መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የኑፋቄ ማዕበል

የትምህርቱ ርዕስ | የኑፋቄ ማዕበል

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

የኑፋቄው ማዕበል

“እንደ ስሕተት ሽንገላ ባለ ተንኮል በሰዎችም ማታለል ምክንያት በትምህርት ነፋስ ሁሉ እየተፍገመገምን ወዲያና ወዲህም እየተንሳፈፍን ሕፃናት መሆን ወደ ፊት አይገባንም” ኤፌ. 4፡14 ።

ጊዜው ከሃያ ሦስት ዓመት በላይ ይሆነዋል ። አንድ ወጣትን አሁንም ድረስ አስታውሰዋለሁ ። ይህ ወጣት ልዩ የሚያደርገው የሄደበትን መዳረሻ ሁሉ ያሳውቀኝ ነበር ። ከማሳወቅ ውጭ ግን ምክር አይቀበልም ነበር ። በእርሱ አእምሮ ያለው ለመንፈሳዊ መምህር ያሉበትን ሁኔታ ማሳወቅ ይገባል የሚል መርህ ነው ። በደወለልኝ ጊዜ ሁሉ አንድ ቦታ ደግሞ ገብቷል ብዬ እገምታለሁ ፣ ተገናኝተንም ሪፖርት አዳምጬ እመለሳለሁ ። መልካም ምክር የምትጠቅመው ሲፈጽሟት ነው ። ይህ ወጣት ዲያቆን ሁኖ የሚቀድስ ነው ። በመቅደሱ አገልግሎት ያልተወሰነ ዐውደ ምሕረቱንም የሚወድድ ነበር ። ቴዎሎጂ መማር አለብኝ ብሎ ኮሌጅ ገባ ። ከወጣ በኋላ ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ጀመረ ። ነገር ግን አልተረጋጋም ነበር ። ራሱ ተቃዋሚ ራሱ መልስ ሰጪ ሆኖ ተሐድሶ ሆንኩኝ አለ ። በተሐድሶም ትኩስ አገልጋይ ሁኖ እንደ ሰነበተ ነገረኝ ። ከዚያም ወጣና ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ገባ ። ከፕሮቴስታንት እምነት ወጥቶ ወደ ይሖዋ ምስክሮች ገባ ። የሚገርመው ላለፈው ነገር ፍጹም ይቅርታ ለራሱ እየሰጠ ባለበት ቦታ ደስተኛነቱን ይገልጥልኛል ። እኔም ካላዳመጠ ብዬ መምከሬን አቁሜ ነበር ። ታዲያ ጂሖቫ ዊትነስ እንደ ገባ ሲነግረኝ፡- “ሌላ ጊዜ እንዳያምርህ ወደ ባሃኢ እምነት ለምን አትገባም?” አልኩት ። እርሱ ግን የሰጠኝ መልስ፡- “ወደዚያ ከምገባ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ብገባ ይሻለኛል” አለ ። እንዲህ ማለቱ የባሃኢ እምነት ይሁዲንም ፣ ቡድሃንም ፣ እስልምናንም ፣ ክርስትናንም ፣ ሳይንስንም ስለሚቀበል ነው ። ይህ ወጣት ከዚያ ጊዜ በኋላ አልተገናኘንም ። ቀጥለው ያሉት ሁለት ነገሮች ውስጥ እንደሚገባ እርግጠኛ ነኝ ። ክህደትና ዘረኝነት ውስጥ መግባቱ የማይቀር ነው ።

ሰይጣን ሰዎችን ከሚዋጋበት ከፍተኛ ውጊያ የመጀመሪያው፡- አማኞች ለመንፈሳዊ አባት ያሉበትን አድራሻ እንዲደብቁ በማድረግ ነው ። ልጆች ወላጆቻቸውን ሲደብቁ ከፍተኛ ችግር ውስጥ እንዳሉ የታወቀ ነው ። ለመንፈሳዊ አባቱም መደበቅ የጀመረ አማኝ ውድቀቱ ከፍ ያለ ነው ። ለመንፈሳዊ አባት ራሱን ሲገልጥና ሲያማክር ሦስት ነገሮች ያስፈልጉታል ። ምክር መስማት ፣ የጸሎት እርዳታ መጠየቅና ውሳኔ ግድ ይሉታል ። ሰይጣን ሰዎችን የሚዋጋባት ትልቁ ፈተና አቃቂር አውጪ በማድረግ ነው ። ሰው አቃቂር ማውጣት ከጀመረ ራሱን አያይም ፣ ጉድለትን ብቻ ስለሚፈልግም ቀና ዓይን አይኖረውም ። ፍጹምነት መፈለግ ዘዋሪ ፣ ቀማሽ ፣ ተቺ ያደርጋል ። ይህ ሰው ዓለሙ ሁሉ ጠፍቶ እኔ ብቻ ንጹሑ ቀረሁ ይላል ። እርካታ ማጣት አዳምን ከገነት ያወጣ ነው ። ብዙ የተፈቀደ ፍሬ እያለ የተከለከለ አንድ ነገርን በአጉሊ መነጽር አሳየው ። ብዙ ሰዎችን ሰይጣን ከኅብረትና ከቤተ ክርስቲያን የሚያወጣቸው አቃቂር እንዲያወጡ በማድረግ ነው ። ለእግዚአብሔር የቀኑለት ይመስላቸውና ራሳቸው ጠያቂ ራሳቸው መልስ ሰጪ ሁነው ይሄዳሉ ። በመሄዳቸው አገልግሎት የቆመና የተጎዳ ይመስላቸዋል ። በመጨረሻ የሚጎዱት ግን ራሳቸው ናቸው ። ሰይጣን የሚዋጋበት ሌላው ትልቅ ፈተና ተስፋ መቍረጥ ነው ። ሁሉንም አየሁት ፣ ደኅና ነገር የለም በማለት ወደ ክህደት ዓለም ይገባል ። የሃይማኖት ነገር ሲወራም ብስጩና ተበቃይ ይሆናል ። ይህ ሰው የሚደመድመው በሰይጣን የመጨረሻ ክፋት በዘረኝነት ላይ ነው ። ብዙ ዘረኞች በሃይማኖት የጀመሩ ፣ በጎሠኝነት የፈጸሙ ናቸው ።

ሐዋርያው እንደ ሕጻናት መሆን የለብንም የሚለው ሲነቀሉ ሲተከሉ መኖርን ነው ። በዚህ ክፍል ላይ የትምህርት ነፋስ ይለዋል ። የትምህርት ነፋስ የተባለው ኑፋቄ ወይም የስህተት ትምህርት ነው ። የስህተት ትምህርት የሚፈበረከው በቀጥታ ከሰይጣን ነው ። ሰይጣን የካደው በመታለል ሳይሆን በአእምሮ ነው ። እግዚአብሔር አዳምን የፈለገው በመታለል ስለወደቀ ነው ። ኑፋቄ በውስጡ ማታለል ያለበት ነው ። ኑፋቄ እግዚአብሔርን አይክድም ፣ እግዚአብሔርን ሌላ መልክ ይሰጠዋል እንጂ ። ኑፋቄ መጽሐፍ ቅዱስን አይጥልም ፣ ለግላዊ አሳብ ይጠቅሰዋል እንጂ ። ከሙሉ ውሸት ከፊል እውነት የሰይጣን ጉዳይ አስፈጻሚ ነው ። ሁላችንም በቂ የሆነ የሃይማኖት እውቀት ላይኖረን ይችላል ። ባለንበት ሃይማኖት በመጽናት ፣ ከመምህራን በትዕግሥት በመማር ወደ ሃይማኖት መረዳት እንደርሳለን ።

ነፋስ የሚግለበለብ ነው ፣ ኑፋቄም መዋከብ ያለበት ነው ። ነፋስ ትልቁን ያቀላል ፣ ኑፋቄ ውስጥም ክብር የለም ። ሽበትም ፣ ቅድስናም ፣ ሽማግሌም አባቶችም አይከበሩም ። የልጆች ዕድር ነው ። እርስ በርስ በመሆኑ የተሻለ እውቀትና መረዳት ያለው ስለማይገኝ መናናቅ ያለበት ነው ። በኑፋቄ የተያዙ ሰዎች የሚጠሉት ተቋም ካልፈጠሩ ህልውናቸው አደጋ ውስጥ ይገባል ። ያኛው ትክክል አይደለም በማለት የራሳቸውን ትክክለኛነት ለማስረዳት ይሞክራሉ ። በኑፋቄ ውስጥ ያለ ሰው ጤናማ ትምህርት ፣ አዎንታዊ ስብከት አይወድም ። አብዛኛው መጽሐፍ ቅዱስን ይዣለሁ የሚለው ወጣት እንደ አውቶብስ መጠበቂያ ጎሣውን እየጠበቀ ያለ ነው ። ብዙዎቹ የጎሣቸው አውቶብስ ስለመጣ ተሳፍረው ሄደዋል ። ከማያልቀ ርእስ ወደሚያልቅ ርእስ ገብተዋል ። እኛንም ይጠብቀን ።

ነፋስ ጣራን ይነቅላል ፣ የትምህርት ማዕበልም የመጨረሻውን ሕይወት ያበላሻል ። ነፋስ ካባን ነጥቄ ካልሄድሁ ይላል ። ኑፋቄም መከበርም ማክበርም አይፈልግም ። ነፋስ ይነጥቃል ፣ የትምህርት ነፋስም ብዙ ሞኞችንና ሕጻናተ አእምሮን ይወስዳል ። የሚባንኑት ሁሉንም ነገር ካጡ በኋላ ነው ። ኑፋቄ ውስጥ የተሳሳተ ትምህርት ስላለ የተሳሳተ ኑሮ አለ ። ሽንገላም ድሩን ያደራው በኑፋቄ ስፍራ ነው ። ወንድሜ ፣ እኅቴ መባባል አለ ፣ ፍቅር ግን የለም ። ተካስሰው ፍርድ ቤት ደጃፍ ላይ ሲደርሱ ዳኛው እስኪገባ እየተመራረቁ ይቆያሉ ። አብዛኛው የመናፍቃን ጎራ ከስለላ ተቋማት ጋር ግንኙነት ያለው ነው ። ከሀብትና ከዝና ውጭ መንግሥተ ሰማያት ጉዳያቸው አይደለም ። የአፍ ጮማ እንጂ ለተራበ የሚሆን ቁራሽ ለመስጠት ይፈተናሉ ። ያደጉባትንና እንጀራ የበሉባትን ቤተ ክርስቲያን ሲሳደቡ መጠን የላቸውም ። ሄደውም ካልረሱአት አላረፉም ማለት ነው ። መሳደብ የመናደድና ያለማረፍ ምልክት ነው ። ሐዋርያው ተንኮልም አለ ይላል ። እርስ በርስ በሴራ ሲጠላለፉ መኖር የኑፋቄው ዓለም መገለጫ ነው ። ሥራ ከሌለ ሴራ ሥራ ይሆናል ። ማታለልም እንዳለ ሐዋርያው ይናገራል ። በሐሰተኛ ፈውስና ትንቢት ሕዝቡን አስፈቅደው ይዘርፉታል ። ወዶ ተድፍቷልና ቢረግጡት አይከፋውም ። የዚህ ሁሉ ምንጩ የትምህርት ነፋስ ነው ። ድንገት የሚመጣ ፣ ጠራርጎ የሚወስድ የትምህርት ነፋስ አለ ። መምህራን በሌሉበት የሚደረጉ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች ሁሉም የመሰለውን ትርጉም ስለሚሰጥበት መጨረሻ ላይ አዲስ ኑፋቄ ይወለድበታል ። ኑፋቄ የቤተ ክርስቲያንን ብቻ ሳይሆን የአገርን አንድነትም አደጋ ላይ ይጥላል ።

ወጣቶች ረጋ በሉ ። ለማመኑም ለመካዱም አትቸኩሉ ። በትንሽ እውቀት ብዙ ስህተት እንደምትሠሩ እወቁ ። ለመማርና ለመመከር ፈቃደኛ ሁኑ ። በወጣትነታችሁ ያበላሻችሁትን እስከ ዕድሜ ልካችሁ ላታስተካክሉት ትችላላችሁ ። ነፋስ ይወስዳል ግን ወደ ትክክለኛ ግብ አይደለም ፣ ኑፋቄም ግብ የሌለው ጉዞ ነው ። ሰይጣን በሃይማኖት ጥሎ በምግባር ሊያቆነጅ ይችላልና አስተውሉ ።

እግዚአብሔር ሆይ ፣ እኛም ቆመናል ብለን አንመካም ። እስከ መጨረሻ ድረስ አንተን በማመን አጽናን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 25 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም