የትምህርቱ ርዕስ | ወዳጄ ሆይ

ወዳጄ ሆይ
መሥራት ቢያቅትህ የሚሠሩትን አትበጥብጥ ። ማፍቀር ቢያቅትህ የሚያፈቅሩህን አትናቅ ። ማመን ቢያቅትህ የሚያምኑትን አትስደብ ። መኖር ቢያቅትህ መልካሙን የመረጡትን አትንቀፍ ። ማግባት ቢያቅትህ ያገቡትን አትተች ። መመንኮስ ቢያቅትህ የመነኮሱትን አታውግዝ ። መጻፍ ቢያቅትህ የሚጽፉትን አታቃልል ። የማይሠራ የሚሠራን ፣ ያልተማረ የተማረን ፣ ያላመነ የሚያምንን ፣ የማይጽፍ እጅ የሚጽፍ እጅን እንዴት ይተቻል ?
ወዳጄ ሆይ
የምትሰማውን ደግና ክፉ ውስጥህ ለመሆን ሲፈልግ በጸሎት አርቀው ። አደርግልሃለሁ ያለህ ባያደርግልህ ምናልባት አልቻለምና ስለ አሳቡ አመስግነው ። በበላይህ የነበረ የበታችህ ሲሆን ላንተ ማስተማሪያ ነውና በትሕትና እንደ ቀድሞው አገልግለው ። መሆን መሞከርን ደግሞም ማስመሰልን የሚያርቅ ቀላል የኑሮ ዘዴ ነው ። በነጻ ማፍቀር ካልቻልህ ጥቅመኛ ነህ ማለት ነው ። ቀን ሁልጊዜ ቀን አይሆንምና ለሌሊቱም ክፍለ ጊዜ ተዘጋጅ ። በብርሃን ለጨለማ ፣ በጨለማም ለብርሃን ተሰናዳ ፤ ሁሉም ነገር ይለወጣልና ። ሰዎች ሁሉ ይወዱኛል ከማለት እወዳቸዋለሁ ማለት የተሻለ ነው ። አድርገህላቸው የሚጎዱህ ፣ አጉርሰሃቸው የሚነክሱህ ከመጡ እግዚአብሔር ዋጋህን ሊከፍል ነውና ደስ ይበልህ ።
ወዳጄ ሆይ
ልብህ እየሸፈተ ከጸሎት መስክ ሲወጣብህ ጸሎትህን በዜማ አድርገው ። ሥጋህ መረን ወጥቶ እንዳይገለብጥህ ኑሮህን መጠነኛ አድርገው ። ጾም የትሕትና መሠረት ፣ የእንባም እናት ናትና ውደዳት ። እውነተኛ ኀዘን ጥቁር ልብስ መልበስ ሳይሆን ለቀረው ወገንህ መልካም ማድረግ ነው ። ወታደርም ልብሱን ሲያወልቅ እንደ አንተው ዜጋ ነውና አትፍራው ። ብዙ ሁነህ ስትሰበሰብ የእኔ ፍላጎት ብቻ ካልሆነ አትበል ። ፍላጎቱን ያልገደለ ኅብረትን ያፈርሳል ። በልጅህ ፊት ሚስትህን አትንቀፍ ። በሠራተኞችህ ፊትም ወዳጅህን አትገሥጽ ። ሚስትህን ለመምታት እጅህ ሲፈተን እየሳትህ ነውና የሥነ ልቡና አማካሪዎችን ፈጥነህ አግኝ ። አደርጋለሁ ብለህ ቃል የገባኸውን አድርግ ። ቃል እግዚአብሔር ወልድ የሚጠራበት የኩነት ስሙ ነውና ቃል ከባድ ነው ። ካልተቸገርህ በቀር የስለላ ሠራተኛ አትሁን ። አገርህን ለመጠበቅ ግን ራስህን እንደ ዘብ ቊጠር ።
ወዳጄ ሆይ
ክፉ አሳብ ሲዋጋህ ያንን ለመርሳት አትታገል ፤ አሳብ የሚሸነፈው በአሳብ ነውና ስለ እግዚአብሔር ማሰብ ጀምር ፤ መጻሕፍትንም አንብብ ። ያዘዝከውን ሰዎች ባይፈጽሙ አቅም አንሷቸው ሊሆን ይችላልና ራስህ ፈጽመው ወይም ለሚሠራ ለሌላ ሰው ስጠው ። መንደሮች የሚያስቡት በመንደራቸው መጠን ነውና ከመንደር ይልቅ ልብህን አስፋው ። አቅምህ እንጂ እምነትህ አናሳ አይሁን ። ኑሮህ እንጂ ፍቅርህ ድሀ አይሁን ። በእጅህ የወደቀ ምርኮኛህ ነውና አቅም አለኝ ብለህ ምንም አታድርግበት ። ተቀምጠህ የምታየውና ቆመህ የምታየው ልዩነት አለው ። ስትቀመጥ ትልቅ የመሰለህ ስትነሣ ትንሽ ነው ። አንድ እርምጃ መራመድም ወደ ግቡ መቃረብ ነው ። እውነተኛ አጥር የሰው ፍቅር ነውና ከአጥር ይልቅ ፍቅርን ገንባ ።
ወዳጄ ሆይ
በዙሪያህ ስላሉት አታስብ ፣ በልብህ ያለውን እምነት ግን አሳድግ ። የምትወድቀው ዙሪያው ደግፎህ ልብህ ሲከዳህ ነው ። ልብህ ከልቡ ጋር ሳይሆን ልብህ ከእግዚአብሔር ጋር ይምከር ። ስምህን ጠርተው ሰላም የሚሉህን ስማቸውን ጠርተህ ሰላም በል ። ከሰዎች ጋር እውነተኛ ግንኙነት ለማድረግ ስማቸውን ከመያዝ የበለጠ መነሻ የለም ። የፈለግኸውን ሳይሆን የሚያስፈልግህን እንዲሰጥህ እግዚአብሔርን ለመን ። እርሱ ሰጥቶ የማይሰለች አምላክ ነው ። ነፋስን ከናቅኸው ዐውሎ ነፋስ ሁኖ ይመጣል ፣ አስቸጋሪ ሰውን በጊዜ ካልገደብከው ፈቃድ ያለው ይመስለዋል ። አለቃ ለመሆን ስታስብ በጨለማ ወጥተህ በጨለማ ለመግባት መወሰን አለብህ ። ከሠራተኛው በፊት የማይገባ ፣ ከሠራተኛው በኋላ የማይወጣ አለቃነት አይኖርም ። ታዝዞ እንደ መኖር ያለ በረከት የለም ።
በብርሃን ዋል !!!
ምክር 17
ዲአመ ሚያዝያ 14 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም