መግቢያ » ትረካ » በርጠሜዎስ ነኝ » በርጠሜዎስ ነኝ /2/

የትምህርቱ ርዕስ | በርጠሜዎስ ነኝ /2/

ጌታዬ ሆይ ያንተ ብርሃን እስኪያስነሣኝ ድረስ ብዙ ዓይነት ሰጪዎችን አይቻለሁ ። ብዙ ዓይነት ስጦታዎችንና ብዙ ዓይነት ተቀባዮችን አውቃለሁ ። መስጠት ሱስ ስለሆነባቸው የሚሰጡ ሰዎችን አውቃለሁ ። የመስጠት ሱስ ስላለባቸው ያደርጉታል ፥ ሱስ ግን ልማድ እንጂ ፍቅር አይደለም ። እነዚህ ሰዎች የባለጠጋ ድሆችን ሲረዱ ይውላሉ ። ገንዘባቸውንም ያለውለታ ይጨርሳሉ ።  ደግሞም ለርኅራኄአቸው ዋጋ የሚከፍሉ ሰጪዎች አሉ ። ዝም ብለው ቢሄዱ ያዩት ጉዳትና ድህነት ቀኑን በሙሉ ሲረብሻቸው ይውላል ። ቀኑ ከሚበላሽባቸው ሳንቲም በመወርወር ያርፋሉ ። ምስኪኑን ሰው ስለወደዱ ሳይሆን ኅሊናቸውን ለማሳረፍ ይጥላሉ ። የተጨነቀው ኅሊናቸውም በሳንቲም ስጦታ ያርፋል ። እነዚህ ሰዎች ለራሳቸው ሰላም የሚመጸውቱ ናቸው ።
የወርቅ ስጦታየሚሰጡ አሉ ። እነርሱ ከፍቅር ጋር እንጀራን የሚቆርሱ ናቸው ። የመዳብ ስጦታ የሚሰጡ አሉ ። መስጠት እየቻሉ አይዞህ እያሉ የሚያጽናኑ ፥ እጸልያለሁ እያሉ የሚዘብቱ ናቸው ። የናስ ስጦታ የሚሰጡ አሉ ። ለታይታ የሚቸሩ ናቸው ። የብረት ስጦታ የሚሰጡ አሉ ። እነዚህ የሰጡትን የሚያወሩ ናቸው ። ስጦታቸውም እንደ ብረት ይከብዳል ። የእርሳስ /የጥይት/ ስጦታ የሚሰጡ አሉ ። እነዚህ አደንዛዥ ዕፅና መጠጥ የሚጋብዙ ናቸው ። ጌታዬ ሆይ ስንት ዓይነት ሰጪዎችን ስንት ዓይነት ስጦታዎችን አይቻለሁ ።
ብዙ ዓይነት ተቀባዮችም አሉ ። የራሳቸውን የግላቸው ፥ የሌላውን የጋራቸው እንደሆነ የሚያስቡ አሉ ። ደግሞም በሌላው እጅ ያለው ሁሉ የሚያምራቸው ፥ በይገባኛል የሚከጅሉ አያሌ ናቸው ። ያገኘ ሰው ሁሉ የሰረቀ ወይም ያስጠነቆለ የሚመስላቸው እግዚአብሔር እንደሚሰጥ የማያውቁ ብዙ ተቀባዮች አሉ ። ሌላው የሰጣቸው ስለፈራቸው የሚመስላቸውና ጨምር ለማለት ዓይናቸውን የሚያፈጡ አሉ ። ለመመረቅ የሚተናነቃቸው ሌሎች የመስጠት ግዴታ እንዳለባቸው የሚያስቡም አሉ ። ስጦታው የሚያሳቅቃቸው በተቀበሉ ቊጥር ወይ ዕድሌ እያሉ የሚያማርሩም አሉ ። እነዚህ ሁሉ ክፉ ተቀባዮች ናቸው ። መስጠት ተራ መሆኑን አይገነዘቡም ። የዛሬ ተቀባይ የነገ ሰጪ ፥ የዛሬ ሰጪም የነገ ተቀባይ መሆኑን አይረዱም ። ስለዚህ ለማመስገን ፍቅር ፥ ለመሻገር ትዕግሥት የላቸውም ።
 ጌታዬ ሆይ የድንጋዩ መቀመጫዬ ለእኔ ትልቅ ትምህርት ቤቴ ነው ። በዚያ መንገድ ብዙዎች በእግር ፥ ብዙዎች በሠረገላ አለፉ ። እነዚህ ሁሉ ችግሬን አተሙት እንጂ አላሳለፉትም ። አንተ ስታልፍ ግን ታሪኬ አለፈ ። የኢያሪኮ መንገድ ከነቢዩ ኤልሳዕ በኋላ ጭርታ እንደ ገጠመው ይሰማኛል ። ዛሬ ግን ደምቋል ። አጠገቤ የሚያልፉት ሰዎች ትላንት በድምፃቸው የማውቃቸው አይደሉም ። “እናንተ ሰዎች እባካችሁ ዛሬ ምን አለ ?” ስላቸው መቶዎች ድምፄን ለመስማትና መልስ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም ። የሚሰሙት የሚያስቡትን ነውና ገንዘብ የጠየቅኋቸው መስሏቸዋል ። ጌታዬ ሆይ ለድሃ የሚያስፈለገው ገንዘብ ብቻ ይመስላቸዋል ። አንተ ግን ከገንዘብ ሌላ የሰጠኸኝ ልዩ ወዳጄ ነህ ። ድሃ የሚመጣው ሁልጊዜ ገንዘብ ፍለጋ አይደለም ። የሚያወራኝ ናፍቆኝ ወደ አንዱ ቤት ስሄድ ሁሉም ሰው ኪሱን ይዳብሳል ። ሰጥቶ ያባርረኛል ። ቆርጠው ከወጡ ገንዘብ አይጠፋም ። ቆርጠው ቢወጡ ግን ፍቅር አይገኝም ። ፍቅር ዘር ነውና ስንዘራው ብቻ ይበቅላል ። ድሃ በዓለም ላይ ትልቁን ስጦታ ይሰጣል ። ራሱን ይሰጣል ። ግን ማንም አይቆጥርለትም ። ለሰዎች ትልቅ ነገራቸው ገንዘብ ነው ። አንተ በእኔ መንገድ የምታልፍ መሆንህን ያወቅሁት ኢየሱስ የሚለውን ስምህን ላይድኑበት ደጋግመው ሲጠሩት ነው ። ጆሮዬን ማመን ስላቃተው እንደ ገና “እናንተ በዚህ የሚያልፈው ማን ነው?” ስል አሥሩ አልፈውኝ አንዱ ፡- “የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው” አለኝ ። ሰው በተወለደበት እንጂ ባደገበት ለምን ይጠራል ? የቤተ ልሔሙ ኢየሱስ ለምን አላሉህም? እያልኩ አስባለሁ ። ለካ ናዝሬት የወንበዴዎች ከተማ ነበረች ። የኃጢአተኛ ወዳጅ መባልን ስለምትፈልግ ነው ። የምናደክምህ ጤና ያጣን ዕውሮች ፥ ገንዘብ ያጣን ድሆች ፥ ጽድቅ ያጣን ኃጢአተኞች ነን ። አንተ ግን እንደ ባለ ጉዳይ እንኳ አላየኸንም ። እንደ ልጅ ተቀበልከን ። እኔ አድናቂህ ሳይሆን ባለ ችግረኛህ መሆኔ ተሰማኝ ። እግዚአብሔርን ቀርቦ ሳለ ጥሩት ፥ በሚገኝበትም ጊዜ ፈልጉት የተባለውን አሰብኩ ። ዛሬ ለእኔ ቊርጥ ቀኔ ነው ።
መቼም ጌታዬ ረጅም ዘመን በብቸኝነት ስለኖርኩ ከሰው ጋር መጫወት አላውቅምና ሁሉንም ላውራህ ። እንዴት እኔ መሆኔን አወቅህ ? መሢሕ መሆኔን እንዴት ተረዳህ ? ብለህ ጠይቀኝ ። አዎ ጠይቀኝ ጌታዬ ። ልመልስልህ ፡- የሰዎች ውድቀት ፥ የመከራ ጽናት ፥ የበሽታ ቊጥር ፥ ልክ የለሽ ሀብትና ልክ የለሽ ድህነት ሲንሰራፋ መምጫህ እንደ ቀረበ አውቄ ነበር።
ሰውንም ስለምን አላፈርኩም ? መስጠት ከማይችለው ከሰው ስቀበልም አልተሰቀቅሁም ። ስለዚህ በልዑል ቃል ፡- “የዳዊት ልጅ ሆይ ማረኝ” ማለት ጀመርኩ ። ሊለመኑ የማይገባቸውን ሰዎች ስለምን ማንም አላስቆመኝም ። የሚለመነውን ሰጪ ጌታ ስለምን ግን ሁሉም ዝም በል አለኝ ። እኔ ችግሬ ከብዶኝ እጮኻለሁ ፥ እነርሱን ግን ጸሎቴ ከበዳቸው ። ባለጠጋ ቢጮህ አብረው ይጮኹለት ነበር ። እንደ እርሱም አይደለም። ዘኬዎስ እኮ ባለጠጋ ነበር ። እንዴት እቤቱ ገባህ ብለው ከስሰውሃል ። ሰው የሚወደው የመካከሉን ነው ።
ማርቆስ ድሮ ዮሐንስ ነበረ ስሙ ። የጴጥሮስ ደቀ መዝሙርም ነበር ። ታዲያ ወንጌሉን ለሮማውያን እየጻፈ መሆኑን ነገረኝ ። አሁን አሥረኛው ምዕራፍ ላይ ደርሻለሁና ከአርባ ስድስት ቊጥር ጀምሮ ልጽፍልህ እፈልጋለሁ አለኝ ። ተው ማርቆስ የሚጻፍ ታሪክ የለኝም ፤ ኑሮዬ የድህነት ፥ ዘመኔ የእውርነት ነው አልኩት ። ማርቆስ ትሑት ነውና ታሪክህ የታደሰ ልዩ ፍጥረት ነህ ። ስለዚህ በእግዚአብሔር መዝገብ ያደረከው ቢጠፋ የተደረገልህ ሲነገር ይኖራል አለኝ ። ያደረግኹት ባይኖርም ያደረገልኝ ግን ብዙ ነው ፥ እሺ ጻፈው አልኩት ። ወይ ጌታዬ ማዶ ገዳመ ቆሮንቶስ ይናገራል ፥ በስተቀኜ ማዶውን የኤልሳዕ ምንጭ ያወራል ። የእኔ ድንጋይም ለዘመናት ልትናገር ነው ? አልኩኝ ።
ጌታዬ ያንተን ላንተው ልናገር ። ያንተን ላንተ መስጠት መልካም ነው። “የዳዊት ልጅ ሆይ ማረኝ”  ብዬ ስጮህ ሰዎች ሁሉ ገሰጹኝ ። የሚገሰጽ ያጠፋ ነው ። የጸለየ እንዴት ይገሰጻል ? አልኩኝ ። ገና ስምህን ስጠራ ውጊያ ጀመረኝ ። አንተ ጌታዬ ውስጥህ ሰላም ፥ ዳርህ እሳት ነው ። ለነገሩ ውስጥ ሰላም ሲሆን ዳሩ እሳት ይሆናል ። ውስጡ እሳት ሲሆን ደግሞ ዳሩ ሰላም ይሆናል ። ለእኔ ግን አንተ ትሻለኛለህ ። ተወዳጅ ለማኝ ከመሆን የተጠላሁ ሠራተኛ መሆንን እፈልጋለሁ ። ተወዳጅ ዓይነ ሥውር ከመሆን የተጠላሁ ተመልካች መሆንን መርጫለሁ ። ቃልህ ፡- “ወዶኛልና አዳነኝ” ይላል ። የሚያድን ፍቅር ያንተ ብቻ ነው ። ሰው ቢወድ ፍቅሩ ከሞት አያድንም ። እኔም ቀኔ ዛሬ ነውና በተወደደ ቀን ጠራሁህ ፥ በመዳን ቀንም ረዳኸኝ ። ዝም በል ሲሉኝ እንደውም ባሰብኝ ። ውስጡ የሚጮህበት ቢጮህ አይጠግብም ። ሁሉም ምሕረትህን ለግል መጽናናት ብቻ ይፈልገዋል ። ምሕረትህ ለሰው ሁሉ መሆኑን ግን አይረዳም ። ለካ እንዳልድን የሚጠብቁኝ ፖሊሶች ፥ የእውርነቴ አድናቂዎች አሉ ። ለነገሩ ዓለም የምትወደኝ የእርሷን ካልነካሁ ነው ። በወንበር ካልተጋፋሁ ትወደኛለች ። ካልበላሁ የበቃ የነቃ ነው መናኝ ነው ትለኛለች ። ምሥጢሩ መብላት በልክ ክፉ ሆኖ አይደለም ፥ስላልነካሁባት ነው ። ዮሐንስ መጥምቅን ያከበረችው ምንም አይነካብኝም ብላ ስለተማመነች ነው ። ውሾች ድሃ ላይ የሚጮኹት ምግቤን የሚወስድ መጣ ብለው ነው ። የለበሰውንማ ውሾችም ያከብራሉ ።
እንዲያ ስጮህ አንተ ግን ቆምክልኝ ። በኢያሪኮ ከእኔና ከዘኬዎስ ሌላ የተጠቀመብህ የለምና ለካ የመጣኸው ለእኛ ነው ። እኛ በጸሎታችን የቆምክልን መሰለን ። አንተ ግን የቆምከው እኛ ጋ ስለመጣህ ነው ። አጃቢዎችህ ያላገኙትን የተጠላነው እኛ አገኘን ። ጌታዬ ሆይ ዘኬዎስን አግኝቼው አላውቅም ። ደህና ነው ? በምድርም በሰማይም ቢሆን አንተን ያገኝሃልና አንተን መጠየቄ ትክክል ነው ። አምጡት ስትል ጀማው ፀጥ አለ። ቅድም የገሰጹኝ አሁን አነሡኝ ። አንተ ድምፅህን ስታሰማ የገፋን ያቅፈናል።  እባክህ ድምፅህን አሰማ ። ዛሬም ብዙ ታሪክ ይለወጣል ። ሊለያዩ የተቃረቡ ባልና ሚስት ፍችው ሊቀደድ ሲል ኧረ አብረን እንኑር ይላሉ ። የድምፅህ መሰማት የሞት ሽታን ይለውጣል ። ኦ ጌታዬ ስንጸልይ አንተ ድምፅህን ታሰማለህ ። ለካ የችግራችን ምንጩ አለመጸለይ ነው ። ጌታዬ ሆይ ባንተ ታድሼ ፥ በድምፅህ በርትቼ እንጂ ዕድሜዬ እኮ ገፍቷል ። ያን ቀን ግን በደስታ ስዘል ድሪቶዬ ወለቀ ። ወደ አንተ እንደሚያይ ሰው በሩጫ ስመጣ ለካ የብርሃን ልብስ ይዘህ ትጠብቀኝ ነበር ። ነቢዩ ፡- ብርሃንን እንደ ልብስ የለበስህ ይልሃል ። አዳምና ሔዋንን ይህን የብርሃን ልብስ አልብሰሃቸው ነበር። እኔም ዛሬ ተራው ደረሰኝ ። ጨርሰህ ፥ ሁሉን አዘጋጅተህ ጠብቀኸኛል ። ንጉሥ ነህና አቤቱታዬንና ጥያቄዬን መስማት ይገባሃል ። “ምን ላደርግልህ ትወዳለህ ?” ስትለኝ ለካ የምንኖረው አድርጉ ያለንን ትእዛዝ ለመፈጸም ብቻ አይደለም ። የምንሻውንም ለማግኘት ነው አልኩኝ ። “መምህር ሆይ አይ ዘንድ” አልኩህ ። ቅድም የዳዊት ልጅ ያልኩህ ዘመዴ ስለሆንህ ነው ። ማረኝ ያልኩህ ምሕረት ገንዘብህ ስለሆነ ነው ። አሁን መምህር ሆይ ያልኩህ መምህር ከጨለማ የሚያወጣ ስለሆነ ነው ። ልቤንም ዓይኔንም ፈውስልኝ ለማለት ነው መምህር ሆይ አይ ዘንድ ያልኩህ ።
አንተም እምነትህ አድኖሃል አልከኝ ። ያዳነኝ ቸርነትህ ቢሆንም ለእምነቴ ዋጋ ሰጠህ ። አዎ ጥቂት እምነት በፊትህ ትልቅ ተራራ ያነሣል ። ያን ጊዜ ተከተልኩህ ። ቤት የለኝ ተመልሼ ልዝጋው አልልም ። ይህን ያህል ዘመን ሲሰጡኝ የነበሩትን ደጎችን ፥ ያዝኑልኝ የነበሩት እውነተኛ እስራኤላውያንን ዛሬ መልካቸውን አየሁ ። የሚያበላኝን አለማየት ፥ የሚወደኝን አለመመልከት ከብዶኝ እኖር ነበር ። ዛሬ ግን ከሰቀቀኔ አወጣኸኝ ። አዎ በርጠሜዎስ እኔ ነኝ ። እኔ ነኝ ያልኩት እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ ያለውን ጌታ አግኝቼ ነው ። በርጠሜዎስ እኔ ነኝ ፡-
ከድንጋይ ትራስ ዳቦ የተንተራስኩኝ ፥ ከመንገድ ጠባቂነት ጌታዬን የተከተልኩኝ ፥ ድምፄ ተለምዶ ጆሮ ያታከትኩኝ ፥ ሕጻን የማይቆምልኝ ዛሬ ግን ንጉሥ የቆመልኝ በርጠሜዎስ እኔ ነኝ ፤ በማታ የተሠረግሁኝ ፥ የሠርክ ሙሽራ የሆንኩኝ ። በቀድሞ አድራሻዬ የምትፈልጉኝ እንኳን አድራሻዬ ድሪቶዬም ተለውጦ ብርሃን ለብሻለሁ ። አለማየትን ዕውርነትን በነበር እተርካለሁ ። በርጠሜዎስ እኔ ነኝ ። ጌታዬ እንደገና የፈጠረኝ ። ምስጋና ያለባችሁ እንደ እኔ ያለይሉኝታ ጩኹ ፥ አመስግኑ ። ጌታዬ ሆይ ሰማይ ስሚ ምድር አድምጪ ብዬ ብናገርም ምስጋናህን ገና አልጠገብኩም ። ስምህ ቡሩክ ቅዱስ ይሁን ለዘላለሙ አሜን !!!
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም