መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ /8

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ /8

የመዘጋጀት ዘመን ያደረገው አስተዋጽዖ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ የነበሩት ምቹ ሁኔታዎች ወንጌል በዓለም ሁሉ እንዲስፋፋ ትልቅ አስተዋጽዖ አድርገዋል ። ዓለም አይሁድና አሕዛብ ተብሎ በሁለት የተከፈለበት ዘመን ነበር ። አይሁድ የሚባሉት አንድ አምላክን የሚያመልኩና በመገለጥና በመጽሐፍ የሆነ እምነት ያላቸው ሲሆኑ አሕዛብ ደግሞ ከእነርሱ የሚያንሱ ፍጥረታትን የሚያመልኩ እምነታቸውንም በተረትና በፈጠራ ላይ የመሠረቱ ነበሩ ። እግዚአብሔር ትክክለኛ ጊዜን የሚያውቅ የጊዜ ድሀም ያልሆነ አምላክ ነው ። ጌታችን በሥጋ ሲመጣ የነበሩት መዘጋጃዎች፡-

1- የሮም መንግሥት በዓለም ላይ መስፋፋት
  በዓለም ላይ ሰልጥኖ የነበረው የግሪክ መንግሥት እየተዳከመና እየተከፋፈለ ሲመጣ የተካው ተረኛ ኃያል የሮም መንግሥት ነበር ። የሮሙ ጀነራል ፖምፔ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ63 ዓመት ኢየሩሳሌምን ተቆጣጥሮ ይሁዳን የሮም አካል ሲያደርግ ያን ጊዜ የሮም መንግሥት በዓለም ላይ ማንሠራራት ጀመረ ። ይህም መንግሥትም እስከ 476 ዓ.ም. ድረስ ለአምስት መቶ ዓመታት ያህል የቆየ ነው ። በርግጥ በሦስተኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ ምሥራቅና ምዕራብ ተብሎ ለሁለት የተከፈለ መሆኑን አንረሳም ። የሮም መንግሥት ለዓለም ሰላም አስገኝቻለሁ ብሎ የሚያምን ሲሆን በርግጥም ሰላምን በማስገኘቱ የተመሰገነ ነበር ። መላውን ዓለም በመንገድ ፣ በባሕር መጓጓዣ አገናኝቶት ስለነበር በቀላሉ ካንዱ አገር ወደ አንዱ አገር መሄድ ይቻል ነበር ። የይለፍ ወረቀትም ስለማይጠየቅ ወደ ፈለጉበት አገር ያለ ጠያቂ መንቀሳቀስ ይቻል ነበር ። ሐዋርያት በዓለም ላይ ዞረው ወንጌልን ለመስበክ ምቹ መንገዶችና ድንበር አለመኖሩ በብርቱ አግዟቸዋል ። ዛሬ ቢሆን ኑሮ ጳውሎስና ጴጥሮስ ወንጌል ለመስበክ የቪዛ ማመልከቻ መጠየቅ ያስፈልጋቸው ነበር ። እግዚአብሔር ግን ጊዜን የሚያውቅ በመሆኑ በዚያ ጊዜ በሥጋ መጣ ። ሐዋርያትንም ወደ ዓለም ላከ ።
2-  የዓለም ቋንቋ አንድ መሆኑ

የግሪክ መንግሥት ቢወድቅም ቋንቋውና የፍልስፍናው ተጽእኖ ግን እንደ ቀጠለ ነበር ። ውጫዊ የሆነ አገዛዙ ቢወድቅም ረቂቅ አገዛዙ ግን ዘመን ተሻግሮ ነበር ። ታላቁ እስክንድር የሄደው በጦር ኃይል ብቻ ሳይሆን በጥበብም ነበር ። የግሪክ ቋንቋ እንደ ዛሬው እንግሊዝኛ የመላው ዓለም መግባቢያ ሁኖ ነበር ። አዲስ ኪዳንም ከማቴዎስ ወንጌል ውጭ በግሪክኛ ተጽፎአል ። የሚበዛው የዓለም ሕዝብ ግሪክኛ ተናጋሪ መሆኑ ለመዘጋጃው ዘመን አስተዋጽዖ አድርጓል ።
3-  የቅዱሳን መጻሕፍት መተርጎም

   ከክርስቶስ ልደት 284 ዓመት ቀደም ብሎ በታላቁ እስክንድር በተሰየመችው ላዕላይ ግብጽ እስክንድርያ በተባለችው የወደብ ከተማ ብሉይ ኪዳን ከዕብራይስጥ ወደ ግሪክ ቋንቋ ተተርጉሟል ። በእስክንድርያ ተቀምጠው የተረጎሙት ሰባ የአይሁድ ሊቃውንት ሲሆኑ ትርጉሙም “የሰባ ሊቃናት ትርጉም” ተብሎ ይጠራል ። በእስክንድርያ ከተማ ትልቅ ቤተ መጻሕፍት ተቋቁሞ የመላው ዓለም ጽሑፎች ተቀምጠውበት ነበር ። በዚህ ቤተ መጻሕፍትም ከ700 ሺህ በላይ መጻሕፍት ተቀምጠው ነበር ። በዚህ ቤተ መጻሕፍት ውስጥ የብሉይ ኪዳን ቅጂ አለመኖሩ ስላሳሰባቸው ሰባ የአይሁድ ሊቃውንት ተሰብስበው ብሉይ ኪዳንን ወደ ግሪክ ቋንቋ ተርጉመዋል ። በዚህም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በዓለም መነበብ ጀመሩ ። አሕዛብም ስለ አንዱ አምላክና ስለ ክርስቶስ መምጣት ማሰብ ጀመሩ ። ይህም ለአዲሱ ኪዳን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነበር ።

4- የአይሁድ በመላው ዓለም መበተን

    አይሁዳውያን ከባቢሎን ምርኮ በኋላ ከአገራቸው ውጭ መኖር ጀምረው ነበር ። የአምልኮ ማዕከላቸው መቅደሱ ስለ ነበር ወደ ኢየሩሳሌም ሦስቱን በዓላት ለማክበር ይመለሱ ነበር ። በ70 ዓ.ም መቅደሱ በመደምሰሱ ግን የአምልኮ ማዕከላቸው የሆነው ኦሪት ነበር ። በአገሩ ከሚኖረው አይሁዳዊ በዝርወት የሚኖረው አይሁዳዊ በልጦ ነበር ። አይሁዳውያን በሚሄዱበት አገር ባሕላቸውንና ሃይማኖታቸውን ይዘው ስለሚሄዱ አሕዛብ ስለ አንዱ አምላክ የማወቅ ዕድል አግኝተዋል ። ይህም መልካም የመዘጋጃ ዘመን ሁኖ የአዲስ ኪዳንን አገልግሎት አቅልሎታል ።
 ጌታችን በሥጋ በተገለጠበት ዘመን የነበረው የዓለም ሁኔታ ባዕድ አምልኮ የተስፋፋበት ዘመን ነበር ። ለእያንዳንዱ ፍጥረት በነፍስ ወከፍ አምላክ እየሰጡ የፀሐይ አምላክ ፣ የዝናብ አምላክ ፣ የጦርነት አምላክ እያሉ የሚያመልኩበት ዘመን ነበር ። የአምልኮ ምንዝርና በብርቱ የነገሠበት ዘመን ነበር ። በዚህም ጣዖት በመጥረብ የሚተዳደሩ ብዙ ሠራተኞችን ፈጥሮ ነበር ። ከአምልኮ ምንዝርና ባሻገር የጌታና የባሪያ ሥርዓት በዓለም ላይ ሰፍኖ ነበር ። ባሮች ሰውነታቸው ተዘንግቶ እንደ ከብት ይሸጡ ይለወጡ ነበር ። ሰውም ሀብቱን የሚለካው ይህን ያህል ባሪያ አለኝ በማለት ነበር ። ባሪያው የጌታው ዕቃ ስለሆነ ጌታው ቢገድለው ንብረቱ ስለሆነ አይጠየቅም ነበር ። ሴቶችም እንደ ተንቀሳቃሽ ዕቃ ይታዩ ነበር እንጂ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው ክብረት ገና አልታወቀም ነበር ። ሐዋርያው፡- ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ” ብሎ መናገሩ የራሱ ምሥጢርም ነበረው ። /ገላ. 4፡4/ በዚያ ዘመን ፍልስፍና ሴት ልጅ ፣ ልጅን በማስገኘት ሂደት ውስጥ ምንም ተሳትፎ የሌላት ማኅፀኗ እንደ ኪራይ ቤት ብቻ ይታሰብ ነበር ። ጌታችን የሴት ዘር ሁኖ መምጣቱ ይህን ፍልስፍና ጭምር ድል የነሣ ነው ።
 ጌታችን በሥጋ በተገለጠበት ዘመን በምድረ እስራኤል የነበረው ሁኔታ ተስፋ የማይጣልበት ፣ ሕዝብ በሥራ አጥነትና በፍርድ መዛባት የሚያለቅስበት ዘመን ነበር ። የአእምሮ ጭንቀትም በብዙ ተስፋፍቶ ነበር ። የሃይማኖት ቡድኖች ቊጥራቸው ቢበዛም አንዳቸውም ዕረፍትን ማምጣት አልቻሉም ነበር ። በሃይማኖት ቡድኖች መካከል የሚነሣው ፍጭትም ሕዝቡን ሜዳ አድርጎ የሚከናወን በመሆኑ አብዛኛው ወገን የመንፈስ ዝለት ገጥሞት ነበር ። ጌታችን ሲመጣ የነበሩት የሃይማኖት ቡድኖች እነማን ናቸው ?
ይቀጥላል
አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም