የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የሚጠቅመው

 “እንደ እነዚህ ያሉ ነገሮች ክርክርን ያመጣሉና በእምነት ግን ላለ ለእግዚአብሔር መጋቢነት አይጠቅሙም ።” 1ጢሞ. 1፡4
በዚያ ዘመን ባለ ሀብቶች እርሻቸውና መኖሪያቸው የተለያየ ነበር ። በእርሻው ላይ ገበሬዎችና ልጆቻቸው ፣ ንብረትና ንግዶች አሉ ። ይህን ትልቅ ተቋም የሚያስተዳድር መጋቢ ሾመው ይሄዳሉ ። በዓመቱ ሲመጡ የገባውንና የወጣውን ሂሳብ ይተሳሰባሉ ። መጋቢውም እርሻንና ተክሉን መቆጣጠር ፣ ለገበሬዎቹ በጊዜ ደመወዝ መክፈል ፣ ቤተሰቡን መመገብ ፣ በሠራተኞች መካከል ጠብ እንዳይነሣ መንገዶች መዝጋትና ከተነሣም የማስታረቅ ኃላፊነት ነበረበት ። መጋቢውም በዓመቱ ጌታው ይቆጣጠረዋልና ገቢውንና ወጪውን በመዝገብ ተቆጣጥሮ ማስቀመጥ ነበረበት ። ጌታውም በመጣ ጊዜ ደስ ከተሰኘበት ሽልማት ይጠብቀዋል ። ባሮቹ ቀርበው ደብድቦናል ካሉ ፣ ቤተሰቡ ቀርቦ አስርቦናል ብለው አቤቱታ ካቀረቡ ከቦታው ይነሣ ነበር ። በደህና ለማስተዳደሩ ምስክርነት ካገኘ ፣ ሥራው ተመዝኖ ካለፈ የበለጠ ኃላፊነት ይሰጠዋል ። በጥቂቱ ታምኗልና በብዙ ይሾማል ።

መጋቢነት የእግዚአብሔር ሥራም ነው ። ሌሊትና ቀኑን ክረምትና በጋውን ማፈራረቁ ፣ ሁሉን ሳይሰለች እንደ ፍላጎቱ መሸከሙ ፣ በስህተቱ ይቅር ማለቱ መጋቢነቱ ነው ። መጋቢው እግዚአብሔር መጋቢዎችን ይሾማል ። እነዚህ አገልጋዮች ፣ የቃሉ ሠራተኞች እንደ እነርሱ ያሉትን አገልጋዮች መንከባከብ አለባቸው ። አገልጋይ በአገልጋይ መጨከን የለበትም ። “የእናቲቱ ደኅንነት የፅንሱ ደኅንነት ነው” ይባላል ። የአገልጋዮች ደኅንነት የምእመናን ደኅንነት ነውና መጋቢው ለአገልጋዮች ቅድሚያ መስጠት ይገባዋል ። እየራበው ከመጣ የሚያገለግለውን ሕዝብ ሊበላ ይችላል ፤ ሐሰትን ሊያስተምርና ውሸታም ነቢይ ሊሆን ይችላል ። የሚያጠፋው እንደ አቅሙ ነውና ቸል ሊባል አይገባውም ። ባሮቹን የሚደበድብ መጋቢ ይጠየቃል ። አገልጋይ ሁኖ አገልጋይን የሚጎዳም ይጠየቃል ። መጋቢው ቤተሰቡን መመገብ ወይም ምእመናንን በእግዚአብሔር ቃል ማጽናናት ይገባዋል ። የጣፈጠ ምግብ ለማቅረብም መዘጋጀት ያስፈልገዋል ። ስብከት መልእክት እንጂ ጩኸት አይደለም ። ስብከት የክርስቶስ ድምፅ እንጂ የንግግር ችሎታ አይደለም ። ስብከት የአእምሮ ጭማቂ ሳይሆን የመንፈስ ቅዱስ መገለጥ ነውና ተግቶ ማዘጋጀት ይገባዋል ። መጋቢው እርሻውን መቆጣጠር አለበት ። ያልታረመ ፣ ውኃ የበዛበትን መለየት አለበት ። ቸል የተባሉ ስህተቶችን በቶሎ ማስወገድ አለበት ። ቸልታ ዘርን ሲያመክን ፣ አረምን ግን የበለጠ ያሳድገዋል ። እንክበካቤ የበዛባቸውም ደካማ ሊሆኑ ይችላሉና ሁሉን በእኩል ማስተናገድ ይገባዋል ። በፊት ለፊት በር እያስገባ በኋላ በር እንዳያስወጣ መጠንቀቅ አለበት ። ትዕግሥቱ ስንፍና ፣ ትጋቱ መክነፍ እንዳይመስል መመርመር አለበት ። አንድ ቀን የሾመው ጌታ ሥራውን ይመዝናልና ያንን ቀን እያሰበ መትጋት ይገባዋል ። የባሮቹ ጠባይ ፣ የቤተሰቡ ሞራል ሳይሆን የእርሱ በደንብ ማገልገል ይታያልና ለራሱና ለአገልግሎቱ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልገዋል ። መጋቢ የቀን ሠራተኛ ሳይሆን የሙሉ ጊዜ ሠራተኛ ነውና ቀንና ሌሊት በሥራው ላይ መሆን ይገባዋል ።
“እንደ እነዚህ ያሉ ነገሮች ክርክርን ያመጣሉና በእምነት ግን ላለ ለእግዚአብሔር መጋቢነት አይጠቅሙም ።” 1ጢሞ. 1፡4
እንደዚህ ያሉ ነገሮች የተባሉት ልዩ ትምህርት ፣ ከቃሉ በላይ የሚከበር ተረትና የትውልዶች ታሪክ ናቸው ። እነዚህ ነገሮች ክርክርን ያመጣሉ ። ክርክር የሥጋ ሥራ ነው ፣ ዓላማው ማሳወቅ ሳይሆን የበላይ መሆን ነው ። የበላይ በመሆን ውስጥ ደግሞ ፍቅርና ትሕትና ይጠፋሉ ። መጋቢዎች በተለያየ ሁኔታ ይሆናሉ ። በእምነት ላለ መጋቢ ግን የማይጠቅሙ ነገሮች ክርክር የሚያመጡ ነገሮች ናቸው ። መጋቢዎች፡-
በሥጋ ይሆናሉ፡- ቦክሰኛ ፣ ካራቲስት ፣ ባለ ጥቁር ቀበቶ ተራጋጮች ፣ ባለ ሽጉጥ አገልጋዮች በልዩ ትምህርትና ተረቶች ተጠቃሚ ናቸው ። ወይም የሚጠቀሙ ይመስላቸዋል ።
በስሜት ይሆናሉ፡- ወቅታዊ ርእስን እንደ ሰበር ዜና የሚያስተጋቡ ፣ ለአሙቁልኝ የሚፈለጉ ፣ በእሳት ላይ ቤንዚን የሚጨምሩ ፣ እግዚአብሔርን በስድብ አስከብራለሁ የሚሉ በስሜት ያሉ አገልጋዮች በዚህ ነገር ይጠቀማሉ ። ክርክር ሲበዛ ገላጋይ ይሆናሉ ። ተረት ሲበዛ የተረት አባት ይሆናሉ ። የትውልዶች ታሪክ ሲነሣ ጎሣዬ ይህ ነው ይላሉ ። በዚህ ለመጠቀም ይሞክራሉ ።
በእውቀት ይሆናሉ፡- ይህ ቃል በዕብራይስጡ የለም ፣ በግሪኩ እንዲህ ይላል ፣ የላቲኑ ትርጉም አያነሣውም ፣ የሰባ ሊቃናት ትርጉም እንዲህ ይለዋል የሚሉ ሰዎች ክርክር ሲነሣ አለን ብለው ይገባሉ ። በዚህም አዋቂ ለመባል ይጥራሉ ። ክርክር ግን በእምነት ላለ መጋቢ አይጠቅምም ። ክርክር የበላይነትን ማስመስከር ነው ። እምነት ደግሞ የበታች ነኝ ማለት ነው ።
በእምነት ይሆናሉ፡- አገልጋዮች የሚጠቀሙትም ሆነ የሚጠቅሙት በእምነት ሲሆኑ ነው ። በእምነት ያለ አገልጋይ የማይታየውን እግዚአብሔርንና መንግሥቱን ያያል ። በሰው ዘንድ አንቱ ለመባልና ትልቅ ተብሎ ለመወደስ ጊዜ የለውም ። ክርክሮች እንዳይነሡ ይጥራል ። ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት ተረድተው ለክብሩ በሚመጥን ኑሮ እንዲገለጡ ይመክራል ። ሰማይን በማየት የምድሩን እንዲንቁ ያስተምራል ።
የሚጠቅመውን እንድንይዝ እግዚአብሔር ይርዳን !
1ጢሞቴዎስ /9/
ኅዳር 14 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ