መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ?

የትምህርቱ ርዕስ | ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ?

የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ ! እንዴት ከእኔ ጋር ኖርህ ? እኔ አንተን ማመን አቅቶኝ ፣ አንተ እኔን አምነኸኝ እንዴት ከእኔ ጋር ኖርህ ? የጸናኸውን ዓለት ትቼ ስሄድ ፣ የባሕር ላይ ኩበት የሆንሁትን እንዴት እኔን መረጥህ ? ፍቅር ዳገት ሆኖብኝ ጥላቻ ከሚገዛኝ ፣ የወዳጄን የብዙ ዓመት ውለታ በአንድ ቀን ስህተት ከምደመስስ ፣ ሲያፈቅሩኝ እየተጠራጠርሁ ፣ ሲጠሉኝ ግን ከማምነው ፣ መልከ ብዙ ከሆንሁት ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ? የተቀበልሁትን ሳላጣጥም ፣ ለጸለይሁበት መልሴ ምስጋና ሳላቀርብ መልሼ ሌላ አምጣ ከምልህ ፣ ቸልታ ከማበዛው ፣ ለጽድቅ ረጅም ቀጠሮ ከምሰጠው ፣ ለወንጌል ተኝቼ ለሣንቲም ከምነቃው ፣ ዘመናት ባለፉ ቍጥር ከበጎነት ከምቀንሰው ፣ የምችላቸው ላይ ክንዴን እያጸናሁ ፣ የማልችላቸውን ከማመልከው ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ? በአሸዋ ገበታ ላይ መናህን ከምበላው ፣ በአንድ ልብ ወሬ እያዳመጥሁ በአንድ ልብ መጸለይ ከማልችለው ፣ በአዋጭ ስሌት ከእኔ ጋር መኖርህ ያከስርሃል ። በወዳጅነት ሚዛን ዘጠና ዘጠኙን ወዳጆች ትተህ አንዱን አጥፊ ፍለጋ መምጣትህ ያስወቅስሃል ። ገብቶ የማያልቀውን እኔነቴን መጠበቅ ያደክምሃል ።

ጌታ ሆይ እንዴት ከእኔ ጋር ኖርህ ? ካልበላሁ ከማልስቀው ፣ ያልከኝን ትእዛዝ እየሻርሁ ፣ ያልሁትን ጸሎት ለምን አልፈጸመም ብዬ ከማኮርፈው እኮ ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ? ሽማግሌ ሳይገባብን ይህን ሁሉ ዘመን ፣ እኔ ስጮህ አንተ ዝም እያልህ ፣ እኔ ሳኮርፍ አንተ እያናገርህ እንዴት ከእኔ ጋር ኖርህ ? ጌታዬ ሆይ ለሕማም ለሞት አብቅቼህ ዛሬም አድሮ ጥጃ ነኝ ። የተሻለ ሰው ፈልግ ፣ ከማያድግ ችግኝ ጋር ፣ ከሁልጊዜ ሀሁ ፣ ከሁልጊዜ ዳዴ ጋር አትኑር ። አብረውኝ የተተከሉ ዛፍ ሁነው ፍሬአቸው ዓለሙን ሲያጠግብ እኔ ግን አድሮ ቃሪያ ከሆንሁት ፣ አቃጣይ ልጅ ጋር ምን ትሠራለህ ? ንጹሕ ልብስ እንጂ ንጹሕ ልብ ከማልወደው ፣ ቃሌ ለስልሶ ልቤ ከሻከረው ፣ በሰዎች ዕድል ደስተኛ ከማልሆነው ፣ እንግዶችን ለመቀበል ከመትጋት ይልቅ ከማኮርፈው ፣ ከሰጠኸኝ ላይ መስጠት ከተሳነኝ ፣ ራስ ወዳድነት ካጠቃኝ እንዴት ከእኔ ጋር ኖርህ ? ለካ ላትተወኝ መሐላ አለህ ። አንተ ከተውኸኝም የሚይዘኝ የለም ። በአማኑኤል ስምህ ፣ በቃል ኪዳን ፍቅርህ ከእኔ ጋር ስለሆንህ አትለየኝም ። ግን ልጠይቅህ ከእኔ ጋር እንዴት ኖርህ ?

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 14 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም