መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » አጋጣሚው አይለፈን

የትምህርቱ ርዕስ | አጋጣሚው አይለፈን

October 1, 2021 by ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

አጋጣሚው አይለፈን

“ክርስቶስን ለመምሰል ያገኛችሁትን አጋጣሚዎች ሁሉ አታሳልፉት ፣ ተጠቀሙበት ።” /እማሆይ ትሬዛ/

የሰው ልጆች ፣ ማኅበራዊ ሕይወት ፣ ምድራዊ ቆይታ ፣ ጸጋ እነዚህ ሁሉ የእገዚአብሔርን ትእዛዝ ተግባዊ የምናደርግባቸው ስለሆኑ ደስ ሊያሰኙን ይገባል ። ከዐሠርቱ ትእዛዛት ግማሹ ከሰው ልጆች ጋር ያለንን ግንኙነት የሚመለከቱ ናቸው ። ሰዎች ጋር መኖራችን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ተግባራዊ ለማድረግ አስፈላጊያችን ነው ። ማኅበራዊ ሕይወትም የመስጠትና የመቀበል ሂደት ነው ። ሕይወት የግል ተጠያቂነት ፣ የጋራ ተጠቃሚነት ያለባት ስሪት ናት ። ሰው በተፈጥሮው ማኅበራዊ ነው ። ከሌላው የሚሻው ፣ ለሌላውም የሚቸረው ሁኖ የተፈጠረ ነው ። በዚህ ዓለም ላይም ከሚያስደስቱ ነገሮች ዋነኛው ማኅበራዊ ሕይወት ነው ። የገለልተኝነት ሕይወት ፣ የግለኝነት ኑሮ ፣ የራስ ወዳድነት ዘይቤ ለጊዜው ስልጣኔ ይመስላል ። ቆይቶ ግን ሰው ራሱን በራሱ እንዲጎዳ የሚያደርግ ክፉ ዝንባሌ ነው ። ሰይጣን የሚያገኘን ብቻችንን ስንሆን ነው ። ሔዋን ብቻዋን በመሆንዋ ለራስዋና ለዘርዋ የሞት ምክንያት ሆነች ።

ምድራዊ ቆይታም እጅግ ደስ የሚል ነው ። ዕድሜ ተከርክሞ ከዘጠኝ መቶ ዓመት ወደ ሰማንያ ዓመት ወርዷል ። በትክክል ካሰብነው ሰማንያ ዓመት ሰማንያ ቀን ማለት ነው ። የተሰጠንን ሥራ ለመፈጸም በጣም አጭር ነው ። ቀጥሎ ምን እንደምንሆን አናውቅምና ሕይወት በጣም አጭር ናት ። ሰው ትላንቱ እርግጥ ፣ አሁኑ እውነት ሲሆን ኋላው ግን አጠራጣሪ ነው ። የአሁን ሰው ፣ የኋላ ሬሳ ነን ። ምድራዊ ቆይታን አስደሳች የሚያደርገው ዘላለማዊ ውሳኔ የምናደርግበት ፣ በክርስቶስ አምነን በጎ የምንሠራበት ስለሆነ ነው ። ጸጋም አቅም ፣ መለኮታዊ እገዛ ነው ። ሰው ፈቃዱን ፣ እግዚአብሔር ኃይሉን ሲሰጥ በጎ መሥራት ይቻላል ። እግዚአብሔር እንደ ሮቦት ያለ ታዛዥ ሰውን አይፈልግም ። ሰው ወድዶና ፈቅዶ እንዲገዛለት ይሻል ።

ወደ መንፈሳዊ ዓለም ከመጣን በኋላ ለእግዚአብሔር ስለሰጠነውና ስለ እግዚአብሔር ብለን ስለተውነው ነገር ብዙ እንቆጥራለን ፣ እንቆጫለን ። እኛን በመጥራቱና በማጽደቁ ክርስቶስ ሳይጸጸት የእኛ መቆጨት ይገርማል ። “ልጅነቴን ለጌታ ሰጥቼ ፣ መማርና መሥራት ስችል አገልግሎት መርጬ” እንላለን ። እኔ ብለን ስንናገር እግዚአብሔርን እንደምናጣ አናስተውልም ። ለጌታ ብለን ከተውነው ጌታ ለደሙ ብሎ የተወልን ይበዛል ። እኛ የእርሱን ጊዜ ለእርሱ ሰጠን ካልን እርሱ ደግሞ የእርሱን ዘላለም ሰጠን ። አገልግለን ገንዘብ ፣ ሮጠን ሹመት ፣ ወድደን መወደድ ባለመቻላችን ወደ ኋላ ለማለት እንዳዳለን ። የእግዚአብሔርን ስም እየጠራን ከሰው ዋጋ እንፈልጋለን ። ስለዚህ የምንጠራው እግዚአብሔርን ፣ የምናምነው ሰውን ነው ። ጴጥሮስ በአፉ ክዶ በልቡ አመነ እንላለን ። እኛ ግን እንደ አርዮስ በአፍ አምነን ፣ በልብ እየካድን ይመስላል ።

ስለሰጠነው ሳይሆን ስለተቀበልነው ፣ ስለተውነው ሳይሆን ስለተተወልን ማሰቡ መልካም ነው ። ቤተ ክርስቲያን የሰማዕታትን መታሰቢያ እንድናከብር ያደረገችው እግዚአብሔርን ያገለገለ ሰው መታሰቢያው መጥፋት ስለሌለበት ፣ ዳግመኛም የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ስለሆነ ሲሆን ከዚያ ባሻገር እኔም ብጋደል ለትውልድ አርአያ እሆናለሁ የሚል ዕጩ ሰማዕትን ለማነሣሣት ፣ ደግሞም ክርስትና ዋጋ እንደሚያስከፍል ለመንገር ነው ። እያንዳንዱ ገጠመኝ ክርስቶስን የምንመስልበት መንፈሳዊ መድረክ ነው ። ከሌለን ሊኖረን ይገባል ። እውቀት ከሌለን መማር ፣ ገንዘብ ከሌለን መሥራት ይገባናል ። ካለን ግን እንደሌለን መኖር ያስፈልገናል ። አለኝ ከምንለው ነገር ይልቅ ያለን ክርስቶስ ነውና ። ራሳችንን ዝቅ አድርገን መኖር ፣ ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች የሚራራ ልብ መያዝ ክርስቶስን በዘመናችን የምሳይበት መድረክ ነው ። ስለጠፉት ወገኖች ከመፍረድ ማልቀስ ፣ ዳግም ገንዘብ እስክናደርጋቸው በክርስቶስ ፊት ማንባት ፣ የሰቀሉትን ይቅር ያለው ጌታ ተከታዮች መሆናችንን የሚያሳይ ነው ። ወንድማችን በመጥፋቱ እኛም ወንድም አጥተናልና ከስረናል ። የእርሱ መገኘት ከጠፋ ወርቅ መገኘት በላይ ነው ።

ብልጣብልጥነትን ክደን ፣ እንዴት ልብላ ? ሳይሆን እንዴት ላብላ ? በማለት ክርስቶስን በሰፈራችንና በአገራችን መጋበዝ ይቻላል ። ድሆች በመንገዳችን ሲገጥሙን ፣ ሰዎች በቍጣ ሲመልሱልን ፣ የጀመርነው ማለቅ ሲሳነው ፣ ቀና ተናግረን ክፉ ትርጉም ሲያዝብን ፣ ዓለም ሁሉ አድሞ ይሰቀል ሲለን ፣ አጠገባችን የነበሩ ርቀው ሲተኩሱብን ፣ ዳቦ ነው ያልነው ድንጋይ ሲሆን … ይህ ሁሉ ክርስቶስን ለመምሰል ልዩ አጋጣሚያችን ነውና አይለፈን ። እንጠቀምበት ። በሰማይ መንግሥቱን የሰጠን በምድር ግን ራሱን ሰጥቶናል ። ወደ ሰማይ ብንሄድም የምንቀበለው የሚያንሰውን ነው ። የመንገሥተ ሰማያት ጌታ በልባችን ለመኖር ይመጣል ። ቃሉን መፈጸምም የልባችንን ዙፋን ማደላደል ነው ።

ጠላቶቻችን የመጨረሻውን ጥላቻና ብቀላቸውን ሲያደርጉ ይቅርታ ማድረግ ፣ ኃጢአተኞች ተስፋ ቆርጠው ሲሰቃዩ ገነትን ማብሰር ፣ በሚጠሉን መካከል ለወዳጆቻችን ዋጋ መስጠት ፣ የሌሎችን ኃጢአት መሥራት ሳይሆን መሸከምና መሰወር ፣ በእግዚአብሔር ረክተን መኖር ፣ ሥራችንን ቶሎ መፈጸም ፣ የነፍሳችን አድራሻ እግዚአብሔር አብ መሆኑን አምነን ልበ ሙሉ መሆን ፣ ሞትን በዝማሬ መቀበል ይህ ሁሉ ክርስቶስን የምንመስልበት አጋጣሚ ነው ። ጌታ ሆይ አንተን ለመምሰል ኃይል ስጠን ።

የብርሃን ጠብታ 10

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 21 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም