መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » የሬሳ ቁንጅና

የትምህርቱ ርዕስ | የሬሳ ቁንጅና

 “እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን ፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ ፥ ወዮላችሁ ።” ማቴ. 23፡27
የትያትር መነሻ ፣ ታሪካዊ ዳራው በዘርፉ ባለሙያዎች ሊተነተን ይችላል ። ትያትር ግን የጀመረው በሃይማኖት ስም በሚደረግ ጥፋት ነው ። የትያትሩ ጀማሪም ቃየን ነው ። ቃየን መሥዋዕት ሲያቀርቡ አይቶ ያቀረበ ነው ። መሥዋዕት ማቅረብ የሚጠይቀው ሀብት ነው ፤ ልብን ለማቅረብ ግን የሚጠይቀው ሃይማኖት ነው ። መሥዋዕት ያለ ልብ ለበጣ ነው ፣ መሥዋዕት ከልብ ጋር ፍቅር ነው ። የልብ አማኝና የታይታ አማኝ አቤልና ቃየን ናቸው ። ተዋናዩ ቃየን ወንድሙን ገደለ ። ቃየን ፍሬን መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ ጀመረ ፣ ወንድሙን በመግደል ፈጸመ ። ግብዝነት ቁራሽ ጽድቅ ሲያሳይ መደምደሚያው ግን መግደል ነው ። ግብዞች የዘመናቸው ጠላት እውነተኛ ሰው ነው ። ሐሰታቸውን ያጋለጠባቸው ስለሚመስላቸው ፣ እውነተኛውን ሰው በሞት ያርቁታል ። ጻፎችና ፈሪሳውያን ሕጉን በቃላቸው የሚያውቁ በኑሮአቸው ግን የካዱት ናቸው ። ውጫቸው ሃይማኖታዊ መሳይ ውስጣቸው ግን በፍላጎት የሸፈተ ነው ። ይህን አይቶ የሚወቅሳቸው ቢመጣ “ሃይማኖት ውስጥ ያለው ፖለቲካ ያልገባው ነው” ብለው ያልፉታል እንጂ አይበሳጩም ። የልቡን የሚሠራ መቼ ይበሳጫል ! እግዚአብሔርን እወዳለሁ እያሉ ወንድምን መጥላት ቃየናዊ መሥዋዕት ፣ ያልተፈተነ ፍቅር ነው ።
የቲያትር ኑሮ በመልአክ ዕድሜ የነበረ ነው ። የመድረክ ተውኔት የተከበረ ሥራ ሊሆን ይችላል ። የምንናገረው በሕይወቱ ስለሚተዉን ወገን ነው ። ሰይጣን የብርሃን ገፀ ባሕርይን በጣም ይወዳል ። ጨለማ መሆኑ ስለሚያሳስበው ተሽቀዳድሞ ብርሃናዊ ለመምሰል ይፈልጋል ። ልብ አድርጉ ሰይጣን በራሱ ስም መጥቶ አያውቅም ፣ በእግዚአብሔር ስም ይመጣል ። ሰይጣን ብርሃን ይመስላል እንጂ ብርሃን መሆን አይፈልግም ። ይህም ድንቅ አይደለም ፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና ።” 2ቆሮ. 11፡14 ። አንዳንድ ውሸት ባለቤቱን ሳይቀር ያሳስታል ። ውሸታሞች የሚያለቅሱት ውሸቱ ለራሳቸው እውነት ስለሚመስላቸው ነው ። የውሸት ችግሩ ሰውዬውን ራሱን ማታለሉ ነው ። ሰው አታልላለሁ ብሎ የተነሣው ሰውዬ ተታሎ ያለቅሳል ፣ አታልላቸዋለሁ ያሉት ይነቁበታል ። ለጊዜው ያጭበረብራል ። ሰይጣን የብርሃን መልአክ እስኪመስል የብርሃን ልብስ ይለብሳል ። ተዋናዩ ከመድረክ ሲወርድ የሚቸኩለው ልብሱን ለማውለቅ ነው ። የድራማ ኑሮ ያደክማልና ። አጥንቶ መስበክ ፣ አጥንቶ ማፍቀር ፣ አጥንቶ ደግ ፣ ደግ ማውራት ይደክማል ። እውነት ሳይጠና ይፈስሳል ።
ጌታችን የገሠጸው በተውኔት ኑሮአቸው ፣ በግብዝነት አቋማቸው ትልቅ ደረጃ ላይ የወጡትን ፣ የሃይማኖታዊ ተውኔት ራስ የሆኑትን ጻፎችና ፈሪሳውያንን ነው ። እነዚህን ወገኖች፡- “እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን ፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ ፥ ወዮላችሁ” አላቸው ።
ሞታችኋል እያላቸው አይደለም ያለው ። ከሞት አልፋችኋል እያላቸው ነው ። በሁለት ዓይነት የሞት መደብ ውስጥ ያሉ ሰዎች አሉ ማለት ነው ። የመጀመሪያው በቁማቸው ሞተው የሚንቀሳቀሱ ናቸው ፣ ሁለተኛዎቹ ደግሞ ሞትን ጌጥ አድርገው የሚኖሩ ናቸው ። ፈሪሳውያን በሁለተኛው ምድብ ላይ ነበሩ ። እንዲህ ያሉ ሰዎች ውሸታቸው እግዚአብሔርንም የሚያታልል እየመሰላቸው ይታለላሉ ።
ሰውየው ወደ ጦር ሜዳ ዘምተው ሲመለሱ ትጥቃቸውን ሁሉ አስረክበው ነበር ። ሚስታቸው፡- “ጋሻው የታለ ?” ሲሏቸው “አስረክቤዋለሁ” አሉ ። “ጦሩስ የት አለ ?” ሲሏቸው “አስረክቤዋለሁ” አሉ ። “ጠመንጃውስ የት አለ ?” ሲሏቸው “አስረክቤዋለሁ” አሉ ። ሚስትየው ባላቸውን ትኩር ብለው ሲያዩ ዝናር ወገባቸው ላይ አለ ። “ዝናሩስ እንዴት ተረፈ ?” ቢሏቸው “እስከዚህስ ሞቻለሁ መሰለሽ ?” ብለው መለሱ ይባላል ። ጋሻው ከተወሰደ ፣ ጦሩ ከተነጠቀ ፣ ጠመንጃው ከተገበረ ወዲያ ምን ቀረ ? ራስን ለማጽናናት ግን በዝናር መፎከር ከንቱ ነው ። ዝናሩ ያለ ጠመንጃው ከድንጋይ ጠጠር የማይሻል ፣ ከቀበቶም የማያልፍ ነው ። መከላከያ ጋሻው ተነጥቆ ፣ ማጥቂያ ጦሩ ተወስዶ ፣ ቆመው የሚልኩት ጠመንጃው ተወርሶ በዝናር መመካት አልሞት ባይ ተጋዳይነት ነው ። ከዝናሩ በቀር ምን የቀረን ነገር አለ ? የቀረን የፌስ ቡክ ፉከራ ፣ የቀረን በኢንተርኔት ጫካ ተደብቆ መለፍለፍ ነው ። ርኅራኄው ፣ ሰው ተቀባይነቱ ፣ ቸርነቱ ፣ የሰው ክብር ፣ የአገር ፍቅር ፣ የንጉሥ ክብር ፣ የሽማግሌ ምክር ፣ የአባት ምርቃት … ይህ ሁሉ ርቆናል ። የምንመካው ፣ አልሞትንም የምንለው መተኮሻ በሌለው ዝናር ነው ። ያለፉት አርባ ዓመታት የተደበቀው የአውሬ ጠባያችን ገሀድ የወጣበት ነበር ። አባት ልጁን ፣ ልጅ አባቱን ያስገደለበት የጉድ ታሪካችን ነው ። ዛሬ ደግሞ የተደበቀው ብልግናችን ዘመን ባመጣው መገናኛ እየወጣ ያለበት ነው ። የቀረን ምንድነው ? አልሞትንም ብለን ለመናገር ያልደፈርነው የቱን ይዘን ነው ? መስቀልና ሽጉጥን ስንቀላቅል አልሞትንም ወይ ? የምድር ነገሥታትን የሃይማኖት አባቶች ሲማጸኑና መጠጊያ ሲያደርጉ አለን ወይ ? የቀረው ልብሳችን እንጂ ሁሉም ተማርኳል ። ያልሠራነው ምን አለ ? የድብቅ ኃጢአተኞች ፣ የግልጽ ጻድቃን ስለሆንን ተውኔቱን ስላስረዘምነው ብቻ ነው ። የሚያድነን መሞታችንን መቀበላችንና የትንሣኤውን ጌታ መማጸናችን ብቻ ነው ። ሳንድንበት መድኃኔዓለም አዳነን እንላለን ፣ ሳንገዛለት ኢየሱስ ጌታ ነው እንላለን ። ስንት ጣዖት በልባችን አዝለን አንድ አምላክ እያልን እንፎክራለን ። ሰውዬው እንዳሉት “አልሞትንም ብለን አንዋሽም ።”
ምንም ባንቀበር ባንገባ መሬት ፣
አያሳፍረንም ሞተናል ማለት ፤
የሞተና ሞቱን ጌጥ ያደረገ ሁለት ዓይነት ሟቾች አሉ ብለናል ። ስለ ሞተ ሰው እስቲ እንናገር ። የሞተ ሰው አለ ግን የለም ። መሞት ማለት እያሉ አለመኖር እንጂ እየሌሉ አለመኖር አይደለም ። ኖሮ መሞት ጸጋ ነው ፣ ሞቶ መኖር ግን ዕዳ ነው ። የሞተ ሰው አሳቡን በሰው ስለጣለ ያለ ልክ የሚከብድ ነው ። አገርን ለመሪው ብቻ ሰጥቶ ፣ ቤተ ክርስቲያንን ለአገልጋይ ብቻ ሰጥቶ መኖር ከዚህ በላይ መሞት የለም ። የማይሠሩ እጆች ይዘን የሚሠሩ እጆችን መንቀፍ ይህ ሞት ነው ። ሌላው ከሚገርፍህ እኔ ብገሸልጥህ ይሻላል ብሎ ጭካኔውን ቂቤ ማስመስል ይህ ሞት ነው ። ስለ ተቆረጠ ጽረዳ እያለቀሱ ስለሚቆረጡ ወጣቶች አለማዘን ይህ ሞት ነው ። የሞተ ያስጨንቃል ። እስኪቀበርም ማንም እህል አይቀምስም ። ማሳረፍ እንጂ ማስጨነቅማ የሬሳ ዋነኛው ሥራ ነው ። ሌላውን ማወክ ፣ ማስለቀስ ፣ በሰው ውድቀት ባለቅኔ መሆን የሞት ባሕርይው ነው ። የሞተ ሰው ብዙ ሰው ቢሸከመውም አይነሣም ። ራሱን የገደለ አገርና ትውልድም የትኛውም እርዳታ ቆሞ እንዲሄድ አያደርገውም ። ምንድነው የቀረን ? ልብሱ የሰው ፣ ግብሩ የአራዊት አይደለም ወይ ? ፍትወት ያልሰለጠነበት ፣ ጭካኔ ጉዳይ አስፈጻሚ ያላደረገው ማን ነው ? በልቼ ልሙት የማይል ፣ ሆዱን ያሸነፈ እስቲ ይናገር ? ሁላችንም ሞተናል ። በፍቅር ተጋብተን በዘር ስንፋታ ፣ ሰማይን እያየን በምድር ስንራኮት ፣ የፖለቲካና የሃይማኖት ድንበሩ ሲጠፋን የቀረው ዝናሩ ብቻ ነው ። አዎ መተኮሻ የሌለበት ፣ ለፉከራ ግን የሚሆን ዝናር ብቻ ቀርቶናል ። አልሞትንም ብለን አንዋሽም ።
ፈሪሳውያን ግን ሐውልት የተሠራለትና የሚጎበኝ የመቃብር ሥፍራ ሁነው ነበር ። ይህኛው ያደገ ሟች ነው ። እርሱ ፈርሶ ቤቱ የታነፀ ፣ ውስጡ ሸትቶ ላዩ የተዋበ ፣ የራሱን ዓለም ሲቀጭ ኑሮ “ሩጫውን ጨርሻለሁ ፣ መልካሙንም የሃይማኖት ገደል ተጋድያለሁ” ብሎ ላዩ ላይ የሚያጽፍ ኩሩ ሟች ነው ። ስለ ቅናትና ስለ ምቀኝነት ሲጋደሉ ኑረው ስለ ሃይማኖት ነው የተፋጀነው የሚሉ ተናጋሪ ሙታን በዓለም እየበዙ ነው ። ሳይታደሱ ሃይማኖትን እናድሳለን  ብለን የተነሡ ፣ የኪራይ ተሳዳቢ ሁነው ቤተ ክርስቲያንን የሚያቃልሉ አያሌ ናቸው ። ሰው ጠፍቷል እያሉ የሚያለቅሱ ራሳቸው ግን እንደ አዳም በገነት የጠፉ ፣ በቤቱ የሸፈቱ ብዙ ናቸው ። አልሞትንም ብለን አንዋሽም ። ቃየንን ያልሰደበ ሰባኪ ማን ነው ? ቃየንስ አንድ ጊዜ የገደለ ነው ፣ እኛ ግን ደጋግመን ወንድሞቻችንን የገደልን ነን ። የቀረው ዝናሩ የቀረው ፉከራ ነው ። ይሁዳን ያልረገመ ማን አለ ? ይሁዳ ያልሆንን እነማን ነን ? እኛ ዝም ብለን እግዚአብሔር ቢናገር ለዘላለም ዝም እንል ነበርን ። ሰባራ በሰንጣራ ይስቃል እንዲሉ የራሳችንን አስቀምጠን በሰዎች የምንስቅ ፣ እንኳን እንደ እገሌ አላደረገኝ እያልን የግብዝ ስብሐት የምንቀርብ ሞኞች ነን ። ቀሚሱና ካባው ለሰው ነው ። አጥርና ቤቱም ለፍጡር ነው ። እርሱ ግን ሳያስፈቅደንና ሳይገልጠን ያየናል ። እርሱ ችሎን ነበር እኛ አልቻል አልን እንጂ ። አዎ ሞተናል ትንሣኤ ያስፈልገናል ። በቂም ፈራርሰናል ፣ በበቀል ተንኮታኩተናል ። የሸኘነው ጋሻ ወንድማችንን ፣ ያስረከብነውን ጦር ታሪካችንን ፣ ያስወረስነውን ጠመንጃ ደግነታችንን እንደገና ገንዘብ ማድረግ ይገባናል ። ከገጣሚው ጋር እንዲህ እንላለን፡-
ምንም ባንቀበር ባንገባ መሬት ፣
አያሳፍረንም ሞተናል ማለት ፤
በዙፋንህ ያለኸው ፣ በባሕርይ ምስጉን የሆንከው ፣ ዛሬም በዓይነ ምሕረት የምታየን ቸሩ ጌታ እናመሰግንሃለን ። መጠላለፍ አልደክም ፣ መገዳደል አልበቃ ፣ መሰዳደብ አልሰለች ያለንን ልጆችህን እባክህን ወደ እውቀትና አንተን ወደ መፍራት መልሰን ። አፍ ተከፍቶ ፣ ጆሮ የተደፈነበትን የእኛን ዓለም ይቅር በለው ። ስለበደልናቸውና ስለገፋናቸው ወገኖቻችን ይቅር በለን ። በረከታችንን ያነቀብንን ስህተት ሁሉ በመሐሪነትህ ደምስስልን ። የጉብኝትህ ቀን ይድረሰን ። እኔን ባሪያህንና ወገኖቼን ይቅር በለን ። ተራው ይድረሰንና በመባረክህ ባርከን ። በታላቁ ፍቅርህ ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 28
ግንቦት 28 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም