መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እውነትን በፍቅር እንያዝ

የትምህርቱ ርዕስ | እውነትን በፍቅር እንያዝ

October 9, 2021 by ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

እውነትን በፍቅር እንያዝ

“ነገር ግን እውነትን በፍቅር እየያዝን በነገር ሁሉ ወደ እርሱ ራስ ወደሚሆን ወደ ክርስቶስ እንደግ፤” ኤፌ. 4፡15።

“ስትጣሉ ለእርቅ ፣ ስትበሉ ለውኃ ቦታ ትታችሁ” ይባላል ። እስከ መጨረሻው መነጋገር ፣ እንዳይድን አድርጎ ማቍሰል ፣ እንዳይነሣ አድርጎ መግደል ዘመን የወለደው የእልህ ጠባያችን ሆኗል ። አሳብን ስላላዳበርን ፣ አሳብን ለማዳበር የሚረዱ መጻሕፍትን እንደ ደመኞቻችን ስለቆጠርን ፣ ሊያስተምሩ የሚችሉ መምህራንን ስም ሰጥተን ስላባረርን ጠብና ጦር ሥራችን ሆኗል ። አሳብና አሳብ ቢፋጩ ትውልድ ብርሃን ያይ ፣ አገርም ያድግ ነበረ ። አገርም የግል ሳይሆን የጋራ መሆንዋ ይታመንና ሌላውም ይምራ ፣ ይናገር ተብሎ ይፈቀድለት ነበር ። አሳብ የሌለው ሰው ድንጋይ የድል መሣሪያው ነው ። በአሳብ ሁሉን ማትረፍ ሲቻል በድንጋይ ግን ደጉ አቤልን ማጣት ፣ ተቅበዝባዥ ቃየንን ማትረፍ ይመጣል ። መጻሕፍት የሚቃጠሉበት ዘመን አገርም ይቃጠላል ። መምህራን የሚናቁበት ዘመን ትውልድ ፍሬኑ የተበጠሰ መኪና ይሆናል ። አዋቂዎች ዱዳ ሲደረጉ ጮሌዎች በመሃይም ቃሌ እያሉ ብዙዎችን ከኋላቸው ያስከትታሉ ። ጋኖች ሲያልቁ ምንቸቶች ጋን ይሆናሉ ። አገር ሲያረጅ ጃርት እያበቀለ ይመጣል ። መናገር መቻል ቁምነገር ማውራት አይደለም ። መጻፍ መቻልም የእውነት ደራሲ አያሰኝም ። ብዙ ተከታይም ዝንጀሮ አመለካከታችንን አያቆነጅም ። እንደ ጦጣ ታስሮ መዝፈን ራስን ከማታለል ውጭ አይሆንም ። ጊዜ እስኪያገኝ ሁሉም ጨዋ ይመስላል ። “የእንጦጦ መምህር ቢናገር ባመት ፣ ያውም እሬት” እንዲሉ ከርመው መናገር የጀመሩ እሬታቸው አገርን እያንገሸገሸ መሆኑን ስናይ ያሳዝናል ።

“የማይደርሱበትን አያኩም” የሚባለው ተረስቶ ሊሰሙን የማይችሉትን ሰዎች ስንሳደብ መዋል ፣ የጻፍነውን መልሰን መልሰን ራሳችን ስናነበው ፣ የተናገርነውን መልሰን መልሰን ራሳችን ስንሰማው መዋላችን አስደናቂ ነው ። “ተንጋለው ቢተፉ ፣ መልሶ ባፉ” እንዲሉ ያስተማሩንን ፣ የክህነት አባቶቻችንን መስደብ ራስን ከማርከስ ውጭ ምንም ትርፍ የለውም ። ደግ መናገር ቢያቅተን ዝምታን ገንዘብ ብናደርግ መልካም ነበር ። ወደ ላይ እያዳጠን ብልሹ ወላጆቻችንን ደብቀን የመንፈስ አባቶቻችንን እያዋረድን መሆኑ ይገርማል ። የዕድሜም የእውቀትም ድኁር/ቅንጭር መሆናችንን ከማስገመት ውጭ ምንም ለውጥ አናመጣም ።

ምድራችንን እየጎዳት ያለው ሁሉን እናውቃለን የሚሉ ሰዎች መፈጠራቸው ፣ አለመናገር አለመኖር የሚመስላቸው ሰዎች መከሰታቸው ፣ ሁሉም ተንታኝ ሁኖ ባለሙያዎችን ማስደንገጣቸው ፣ ያወቁ ሰዎች ያላወቁ ሰዎች የማይሠሩትን ስህተት መፈጸማቸው ፣ ጆሮ ተቆርጦ መላ ሰውነት አፍ ብቻ መሆኑ ነው ። ቦታ ተለዋውጦ ምሁር መሃይም ፣ መሃይም ምሁር መባሉ ፣ ፖለቲከኛ ዕጣን ዕጣን ፣ ካህን ፖለቲካ ፖለቲካ መሽተቱ ፣ ወንበሮች ባዶ ሆነው ውሳኔ የሚሰጥ መታጣቱ ዘመኑን እያከፋው መሆኑ በግልጽ ይታያል ። አንድ ሰው መምራት ትቶ ሚሊየኖች መሪ ሲሆኑ አሟሟት እንኳ ክብር እያጣ ይመጣል ። ሰዎቹ የማይገቡ/የማይመጥኑ ሊሆኑ ይችሉ ይሆናል ፣ የያዙት ሥልጣን ግን ሐዋርያዊና ክርስቶሳዊ ነውና መንበርን መዳፈር ዋጋ ያስከፍላል ። የስድብ ዕድርተኞች መጨረሻ እርስ በርስ ይጠፋፋሉ ። ዛሬ እሰይ የእኔ ሽታ ፣ እሰይ የእኔ ሽታ እየተባባሉ በመጥፎ ጠረን ይወዳደራሉ ፣ በስድብ ቁመት ይለካካሉ ። ተቃቅፈው የሚሄዱ ሁለት ያልታጠቡ ሰዎች እሰይ የእኔ ሽታ እሰይ የእኔ ሽታ ይባባላሉ ይባላል ። አንዳችን ለአንዳችን ክፋት እውቅና የምንሰጠው እስከ ጊዜው ነው ። ክፉ ነገር ያልቃልና በቅርቡ እናፍራለን ። ትላንት ለውሸት ያጥኑ የነበሩ ዛሬ መግቢያ ሲያጡ ፣ ነግ ለእኔም ይህ መለኮታዊ ብይን ይሠራል ብለን መጠንቀቅ ይገባን ነበር ።

እውነት መነገር አለበት ። ሊነገር የሚገባው እውነት ምንድነው ? ማለት አለብን ። ሰይጣን እውነትን ሊናገር ይችላል ። ክርስቶስን ከአይሁድ ይልቅ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ያለው ሰይጣን ነው ። ምስክርነቱ ግን መገዛት የለበትምና እንደ እውነተኛ አይጠቀስም ። ሰይጣን ኃጢአት ስንሠራ ይህን ኃጢአት ሠርተሃል ይለናል ። ዓላማው ግን በክስ ተስፋ ማስቆረጥ በመሆኑ ከእውነት አይቆጠርም ። በዚህ ዓለም ላይ ያለው ትልቅ እውነት ፣ ሰው ሁሉ ሊቀበለው የሚገባው ክርስቶስ ስለ ኃጢአተኞች መሞቱ ነው ። “ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው ፤ ከኃጢአተኞችም ዋና እኔ ነኝ ፤” 1ጢሞ. 1፡15 ። ካም የአባቱን ሐፍረት ማየቱና መናገሩ እውነት ነበር ። ነገር ግን በልጅነቱ የእርሱን ዕራቁትነት የሰወረውን አባቱን ዛሬ ሊሰውረው ይገባ ነበር ። በዚህ ምክንያት ተረገመ ። ኖኅ ጠጥቶ መስከሩም ፣ መራቆቱም እውነት ነው ። ካም ግን ሐቀኛ አልተባለም ። የካም ጠባይ ዛሬም አልለቅቅ ብሎን የማጋለጥ እውነት እንጂ የመሰወር ጻድቅነት አልተገኘብንምና ወዮልን ። ዘፍ. 9 ፡ 22 ፤ ማቴ. 1 ፡ 19 ።

ሌሎችን ያዋረዱ ፣ መንፈሳዊ መምህራንን የነኩ ሁሉ በክብር አልኖሩም ፣ አልሞቱም ። የአንድ ሚኒስትር ውርደት እውነት ቢሆንም የመንግሥቱ ውርደት ነው ። የአንድ አገልጋይ ውርደትም የእግዚአብሔር መንግሥት የሚሰደብበት ፣ ሊድኑ ያላቸው ወደ ኋላ የሚጋልቡበት መሰናክል ነውና በልባችን ይዘን ፣ በአፋችን ልንጸልይበት ይገባል ። የማይጸልዩ አፎች ምልክታቸው መሳደብ ነው ። እውነትን በፍቅር መያዝ ይገባል ። ክፍሉን የምናነበረው እውነትን በፍቅር መናገር ብለን ነው ። ነገር ግን እውነትን በፍቅር ራሳችን መያዝ ይገባናል ። የሰውዬው ውድቀቱ እውነት ነው ። በፍቅር የምንይዘው ግን፡- “ጌታ ሆይ ከእኔ ይልቅ የሚሻለው ወንድሜ ወድቋልና የእኔን ፍጻሜ አሳምርልኝ” ብለን ነው ። ካወራወራችን ጋር ሳይሆን ካያያዛችን ጋር መታገል አለብን ። የምንወረውረው በያዝንበት መጠን ነውና ። ያለ ፍቅር መገሠጽም ፣ ማስተማርም ተገቢ አይደለም ። ፍቅር የሌለው ነገር ሕይወት የማይሰጥ ደረቅ ነውና ። ለአንድ ሰው አንድ እውነት ከመናገራችን በፊት እንደምንወደው እርግጠኛ መሆን አለብን ። ለማይወዱት ሰው ክርስቶስን መስበክ አምላክን እንደ መሳደብ ነው ።

እውነት ያለ ፍቅር ከተያዘች ኃጢአት በምድር ላይ እንዲጨምር ታደርጋለች ። ፍቅርም ያለ እውነት ከተያዘች ዘላኖችን ታፈራለች ። እውነት ያለ ፍቅር ብስጭት ናት ፣ ፍቅርም ያለ እውነት ግዴለሽ ናት ። እውነት ያለ ፍቅር ደረቅ ዱላ ነው ፣ ፍቅርም ያለ እውነት የማይቆም እንግጫ /ቄጠማ/ ነው ። እውነትን በፍቅር ስንይዝ ለማነጽ እንናገራለን ፣ ለማዳን እንሮጣለን ፣ ኅብረትን ለመመሥረት እንተጋለን ። “እንጨት ካልነሡት እሳት አይጠፋምና ከማጋጋል ማስታረቅ ፣ ከጠብ ቃላት የፍቅር ድምፆች ያስፈልጋሉ ። እውነትን ያለ ፍቅር መያዝ መራርነትን ፣ እውነትን ያለ ፍቅር መናገር ሰባሪነትን ፣ እውነትን ያለ ፍቅር መኖር ገዳይነትን ያመጣል ።

እውነትን ፍቅር እንያዝ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 29 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም