መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » በጥቂቱ ዕድሜ

የትምህርቱ ርዕስ | በጥቂቱ ዕድሜ

 
“ማንም በዕድሜው ብዛት አያስጠራም ስሙን ፣
በጥቂቱም ዕድሜው ይሠራል ሐውልቱን ።”
 
               ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ
 
ዕድሜ ሲያንስም ያሳዝናል ፣ ሲበዛም ይታክታል ። በለጋነታቸው የተቆረጡትን ፣ ዕድሜአቸው በዝቶ የጃጁትን ስናስብ ነቢዩ ሙሴ፡- “የዘመኖቻችንም ዕድሜ ሰባ ዓመት ፥ ቢበረታም ሰማንያ ዓመት ነው ቢበዛ ግን ድካምና መከራ ነው” ያለውን እናስታውሳለን  ። መዝ. 89 ፡ 10 ። ከዚህ በፊት የማናውቀውን ዓለም በልደት አወቅነው ፣ ከዚህ በኋላ ላንመጣ በሞት ተሰናብተነው እንሄዳለን ። ሰባና ሰማንያ ዓመት ጥቂት ቢሆንም ሰውን ያደክመዋል ። ድካሙ ዕቃ ተሸክሞ ሳይሆን ራስን ፣ ፍላጎትን ፣ ሰውን ፣ ኑሮን ፣ አገርን ፣ ግዳጅን ተሸክሞ ነው ። ብዙ ዕድሜ ማግኘት ብዙ የመሥራት ዋስትና አይደለም ። ጥቂት ዕድሜም የሥራ እንቅፋት አይደለም ። ራስን ታሪክን ፣ አገርን ፣ ሕዝብን ለመለወጥ የሚያስፈልገው ትልቅ ዕድሜ ሳይሆን ትልቅ ልብ ነው ። አቤል ለእግዚአብሔር የተመረጠ መሥዋዕት ያቀረበው በወጣትነቱ ነው ። ቃየንም ገዳይ የሆነው በወጣትነቱ ነው ። መክሊት ለሁለት ሰዎች ቢሰጥ አንዱ ይመጸውትበታል ፣ ሌላው ግፍ ይሠራበታል ። መክሊቱ በራሱ ክፉና ደግ አይደለም ። ወጣትነትም እንደ መክሊት ነው ። ደግነትና ክፋት ግን ምርጫ ነው ። በሽምግልናው የሚያመነዝር አለና ወጣት ስለሆንሁ ፍላጎቴን መከልከል የለብኝም ማለት አይገባም ። ኃጢአትን የሚያስጥለን ዕድሜ ሳይሆን ፍቅረ እግዚአብሔር ነው ። ከሰው ልጆች የመጀመሪያው ሰማዕት ወጣቱ አቤል ነው ። በቤተ ክርስቲያን ጉዞም ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ ነው ። ዋናው ብዙ ዘመን መቆየታችን ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መኖራችን ነው ። ለአንዳንድ ሰው መኖር ያመነውን ለመካድ ሲሆንበት በሊቃነ ካህናቱ በሐናና በቀያፋ እናያለን ፣ መኖር በረከት ሲሆንም በፈያታዊ ዘየማን/በቀኙ ወንበዴ እናስተውላለን ። 
 
ስም ከመቃብር በላይ ይውላል ። ሰው ኖሮ ቢያደንቁት ብዙ ይሠራል ። አዝኖና ረግሞም አይሞትም ። ስሙ ቢጠራ የሚያምረው ግን ከሞት በኋላ ነው ። ሞት የዚህ ዓለም ኑሮ መጨረሻ ብቻ ሳይሆን ያ ሰው ከዚህ በኋላ የሠራውን ያበላሻል ተብሎ አይሰጋም ። የቆመ ሰው ግን የራሱን ሥራ ራሱ ሊያፈርሰው ይችላልና ኖሮ ያልጨረሰን ማመስገን ከባድ ነው ። በፍቅር ጀምረው በጥላቻ ፣ በሰላም ጀምረው በሁከት የሚፈጽሙ ፣ እንዳማረባቸው ማለፍ ያቃታቸው ብዙ ወገኖች አሉ ። ስም ማስጠሪያ የሚሆን በጎ ነገር ፣ ከራስ ተርፎ ለአገር የሚሆን ደግነት ያስፈልጋል ። አንድ ነገርን ለአገር ማበርከት አለብኝ ብለው ከልጅነት ጀምሮ የሚያስቡ ሕዝቦች የሥልጣኔ ማማ ላይ ወጥተዋል ። ሰው ያደረገውን የሚደግሙ ሳይሆኑ ያልተሠራውን የሚሠሩ ሕዝቦች አገራቸውን ከፍ አድርገዋል ። እኛ አዲስ ነገር ስለማይታየን ከምግብ ቤት አጠገብ ምግብ ቤት እንከፍታለን ። ሥራን መቀማማት እንጂ አዲስ ነገር አይታየንም ። 
 
ታምመን እንኳ የምንፈራው ሕመሙ የብቻችን ከሆነ ነው ። አገር ሁሉ ታሟል ስንባል እንበረታለን ። ሁሉ ከታመመ ግን አስታማሚ እንደሚጠፋ እንዘነጋለን ። ሁሉ አይቸገር የሚሰጥ እንዳይጠፋ ፣ ሁሉ አይከፋ የሚያጽናና እንዳይታጣ ። ተወለደ ሞተ የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ሰዎች በጣም ያሳዝናሉ ። በዚህ ዓለም እንደ ቋጥኝ ተቀምጦ ማለፍን መጸየፍ ያስፈልጋል ። ጨው ይዘን ምድር አልጫ መሆኑ ፣ ብርሃን ይዘን ዓለም ጨለማ መሆኑ በእግዚአብሔር ዘንድ ያስጠይቀናል ። ይህን ዓለም ውብ የሚያደርገው ዘላለማዊ ውሳኔ የምናደርግበት በመሆኑ ነው ። በሚያልፈው ዕድሜ የማያልፍ ሥራ መሥራት ይቻላል ። ለሚያልፍ ቀንም የማያልፍ ንግግር እንናገራለን ። አንድ ቀን በዚህ ዓለም ላይ ዋጋ አለው ። አንድ ቀን ተወልደናል ፣ አንድ ቀን እንሞታለንና አንድ ቀን ብዙ ነው ። ሥራቸውን የፈጸሙ ሰዎች መኖርን ስለሚረኩ ብዙ ዕድሜን አይለምኑም ። ሥራቸውን የጨረሱም ፣ ለተፈጠሩበት ነገር የኖሩ በዕድሜአቸው አያፍሩም ። እግዚአብሔር የሰጣቸውን ዕድሜ ቀንሰው አይናገሩም ። ኖሮ አልኖርኩም ከማለት በላይ ክህደት የለም ። 
 
ወጣት ነኝ እንጂ ብዙ መሥራት እፈልግ ነበር አይባልም ። ዕድሜ ገፋ እንጂ ልሠራው የምመኘው ነገር አለ አይባልም ። ባለን ጥቂት ዘመን ለዘመን የሚተርፍ ፣ ለትውልድ የሚፈስስ ነገር መሥራት ይቻላል ። ይህችን ጀንበር ከተጣላነው ታርቀን ፣ የቀማነውን መልሰን ፣ የበደልናቸውን ክሰን አዲስ ማድረግ እንችላለን ። በዚህች ቀን የአርባ ዓመት ቂምን መሻር የምንችል ከሆነ አንድ ቀን ብዙ ነው ። ልንሠራው ለምናስበው ዓላማ የሚረዱ ትምህርቶችን ፣ የአካል ብቃትን ፣ መካሪዎችን ፣ ኅብረቶችን ፣ በጸሎት የሚያግዙንን ዛሬ መፈለግ ይቻላል ። 
 
ብዙ ስለመኖር ሳይሆን ብዙ ስለመሥራት እናስብ ። ብዙ ባንኖር የእኛ ጉዳይ ሳይሆን የአምላክ ፈቃድ ነው ። ብዙ ባንሠራ ግን የእኛ ስንፍና ነው ። ባለጠጋው ቢልጌት፡- “ድሀ ሆነህ መወለድህ የአንተ ጥፋት አይደለም ፣ ድሀ ሆነህ መሞትህ ግን ያንተ ጥፋት ነው” ብሏል ። በጥቂትዋ ዕድሜአችን ብዙ መሥራት እንችላለን ። እስጢፋኖስ ሰማዕት በ17 ዓመቱ ስሙ ተጠራ ፣ ማቱሳላ 965 ዓመት ኖሮ ይህን ሠራ አልተባለን ። 
 
እግዚአብሔር ያግዘን ።
 
የብርሃን ጠብታ 2 
 
 
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
 
 ነሐሴ 24 ቀን 2013 ዓ.ም
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም