች ማለት ይጀምራሉ ። የጎዱአቸው ሰዎች እያበቡ እነርሱ ግን እየኮሰሱ የመጡ ሲመስላቸው እግዚአብሔርን መቀየም ይጀምራሉ ። ጸሎትን ሊያቆሙ ከመንፈሳዊ አገልግሎትም ሊወጡ ይችላሉ ።የእግዚአብሔር ፍርድ በእነርሱ ጊዜና እነርሱ በሚፈልጉት መንገድ ባለመከናወኑ ብስጩ እየሆኑ ይመጣሉ ። ክርክር ያለባቸው ሰዎች ወደ መንፈሳዊ ሹመት ከመጠራታቸው በፊት ሊለወጡ ይገባል ።
ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል ።
1ጢሞቴዎስ 43
ጥር 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም