የትምህርቱ ርዕስ | የተዘረጋው ጥላ

“ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከክርስቶስ ኢየሱስም ከጌታችን ጸጋና ምሕረት ሰላምም ይሁን 1ጢሞ 1፡2
በዚህ ዘመን ሦስት ነገሮች ያስፈልጋሉ ካልን ጸጋ ፣ ምሕረትና ሰላም ናቸው ። የሰው ልጆች ኑሮ የመጠባበቅ ፣ ምን እሰጣለሁ ? ሳይሆን ምን እቀበላለሁ ? የሚል ስሌት ውስጥ ከገባ ዓመታት ተቆጥረዋል ። ጸጋ ማለት የማይገባ ደግነት ነው ። ለማይገባቸው ሰዎች የማይገባቸውን ነገር ካላደረግን ይህን ዘመን መሻገር ይከብዳል ። ሰዎች እኔ ተጎዳሁ እንጂ ሌላውን ጎድቻለሁ ለማለት የሞራል ከፍታን ማግኘት አልቻሉም ። በሕይወት ውስጥ ትልቁ የሞራል ከፍታ አልቻልኩም ብሎ አቅምን ማወቅና አጥፍቻለሁ ብሎ በደልን ማመን ነው ። ሁሉን ነገር ለእኔ ብቻ ማለት ፣ እንደሚበሉት ሳያረጋግጡ መሰብሰብ ፣ የራስን ስሜት እንጂ የጎረቤትን አለማዳመጥ ዕለት ዕለት እየበዛ ነው ። በነጻ ማፍቀር አይቻልም ፣ ለማያውቁትና ምንም ላላደረገ ሰው ውለታ መዋል እብደት ነው የሚል አስተሳሰብ እየፈላ ነው ። ሰዎች ራሳቸው ማድረግ ያቃታቸውን ደግነት ሌሎች ሲያደርጉት እውነት ነው ብለው ከመቀበል ውሸት ነው እያሉ ማጣጣል አብዝተዋል ። ጸጋ ማለት ቀድሞ ማፍቀር ፣ ቀድሞ መልካም ማድረግ ፣ በራስ ፍቅር ላይ ተመሥርቶ ያንን ወገን መውደድ ፣ ብድር መላሽነቱን ሳያገናዝቡ ስጦታን መስጠት ነው ። አመሰግናለሁ ሲባሉ የሚሰጡ ሰዎች ምላሽ ሲያጡ ያቆማሉ ። ዘመኑ ሰዎች ሲደረግላቸው ይገባኛል ብለው የሚያስቡበት ፣ መንፈሳዊነት ሳይሆን ሰብአዊነት እየጠፋ ያለበት ነው ። ይህን ዘመን የጸጋ መንገድ ካልሆነ ምንም ሊታደገው አይችልም ።

ሁለት ነገሮች እየደበዘዙ እንዳይመጡ ያሰጋል ። ለተቸገሩት እንጀራ ፣ ለበደሉን ይቅርታ መስጠት እንዳይከዳን ያስፈራል ። ችግረኛውን ስናይ ውስጣችን የቀን ገቢያቸው ይህን ያህል ደርሷል ፣ ሠርተው አይበሉም ወይ ? ይላል ። ብንሰጥም በፍጹም ለጋስነት ሳይሆን በመጠራጠር ነው ። ነፍሳቸው ታስራ ይቅርታ የሚለምኑን ሰዎችን ይቅርታ መስጠት አለብን ። ታስረዋልና ምንም መንቀሳቀስ አይችሉም ። ትልቁ ችግራቸው የጸሎት መንገዳቸው ዝግ መሆኑ ነው ። ሌላውን አሳዝኖ መጸለይ በእግዚአብሔር መቀለድ ነው ። አንድ አባትን ልጁን ገድለህበት ጮማ ብትቆርጥለት ደስ ይለዋልን ? የሰዎችን ልብ ሰብሮ መጸለይም ወደ ተዘጋ ሰማይ መገስገስ ነው ። ዛሬ ጸሎት አላነሰም ፤ ንጹሕ ልብ ግን እየጠፋ ነው ። ሌላው ችግር በጸሎት ይፈታል ፣ የጸሎት መስመር ከተዘጋ ግን በምንም ይከፈታል ? ከምህላ በፊት ይቅርታ እንደሚያስፈልግ እንዴት ተዘነጋ ?
በእውነተኛ ልብ ሁነው ይቅርታ የሚጠይቁ መሳሳታቸውን አምነዋልና ይቅርታችንን ልንሰጣቸው ይገባል ። ምሕረት ማለት ለተራበ እንጀራን ፣ ለበደለ ይቅርታን መስጠት ነው ። ጥሩ የለበሱ ሰዎች ጥሩ መብላታቸውን እጠራጠራለሁ ። ልብስ የዓመት ነው ፤ ሆድ ግን የዕለት ነው ። አምና በገዙት ልብስ እንዳንለካቸው መጠንቀቅ ያስፈልጋል ።
ሰላም ዕለታዊ ርእስ ፣ የመንግሥታት ስብሰባ አጀንዳ ናት ። ሰላም እንዳይመጣ የሚጥሩ ብዙ ወገኖች አሉ ። የጦር መሣሪያ ነጋዴዎች ፣ የሕዝብ ቊጥር እንዲቀንስ የሚያሰሉ አዋቂ ተብዬዎች ፣ በዕዳ የሚፈለጉ ወንጀለኞች ፣ መኖርን የተመረሩ ስልቹዎች ፣ ሥራን ጠልተው በመዝረፍ መክበር የሚሹ የጥፋት ጓዶች ፣ ትዕቢት ያነቃቸው ነገሥታቶች ፣ ግላዊ ጉዳታቸውን አገራዊ የሚያደርጉ ተገፊዎች እነዚህ ሁሉ ሰላምን አይፈልጉም ። ሰላም እንዳይሆንም ይጥራሉ ። ሰላም ስትያዝ እርካሽ ፣ ስትጠፋ ግን ውድ ናት ። ሰላም በማጣት ገበሬ የዘራውን አያጭድም ፣ ነጋዴ ሮጦ አያተርፍም ፣ የተለያየው ወገን አይገናኝም ፣ ልጆች ለድንጋጤና ለአእምሮ ስብራት ይዳረጋሉ ፣ በሽተኞች መታከም አይችሉም ። ጤና ባይኖር በገንዘብ ለመዳን ይሞከራል ። ገንዘብ ባይኖር በጤና መጽናናት ይቻላል ። ሰላም ግን ሁሉም ነገር ነውና ከራሱ ውጭ ምንም ምትክ የለውም ። ሰላም ብንሆን እንኳ በቀጣይ አሥር ዓመታት ማደግና መለወጥ ከቻልን መልካም ነው ። አንድ ቀን ሰላም ስናጣ የአንድ ዓመት ዕድገታችን ይዘገያል ። ሰላም መጣት የዛሬ ቊስል ፣ የነገ ጠባሳ ነው ። ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ሰላም ያስፈልገናል ። ሰላም ግን ዋጋ ያስከፍላል ። ከእኔ ይቅር ካላሉ ሰላም ከየት ይገኛል ?
ሐዋርያው፡- “ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከክርስቶስ ኢየሱስም ከጌታችን ጸጋና ምሕረት ሰላምም ይሁን” ብሎ መመረቁ እውነት ነው ። የእግዚአብሔር ሰዎች የሚያዩበት መነጽር ረቂቅ ነውና ሐዋርያው የጎደለንን በትክክል አውቋል ።
ጸጋ ፣ ምሕረትና ሰላም የሚገኙት የእግዚአብሔር አባትነት የክርስቶስ ጌትነት ሲገባን ብቻ ነው ። የእግዚአብሔርን አባትነት ስንረዳ ጸጋን የምንቀበል ብቻ ሳይሆን በጸጋ የምንለቅቅ እንሆናለን ። ምሕረት ተደርጎልናልና እንደ ተቀበልነው ለመስጠት አንፈተንም ። ሰላምን አግኝተናልና ሌላውን አናውክም ። የክርስቶስ ጌትነትም ሕይወታችንን ሲገዛ ጸጋ እናገኛለን ። ጸጋ ማለት የዘላለም ሕይወት ነው ። ይህ የሚገኘው ወልድ ዋሕድ ፣ ቤዛ ኩሉ ዓለም ብሎ በክርስቶስ በማመን ነው ። በክርስቶስ ጌትነት የምናገኘው እንጀራን ብቻ ሳይሆን በየዕለቱ የኃጢአት ይቅርታን ነው ። ይህም ምሕረት የተባለው ነው ። የእግዚአብሔር ሥልጣን ባይኖር የአንድ ቀን እንጀራ መቊረስ ባልቻልን ነበር ። እርሱ ባይሆንም እኛን ይቅር የሚል አይኖርም ነበር ። እርሱ ይቅር ላለንም የሚበሳጩ ብዙ ፈሪሳውያን አሉ ። ሰላሜን እሰጣችኋለሁ በማለት ኪዳን የገባልን ክርስቶስ ኢየሱስ ነው ። ሰላም የእርሱ መለኮታዊ ገንዘብ ናት ።
ብዙ ሰው በነፍሱ እየባከነ ነው ። እኔን የሚቀበል አምላክ የለም እያለ ለገዛው ነገር እንደገና እየተገዛ ለመኖር የወሰነ ነው ። ስብከቶችም ፍርድ እንጂ ወንጌል አይደሉም ። የሚያደናብር ፣ በሌላው ኃጢአት የራሱን ጽድቅ የሚሠራ ሰባኪ አያሌ ነው ። በዚህ ዘመን ጸጋ ወይም የሥላሴ ቸርነት አብዝቶ ሊነገር ይገባዋል ። “ደም በደም አይጠራም” እንዲሉ ኃጢአት በሌላ ኃጢአት አይወገድም ። የክርስቶስ ደም ለምሕረት ቁሟል ። እኔ አልድንም በማለት ዘወትር ሰላም በማጣት ፣ በሱስ ውስጥ የተደበቁ አያሌ ወገኖች አሉ ። አይዟችሁ እግዚአብሔር እናንተን በጸጋው ወዶአችኋል ። በምሕረቱም ነፍሳችሁን ከእስራት ይፈታል ። ሰላሙንም ሰጥቶ የጨው ውኃ ከመጠጣት ፣ ወይም ከኃጢአት ደስታን ከመፈለግ ያድናችኋል ።
የሐዋርያው ምርቃት በራሳቸው ብቃት ለሚመጻደቁ አሜን የሚያሰኛቸው አይደለም ። እኔ ኃጢአተኛ ነኝ የምትሉ ግን አሜን በሉ ። በአሚነ ሥላሴም ጽኑ ። ንስሐ ግቡ ፤ የበደላችሁትን ሰው ይቅርታ ጠይቁ ። በልባችሁም እንዲህ ጸልዩ፡-
ጌታ ሆይ ከአሉተኛ ትውልድ ፣ ይህን አሉ ከሚል ማንነትም አድነኝ ። የተዘረጋልኝን የቸርነትህን ጥላ እንድጠለልበት እፈልጋለሁ ። ምሕረትና ሰላምህ ከእኔ ጋር ይሁን ። ያለፈውን ዘመን ስህተቴን ይቅር በል ። ለዘላለሙ አሜን ።
1ጢሞቴዎስ /7/
ኅዳር 11 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም