መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/6

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/6

የቤተ ክርስቲያን ምሥረታ
ቤተ ክርስቲያን እንደትመሠረት ምክንያት የሆነው የአዳም በበደል መውደቅ ነው ። አዳም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፉ ምክንያት ለራሱና ለልጆቹ መከራ አምጥቶአል ። መሪውን የያዘው ሾፌር ወይም ካፒቴን ተሳፋሪውን ያደርሳል ወይም ገደል ይዞ ይገባል ። አዳምም መሪ ነበርና እርሱ ሲስት ትውልዱ ሁሉ የሳተ ሆነ ። አዳም መንገድ እንደ ጠፋውና እንደ ወደቀ እግዚአብሔር አምላክ “ወዴት ነህ ?” በማለት ባሰማው ድምፁ ታውቋል ። ዘፍ. 3፡10 ። ኃጢአት የሚለው ቃል በዕብራይስጡ “ዓላማ መሳት” የሚል ፍቺ አለው ። ለአዳም በቀጥታ ትእዛዝ የሰጠው ራሱ እግዚአብሔር ሲሆን ሔዋንን በቀጥታ ያማከረው ደግሞ ራሱ ሰይጣን ነው ። አዳም ከእግዚአብሔር የሰማውን በትክክልና በሰማበት ሙቀት ለሔዋን አልነገራትም ፣ ሔዋን ግን ከሰይጣን የሰማችውን በሰማችበት ግለት ነገረችው ፣ መንገድ አጋምሳም ጠራችው ። ትእዛዝ ዋጋ የሚኖረው ሲፈጽሙት ሰላም ፣ ካልፈጸሙት ቅጣት ሲኖረው ነው ። አዳም እንዲሁ ቢታለፍ እግዚአብሔር የገዛ ትእዛዙን እንደ ናቀ ይቆጠራል ። ራሱን የማይክድ ፍትሐ ጽድቅ ያለው እግዚአብሔር በአዳም ላይ ሞትን ፈረደበት ። ልጅ የአባቱን ሀብት ብቻ ሳይሆን ዕዳም ይወርሳልና የአዳም ልጆች ከአዳም የሞትን ዕዳ ወረሱ ።

እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ከገነት ሳያስወጣው ወደ ገነት እንደሚመለስ ተስፋ ሰጠው ። ዘፍ. 3፡15 ። ከዚህ በኋላ እርሱ የሚመራው የሰው ልጅ ማኅበር ማኅበረ ሙታን ስለሚሆን የሕያዋን ማኅበር የምትሆን ቤተ ክርስቲያን እንደምትመሠረት ተስፋ ሰጠው ። ይህም ዳግማዊ አዳም ሁኖ በሚመጣው በክርስቶስ የሚፈጸም ነው ። ዳግማዊ አዳም ክርስቶስም የአዲሲቱ ዓለም የቤተ ክርስቲያን መሥራችና ራስ ነው ። የቤተ ክርስቲያን ምሥረታ በገነት የተነገረ ሲሆን አዳም ገነትን በአካል ለቆ ቤተ ክርስቲያንን በልቡ ይዞ ወጣ ።
ይህ ታላቅ ተስፋ የተነገረው ለሰይጣን ነው ። አዳምና ሔዋንን በመጣሉ ፈጽሞ ደስ እንዳይለው በተስፋ ቃል ደስታውን አቋረጠው ። ሰይጣንም አዳኙ ዘር የሚወጣበትን ወገን ለማጥቃት ከጠዋቱ ውጊያና ሰልፍ ጀመረ ። ያ አዳኝ ዘር ከማን እንደሚወለድ መንገዱ ጥርት ብሎ መታየት የጀመረው አብርሃም በተጠራ ጊዜ ነው ። ዘፍ. 12፡1 ። መሢሑ የሚወጣበት ዘር አውራ ጎዳናው ታየ ። አብርሃም ይስሐቅን ወለደ ፣ ይስሐቅም ያዕቆብን ወለደ ። ያዕቆብም የእስራኤል መሥራች የነበሩትን አሥራ ሁለት የነገድ አለቆች ወለደ ። ያዕቆብ ሰባ ነፍስ ሁኖ ወደ ግብጽ ገብቶ ነበር ። ከ215 ዓመታት በኋላ ግን ሕዝቡ ግማሽ ሚሊየን አለፈ ። እግዚአብሔርም በታላቁ የነጻነት ታጋይ በሙሴ በኩል እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ነጻ አወጣ ። አገር አልባ ሁነው የኖሩበት ጠቅላላው ዘመን 430 ዓመት ሲሆን በግብጽ የቆዩት ግን 215 ዘመን ነው ። የ430 ዓመታት የባርነትና የስደተኛነት ዘመን አበቃ ። ባለማመናቸው ምክንያት የአርባ ቀኑ መንገድ አርባ ዓመት ፈጀባቸው ። በሙሴ የተጀመረው የተስፋይቱ አገር ጉዞ በኢያሱ ተጠናቀቀ ። ኢያሱ ርስትን አካፍሎ ሁለተኛው መስፍን ሆነ ። ከኢያሱ ሞት በኋላ 13 የሚሆኑ መሳፍንት አስተዳደሩአቸው ። ይህም ለ300 ዓመታት መሆኑ ነው ። ዘመነ መሳፍንት እንዳለፈ “ዘመነ ነገሥት” መጣ ። የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳኦል ሲሆን ሁለተኛው የእስራኤል ንጉሥ ዳዊት ነው ። ዳዊትም መሢሑ የሚወጣበት ዘር በመሆኑ ከአብርሃም በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ መሢሑ የሚወጣበት አውራ ጎዳና ፍንትው ብሎ ታየ ።
ከዳዊት በኋላ እስራኤልን ያስተዳደረው ጠቢቡ ሰሎሞን ነው ። ከሰሎሞን በኋላ ልጁ ሮብዓም ነገሠ ። እስራኤልም ቀንበር እንዲያቀልላቸው ጠየቁት፤ እርሱ ግን ከቢጤዎቹ ጋር በመምከሩ በእልህ እስራኤል ለሁለት ተከፈለች ። /1ነገሥ.12 ።/ አሥሩ ነገድ ከዳዊት ሥርወ መንግሥት ተነጥሎ የንግሥና ዘር ያልነበረውን ኢዮርብዓምን አነገሠ ። የግዛቱ ስም እስራኤል ፣ የግዛቱ አውራጃ ሰማርያ ፣ መናገሻ ከተማውም ሴኬም ሆነ ። ለዳዊት ቤት ሁለት ነገድ ቀረ ። የይሁዳና የብንያም ነገድ ። በዚህም የደቡብ ግዛት ይሁዳ ፣ መንግሥቱም የይሁዳ መንግሥት ተባለ ። መናገሻ ከተማዋም ኢየሩሳሌም ነበረች ።መለያየት ግን ጥፋትን እንጂ ልማትን አምጥቶ አያውቅምና  ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ722 ዓመት የሰማርያ ግዛት ወይም የእስራኤል መንግሥት በአሦራውያን ተወረረ ። አሦራውያን የአገራቸውን ዱርዬዎች አምጥተው በሰማርያ አፈሰሱ ። የእስራኤልን ክብር የሚያውቁ ፣ ታሪክ አዋቂ ሽማግሌና ምሁራንን ማርከው ወደ አሦር ወሰዱ ። የቀረው ሕዝብ ከአሦራውያን ጋር በጋብቻ ተቀላቀለ ። ማንነቱን እንዳያውቅ ምሁር አልባ ሆነ ። በዚህም ሳምራውያን ቅይጥ ሕዝቦች ተብለው በደቡብ ከሚኖሩት ጋር በፖለቲካ ብቻ ሳይሆን በሃይማኖትም ተለያዩ ።
የሰሜኑ ዕጣ በደቡቡ ደረሰ ። በ586 ዓመት ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ባቢሎናውያን የይሁዳን መንግሥት አፍርሰው ፣ ታላቁን መቅደስ አቃጥለው ፣ የኢየሩሳሌምን ቅጥር እንዳልነበር አድርገው ሕዝቡን ማርከው ወሰዱት ። የምርኮው ዘመናት ሰባ ዓመታት ፈጀ ። ከሰባ ዓመታት በኋላ መቅደሱን እንደገና ሠሩ ። የመጀመሪያው በሰሎሞን ፊታውራሪነት ስለተሠራ “የሰሎሞን መቅደስ” ይባል ነበር ። ሁለተኛው መቅደስ በዘሩባቤል መሪነት ስለ ተሠራ “የዘሩባቤል መቅደስ” ይባላል ። ኢየሩሳሌምም ቅጥሯ ታድሶ ብትኖርም መንግሥቷን መመሥረት ግን አልቻለችም ነበር ። እስከ ክርስቶስ መምጣት ድረስ ያስተዳድሩ የነበሩት ካህናት ነበሩና ጊዜው “ዘመነ ካህናት” ተብሎ ይጠራል ። የዓለም ፖለቲካም በየጊዜው እየተለዋወጠ ተረኛ ኃይለኛ ሲመጣ እስራኤልን አላለፋትም ። የባቢሎን አገዛዝ እንደ ወደቀ የፋርስና የሜዶን ጥምር መንግሥት ቀጠለ ፣ ከዚያም የታላቁ እስክንድር ግሪካዊ መንግሥት በዓለም ላይ ተንሠራፋ ። እስራኤል አሁን በግሪካውያን እጅ ወደቀች ። የግሪካውያን ተራ ሲያበቃ የሮማውያን አገዛዝ ሰፈነ ። ታላቁ እስክንድር ለጥበብ ያደላ ነበርና የአይሁድ እምነት ባለ መጽሐፍ በመሆኑ ፣ በአደረጃጀቱም እንከን አልባ በመሆኑ እውቅና ሰጥቶት ነበር ። ሮማውያንም ያንን እውቅና ተቀብለው አክበረዋቸዋል ። ነገር ግን ቅኝ አድርገው መግዛታቸው አልቀረም ። ለአጥቢያውም ሹም እንዲሆን ታማኝነትን ያሳየውን ኤዶማዊውን ሄሮድስን የሮሙ ቄሣር ሮም ላይ ቀባው ። የሄሮድሳውያን መንግሥትም ከክርስቶስ ልደት 37 ዓመት ቀደም ብሎ ጀመረ ። የአይሁድን ሃይማኖት ተቀብለው ነበርና ትልቁ ሄሮድስ የዘሩባቤል መቅደስ እንዲስፋፋና እንዲጠገን ሥራ ጀመረ ። በዚህም የአይሁድን ቀልብ የሳበ ይመስላል ። ጌታችን በምድር ላይ ሲመጣ ይህ መቅደስ በእድሳት ላይ ነበረ ። መቅደሱም እድሳቱ አልቆ የተመረቀው በ64 ዓ.ም. ነው ። የሚገርመው በ70 ዓ.ም. በሮማውያን ተደመሰሰ ።
ሮማውያን ግዛታቸውን በመላው ዓለም አስፍነው ሳለ ጌታችን ተወለደ ። ማደሪያው ትሆነው ዘንድ የመረጣት በሁለት ወገን ድንግል የሆነችውን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው ። የሔዋን አለመታዝዝ ሁልጊዜ እንዳይወራ የድንግል ማርያም መታዘዝ እንደ ገታው እንረዳለን ። እርሷም ሰማይና ምድር የማይችሉትን ጌታ በማኅፀኗ ተሸከመችው ። ታላቅም ተአምርና ሊነገር የማይችል ምሥጢር በድንግል ማርያም ላይ ተከናወነ ። ይህም ምሥጢር ወንጌል በተነገረበት ስፍራና ዘመን ሁሉ ሲወሳ ይኖራል ። ከብፅዕት ድንግል በቤተ ልሔም የተወለደው ጌታ ለዕድገቱ የሽፍቶቹን ከተማ ናዝሬት መረጠ ። ሞቱም በኢየሩሳሌም ሆነ ። በቀራንዮ ገድለውት እርሱ ግን በጎልጎታ ተነሣ ። እያዩትም ሽቅብ ወደ ሰማይ ዐረገ ። እርሱ የአዲሲቱ ዓለም መሥራች ነውና “ዳግማዊ አዳም” ይባላል /1ቆሮ. 15፡45/ ። የአዲሲቱ እስራኤል መሪ ነውና በያዕቆብ ወገን ላይ ለዘላለም ይነግሣል ተባለለት ። /ሉቃ. 1፡33/።
እስራኤላውያን መንግሥታቸው ከፈረሰ 400 ዓመታት በላይ ሆነ ። ይህ ዘመንም ነቢያት ያልተነሡበት ዘመን ነበር ። ነቢያት የሚላኩት ለአገራዊ አጀንዳ እንጂ ለሽሮና ለበርበሬ ስላልሆነ መንገሥት ሲፈርስ የነቢያት አገልግሎትም ቆመ ። አስራኤልም አንድ ተስፋ ብቻ በልባቸው ቀረ ። መሢሑ ሲመጣ የጦር ሰዎችን አሰባስቦ ከሮማውያን ጋር ተዋግቶ ነጻ ያወጣናል ። እኛን የቅርብ ባለሟሎቹ አድርጎ በመላው ዓለም ይነግሣል እያሉ መጠበቅ ጀመሩ ። “ዶሮ ብታልም ጥሬዋን” እንዲሉ ። መሢሑን ያልተቀበሉት እንደ ጠበቁት ስላልተገለጠ ነው ።
እስራኤል በአሥራ ሁለት የነገድ አለቆች እንደ ተመሠረተች ቤተ ክርስቲያንም በአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ተመሠረተች ። የልደት ቀኗንም በበዓለ ሃምሳ የመንፈስ ቅዱስ ድግስ አክብራ ሥራዋን ጀመረች ። የተነሣቸው የምድርን ዳርቻ የግዛት ጠረፍ አድርጋ በመሆኑ ዓለም አቀፋዊት ናት ። ሥራዋንም መሥራቿ የሆነው ክርስቶስ እስኪመጣ ድረስ እስከ ዓለም ፍጻሜ ትቀጥላለች ። /ማቴ. 28፡20/
የአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ስምና አገልግሎት በአጭሩ ምን ይመስላል ?
ይቀጥላል
አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ አንብቡ ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም