መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ማን ቀረ ከጸጋ ?

የትምህርቱ ርዕስ | ማን ቀረ ከጸጋ ?

 

 

“ነገር ግን እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን ።” ኤፌ. 4፡7። 

 

“ይታደሉታል እንጂ አይታገሉትም” ይባላል ። እግዚአብሔር ሲሰጥ እንቀበለዋለን እንጂ እጅ ጠምዝዘን አንቀበለውም ። እንዲሁ በጸጋ የሚሰጠን ነገር አለ ። በልመና የምንቀበለው ፣ በብርቱ ፍለጋ የምናገኘው ስጦታ አለ ። /1ቆሮ. 14 ፡ 1 ፤ ያዕ. 1 ፡ 5/ በተፈጥሮ የሆነልን ፣ በእምነት የምንቀበለውም ጸጋ አለ ። ሰዎችን በተሰጣቸው ጸጋ እናከብራቸዋለን ፣ የሰጣቸውን እግዚአብሔርን እናመሰግናለን ። ወታደር ራሱን ለማስከበር ሳይሆን አገሩንና ወገኑን ለመጠበቅ እንዲታጠቅ ጸጋም ለባለጸጎቹ ሳይሆን ለእኛ ጥቅም የተሰጠን ነው ። የፈውስ ጸጋ ያለው ሰው ለታማሚው የበለጠ ጠቃሚ ነው ። እርሱ ግን በክርስቶስ ከፈሰሰለት ሰማያዊ ፍቅር የተነሣ ድውያን ሲፈወሱ ያመሰግናል ፣ ይደሰታል ። ሌሎች በእጁ እየተፈወሱ እርሱ ግን ያልዳነበት ደዌ ይኖራልና በዚህ ትሕትናን ይማራል ። ሰዎች በጸጋው ቢመዝኑትም የግሉን የፍሬውን አናሳነት በማየት በራሱ ያዝናል ። ጸጋ የተሰጣቸውን ሰዎች ለራሳችን ስንል መንከባከብ መልካም ነው ። ድንበር የሚጠብቀው ወታደር ሲነሣ አገር እንዲደፈር ፣ ጠባቂ ከሌለም ዘራፊ ከተማ ሰብሮ እንደሚገባ ጸጋ ያላቸው ሰዎች ሲነሡ የተያዘ ክፋት ይለቀቃል ፣ የታሰረ ደዌ ይፈታል ። ጸጋ ያላቸውን ሰዎች ላጥፋ ብሎ መነሣት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማፍረስ መታገል ነው ። ጸጋ ያላቸውን ሰዎች ብንሰድባቸው ፣ ብናጠፋቸው ጸጋቸውን መውሰድ አንችልም ። የተሰጣቸው ሌባ የማይሰርቀው ነው ። በሕዝብ አስተያየት አልተቸሩምና በሰው ትችት አይራቆቱም ። ታድለው ያገኙት እንጂ ታግለው የማረኩት አይደለም ። በሰው ላይ እንዲህ ያለ ጸጋን የሚያፈስስ እግዚአብሔርን ብናመሰግን ለእኛም ጸጋ ይበዛልናል ። ጸጋ የሚበዛው በትሕትና ነውና ። 

 

በሌለን ጸጋ መታገል ያለንን ጸጋ ማስወሰድ ነው ። ጸጋ እሳት ነውና እሳቱን መቆስቆስ ትተን ፍም በሌለበት እፍ ብንል ይህ ላይነድ ያኛው ይከስማል ። እግዚአብሔር ያማረንን ሳይሆን የሚያምርብንን ጸጋ ይሰጠናል ። አስቀድሞ ሲፈጥረንም የአካልና የሰውነት መዋቅራችን ለሚሰጠን ጸጋ እንዲስማማ ሆኖ የተሠራ ነው ። ከሁሉ በላይም በገዛ ገንዘቡ የሚያዝዘው እግዚአብሔር ነውና ይህኛው ይሁንልኝ ማለት አንችልም ። ሳንጠይቅ ሰው ሆነናል ። ሳንጠይቅ መንግሥተ ሰማያት ተዘጋጅቶልናል ። ለምነን ከተቀበልነው ሳንለምን የተቀበልነው እጅግ ውድ ነው ። ጸጋንም በሚመለከት እርሱ የመረጠውን ሲሰጠን መደሰት ይገባል ። ብዙ ሰዎች ከጸጋቸው መፈናቀል ይገጥማቸዋል ። ይህም በሦስት ነገሮች ነው፡- የመጀመሪያው ጸጋቸውን በማባከናቸው ጸጋቸው ሊወሰድ ይችላል ። ሁለተኛው ፣ ከመዳን ጸጋ ውጭ ዘላለማዊ የሆነ ስጦታ የለም ። ዘላለማዊ የሆነ ድውይ የመፈወስ ጸጋ የለም ። ለምሳሌ በሰማይ ታማሚዎች የሉም ። ሦስተኛው ከጸጋቸው ራሳቸው ይሸሻሉ ። ይኸውም በጸጋቸው ደስታን ሲፈልጉ ያጣሉ ፤ በዚህ ምክንያት አኵርፈው ይቀመጣሉ ። ደስታ ስሜት ነው ፣ ጸጋ ግን እውነት ነው ። ደግሞም ሁልጊዜ በጌታ እንጂ በጸጋችሁ ደስ ይበላችሁ ተብሎ አልተጻፈልንም ። 

 

እኛ የምንጠቀመው ከራሳችን ጸጋ ይልቅ በሰዎች ጸጋ ነውና የሌሎች ጸጋ ለእኔ ነው ብለን ማሰብ አለብን ። ጸጋን የፈለግንበት ጸጋ ስለሌለን አይደለም ። የመጀመሪያው ጸጋ እንዳለን አለማወቃችን ነው ። ሁለተኛው በሰው እጅ ላይ ያየነው ጸጋ ስላጓጓን ነው ። አንዳንዱ ጸጋ ስመ ጥር ሊያደርግ ይችላል ። አሁን የምንከጅለውን ጸጋ የተመኘነው በዓለም ሁሉ ለመዞር ነው ? ባለጠጋ ለመሆን ነው ? አስደማሚ ሰው ለመሆን ነው ? ታይታን ከፈለግን ሰባኪ መሆንን መመኘት አያስፈልግም ። የሚያስፈልገው የፊልም ተዋናይ መሆን ነው ። ዓለምን ለመዞር ከፈለግንም የትንቢት ጸጋ ሳይሆን ጥሩ ሯጭ መሆን ለዚያም ልምምድ ማድረግ መልካም ነው ። ባለጠጋ ለመሆንም ተግቶ መሥራት እንጂ ድዉይ የመፈወስ ጸጋ አስፈላጊያችን አይደለም ። ጸጋን ለግል ዝና ግንባታ መጠቀም እግዚአብሔርን የመካድ ኃጢአት ነው ። ጸጋን መቀበል የእግዚአብሔር እንደራሴ መሆን ነው ፣ አምባሳደር ራሱን የሚያሳይ ሳይሆን አገሩንና መንግሥቱን ወክሎ የሚኖር ነው ። ጸጋም የተቸረው ሰው የላከውን እግዚብሔርን ማሳየት አለበት ። ይህ ፍላጎት ሳይሆን ግዴታ ነው ። እግዚአብሔር ጸጋ የሰጠን ድካማችንን ለመሸፈን ነው ። በጸጋችን ግን የሌሎችን ድካም የምናጋልጥ ከሆነ እግዚአብሔር የለም ብሎ እንደ መካድ ነው ። 

 

እኛ ተኝተን የተቀበልነው ፣ እንዳለን ሳናውቅ ይዘነው የምንዞረው ፣ በሰው ላይ እየከጀልነው ገንዘባችን የሆነ ጸጋ አለ ። ያመኑ የተጠመቁ ሁሉ ጸጋ አላቸው ። ሁሉ ዓይነት ጸጋ የለንም ፣ ከጸጋም ባዶ አይደለንም ። ጸጋን በሚመለከት ሙሉ በሙሉ ድሀ እና ሙሉ በሙሉ ባለጠጋ የለም ። 

 

ጸጋን እንደ ባለጠግነቱ መጠን የሰጠ ፣ ለእያንዳንዳችንም ያለ አድልኦ የናኘ እግዚአብሔር ቡሩክ ነው ! 

 

 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 18 ቀን 2013 ዓ.ም 

 

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም