መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የብርሃን ጠብታ » ጠላቶችህን ውደዳቸው

የትምህርቱ ርዕስ | ጠላቶችህን ውደዳቸው

“ቀንዴን ከፍ ለማድረግ ባሰበ ጊዜ በጠላት መካከል ከበበኝ ።” ቅዱስ አግናጥዮስ

“እንቅፋት የሚጥለው ወደፊት ነው” ይላል የአገራችን ሰው ። እንቅፋቱ የሚያም ቢሆንም መንገዱን ግን ያጋምሳል ። ጋሬጣ በተቀመጠ ቍጥር ከነሕመማችን ወደፊት እየሄድን ነው ። የእንቅፋቱ ዓላማ አቍስሎ ወደ ኋላ ሊመልሰን ፣ የተመታንበት ቦታ በምሬት እያለቀስን እንድንኖር ሊያደርገን ነው ። እንቅፋት ከመታን ተራምደናል ማለት ነው ። እንቅፋት አለ ተብሎ ጉዞ አይቀርም ። እንቅፋቱን ግን እንደ ዕድል ከተጠቀምነው ከነሕመሙም ቢሆን እልፍ ያደርገናል ። እግዚአብሔር እየፈዘዘ ያለውን ማንነታችንን የሚያነቃው በእንቅፋቶች ነው ። ከእንቅፋት ጋር ተከባብሮ መኖር ይቻላል ። ካልሄዱበት አይመጣም ። ከተራመድን ግን እንቅፋት ይገጥመናል ። ሰነፎች እንቅፋት የለባቸውም ። ምክንያቱም ከመቀመጫቸው አይነሡምና ። ሀኬተኞች እንቅፋት አይገጥማቸውም ፤ ምክንያቱም ከመኝታቸው አይወርዱምና ። የማይሠሩ ሰዎች አይሳሳቱም ። የሚሳሳት ሥራ የጀመረ ነውና ። አለመሳሳት ፍጹምነት አይደለም ። አለመሞከር ነው ። እንደ ተፈጠርን መጥተን እንዲሁ መሄድ ይቻላል ። ፍሬ የማያፈሩ ሰዎች ግን ምድርን ያጎሳቁላሉ ። የተሰጣቸውን ዕድል ለተጨማሪ ስንፍና ስለሚጠቀሙበት ይቆረጣሉ ። እንቅፋትን በሚመለከት ሦስት ዓይነት ሰዎች አሉ፡- ዘለው የሚያልፉ ጎበዞች ፣ ቆስለው የሚሻገሩበት ጽኑዓን ፣ ዘላቂውን ራእይ ሳይሆን ጊዜያዊውን ሕመም አስበው ወደ ኋላ የሚመለሱ ደካሞች ።

ሰውዬው ድሀ ነው ። የድህነቱ ምንጭ ግን ፍርጃ ሳይሆን ስንፍና ነበር ። ዝናቡ ሲመጣበት በገዛ ቤቱ ይንቆራጠጣል ። ወደማያፈሰው በኩል እየሄደ ይቀመጣል ። አንድ ጊዜ ጠግኖ በሰላም መኖር ሲችል ክረምት በገዛ ቤቱ እያባረረው ይኖራል ። ታዲያ ደኅና ጣራ የነበረው ወደ መስኮቱ አጠገብ ነበርና በቤቱ ከዝናብ ተጠልሎ ማዶ ማዶ ያያል ። አንድ ባለጠጋም በዝናብ እየተደበደበ ከብቶችን ሲነዳ አየውና፡- “እንኳን ባለጠጋ አልሆንሁ ዝናብ ይመታኝ ነበር” አለ ይባላል ። እጆቻችን በሥራ ከቆሸሹ ቤታችን ንጹሕ ይሆናል ። እጆቻችን ሥራን ተጸይፈው ንጹሕ ከሆኑ ኑሮአችን ጎስቋላ ይሆናል ። ዝናብን የሚፈራ ከቤቱ አይወጣም ። ከቤቱ የማይወጣም እንጀራ አይበላም ። ይልማ ዴሬሳ የተባሉ ባለሥልጣን በክረምት የበታች ሠራተኛቸው አርፍዶ ሲገባ ቀድመው ይጠብቁታል ። “ለምን አረፈድህ ?” ቢሉት “ዝናቡ ይዞኝ ነው” አላቸው ። እርሳቸውም፡- “አንደኛህን ክረምት ሲወጣ ለምን አትመጣም?” አሉት ይባላል ።

ጠላት በተለያየ መንገድ ይነሣል ። ሰይጣን የመንገዳችን እንቅፋት ፣ የግባችን ባላጋራ ነውና ብዙ ድምፆችን በማሰማት ከመንገዳችን እንድንቀር ይታገለናል ። አንዳንድ ጠላት ውጫዊ ነው ። አንዳንድ ጠላት ግን ውስጣዊ የገዛ ሥጋችንን የተተገነ ምኞት ሊሆን ይችላል ። ዐረቦች፡- “ቤት ውስጥ ካለ አንድ ጠላት ውጭ ያለ መቶ ጠላት ይሻላል” ይላሉ ። ሰይጣን የሰዎችን ፈቃድ ተጠቅሞ ልባቸውን መቆጣጠር ይፈልጋል ። ልባቸው የክፉ ምኞቱ መድረክ ከሆነ እርሱን በግብር የሚመስሉት ልጆቹ ይሆናሉ ። ሰይጣን አመክንዮን ፣ ክፋትና ምቀኝነትን ስለሚያስታጥቃቸው የሚጠሉን ሰዎች ራሳቸውን በጨለማው አምሳል ይቀርጻሉ ። በታሪክ ሁሉ እንደ ታየው ግን ጠላት ያሳድጋል እንጂ አያሳንስም ። በሕይወታችን ከመፍዘዝ የምንወጣው እንቅፋት ሲገጥመን ነው ። ያን ጊዜ መንገዳችንን በትክክል ማየት እንጀምራለን ። ዋጋ ከፍለን ስለምንጓዝም በቀላሉ ውጥናችንን አንተውም ። መውደቅ ቢገጥመንም የተስፋ ችቦ የሚለኮሰው ሰውዬው በፈቀደ መጠን እንጂ ለአንድ ጊዜ ብቻ አይደለም ። የጠፋውን እምነት በተስፋ መፈለግ ፣ የራቀንን ፍቅር በተስፋ ገንዘብ ማድረግ ይቻላል ። ሰው ተስፋ ሲቆርጥ ራሱን ይጠላል ፣ ራሱንም ሲጠላ ሰዎችን እየጠላ ይመጣል ። የቆሰለ ሰው ከሕመሙ ጋር እልህና ቀናዒነት በውስጡ ይመጣል ። ጠላትንም የሚያሸንፈው በሥራ ብቻ መሆኑ ሲገባው ያለ ሰዓት ገደብ መሮጥ ይጀምራል ። ድንገተኛ ኃይል ሰውን ከተፈጥሮ በላይ እንዲራመድ ያደርገዋል ። በአደጋ ሰዓት ወፍራሙ ሰው በቀጭን ቀዳዳ ሾልኮ ይወጣል ። እግሮቼ መራመድ አይችሉም የሚለው ሰው ችግር ሲገጥመው በሩጫ ያመልጣል ። ጣር የያዘው ሰው የአደጋ ድምፅ ሲሰማ በሽታው ሄዶለት ፣ ከአልጋ ላይ ወርዶ ደጅ ላይ ይገኛል ። አስቸጋሪ ሁኔታዎች የሚያመጡልን ዕድል አለ ። የምንጠቀምበት ኮምፒዩተር እንኳ በመሳሳት ሌላ አዲስ እውቀት እንድናገኝ ያደርገናል ። ተሳስተናል ፣ ግን አዲስ ነገር ብልጭ ብሎልናል ።
ጠላት አልባ ስንሆን ፍዝ እንሆናለን ። ጠላት አልባ ስንሆን ምቾት ሥራ ፈት ያደርገናል ። ጠላት አልባ ስንሆን አእምሮአችን መፍትሔ ማፈላለግ ያቆማል ። ጠላት አልባ ስንሆን ሥጋችን እየዛለ ፣ እውቀታችን እየተነነ ፣ መንፈሳችን እየተዳከመ ይመጣል ። ጠላት አልባ ከሆንን የማንጠቅም የማንጎዳ ተደርገን ተቆጥረናል ማለት ነው ። ጠላት አንፈጥርም ፣ የተፈጠሩትን ጠላቶችም መፍራት አይገባንም ።

እግዚአብሔር ቀንድን ከፍ ከፍ ያደርጋል ። ቀንድ መለያ ነው ። ቀንድ ኃይል ነው ። ቀንድ የጽናት መገለጫ ነው ። ቀንድ የዜማ ዕቃ ነው ። ቀንድ መከላከያ ነው ። ቀንድ ክብር ነው ። እግዚአብሔር ይህን ቀንድ ለማሳደግ የሚጠቀመው አንድ ነገር አለ ። በጠላት ይከበናል ። ለካ ይህም አለ የሚል አዲስ እውቀት የምናገኘው ጠላት ሲነሣብን ነው ። ያለንን ነገር መጠቀም የምንጀምረው ጠላትን ድል ለመንሣት ስንነሣ ነው ። ቀንድ አልባ ከሆንን በቀላሉ እንበላለን ። ጠላት ባይኖር ቀንድ አያስፈልግም ነበር ።

ቅዱስ አግናጥዮስ፡- “ቀንዴን ከፍ ለማድረግ ባሰበ ጊዜ በጠላት መካከል ከበበኝ” አለ ። አንድ ሰውም፡- “ጠላቶችህ አንተ ራስህን ከምታየው በላይ በጠራ መልኩ ያዩሃል ። ጠላቶችህ ኃይለኛ ሃያሲዎችህ ናቸው” ብሏል ። ጠላቶች ስላሉ የጠራ ሥራ እንሠራለን ማለት ነው ። ሳንከፍላቸው የሚያርሙን ፣ እንከናችንን ያለ ይሉኝታ የሚነግሩን ጠላቶቻችን ናቸው ። ለበጎ ከተጠቀምንበት ጠላቶቻችን የጠራ ተግባር እንዲኖረን እኛን የሚጠብቁ ዘቦች ናቸው ። ይህን ተረድቶ ደስ የሚለው ግን ብልህና ግቡን የሚያውቅ ነው ። አንድ የላቲኖች አባባል፡- “የመድረሻ ወደቡን የማያውቅ መርከብ ከየትኛውም አቅጣጫ የሚነፍስ ነፋስ አይረዳውም” ይላል ። የሚያጠፋው ነፋስ ወደ ግብ የሚገፋ ይሆናል ። ነገር ግን መድረሻን ማወቅ ይፈልጋል ።

ከክፉ ነገሮች በጎ ነገርን የሚያወጣ እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው !

የብርሃን ጠብታ 25

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 20 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም