የትምህርቱ ርዕስ | አምነው ሞቱ

አምነው ሞቱ

“በውድ ልጁም ፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን ፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት ። ጸጋውንም በጥበብና በአእምሮ ሁሉ አበዛልን ።” ኤፌ. 1 ፡ 7-8 ።

ክርስቶስ ውድ ነው ። እንደ እርሱ የሚወደን የለም ። እኛም ከሁሉ አብልጠን ብንወደው ኖሮ በታደልን ነበር !! እንኳን ውድ ልጁን ፣ የበደለ ልጁን ለሞት አሳልፎ የሚሰጥ ወላጅ የለም ። ልጃቸውን ለዘመቻ በላኩ ወላጆች እንደነቃለን ። “ማን በሞተለት አገር ልትኖር ነው !” ብለው ሲልኩ ፣ “የእርሱን ሞት ማን ይሙትለት ” ብለው ሲፎክሩ መስማት ይገርማል ። እነዚህ ሁሉ ጠላትን ገድለው አገርን እንዲያድኑ ልጆቻቸውን ልከዋል ። ቅዱስ እግዚአብሔር አብ ግን ልጁን ግደል ሳይሆን ሙትላቸው ብሎ ልኮታል ። ይህ ልጅም ውድ ልጅ ነው ። ልጆች ሁሉ ከአባታቸው ቤት ወጥተው ርቀው ይኖራሉ ። የአባታቸውን ስም ሲያስጠሩ ይኖራሉ ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ከአባቱ ለቅጽበት ሳይለይ “የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አባት ይመስገን” ተብሎ አባቱን ሲያስጠራ ሲያስመሰግን ይኖራል ።

በዘመናት ሁሉ እኔ ልሙትልህ የሚል መሐላ ነበረ ። ሞቶ ያሳየ ግን ላይኖር ይችላል ። እኔ ልሙትላችሁ ብሎ ምሎ የመጣ ፣ ሞቶ ያሳየን ግን የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። የፍቅር ጥግ የሆነውን ለሌላው የመሞትን መሥዋዕትነት ለዓለም ይገልጥ ዘንድ ወደ ዓለም መጣ ። በመለኮታዊ ባሕርይው ሊሞት አይችልምና የእኛን መዋቲ ሥጋ ለብሶ በመስቀል ላይ ዋለ ። መለኮት በሥጋ ሞተ ። ሥጋ ብቻውን ቢሞት የዕሩቅ ብእሲ/የፍጡር ሞት ዓለምን ማዳን ባልተቻለው ነበር ። ሥጋም በመለኮት ከበረ ። ሞትን ድል ነሺ ሆነ ። ይህ ሁሉ የተደረገልን በውድ ልጁ ነው ። ሰው የድኅነቱን አድራሻ ማወቅ ክርስቲያናዊ ግዴታው ነው ። እርሱ ያዳነንም እንድንፎክር ሳይሆን መልካም እንድንሠራ ነው ። በሥራ ብቻ ልዳን የሚል እምነትን ሲጥል ፣ በእምነት ብቻ የሚልም በአፉ ብቻ ጌታን አከብራለሁ ባይ ነው ። እምነታችን የሚያሠራ ፣ ሥራችንም የሚያምን መሆን ይገባዋል ።

ነቢያት ነባዮች ቢባሉ ስለ ክርስቶስ ትንቢት ተናግረው ፣ ሐዋርያት ሐዋርያት ቢባሉም ስለ ክርስቶስ ሰብከው ፣ ሰማዕታት ሰማዕታት ቢባሉ ስለ ክርስቶስ ሞተው ነው ። ሁሉ ስለ እርሱ ይወደዳሉ ። እርሱ በባሕርይው ውድ ነው ። ሙሽራ ነውና ሚዜዎች አሉት ። ቅዱሳንም ከክርስቶስ አይለዩም ። ሚዜዎችም ሙሽራውን ያጎላሉ ፣ ቅዱሳንም ክርስቶስን ለዓለም ያሳያሉ ። ሙሽራ የሌለው ሚዜ ፣ ሚዜም የሌለው ሙሽራ የለም ። እርሱ ቤዛ ሁኗልና የቅዱሳን ምልጃም ወደዚህ ቤዛነት እንደርስ ዘንድ ንስሐና እምነትን ገንዘብ እንድናደርግ የሚረዳን ነው ። ይልቁንም የቤተ ክርስቲያን የአንድነት መለኪያዋ ምልጃ ነው ። እግር ሲመታ ላይ ያለው ዓይን የሚያለቅሰው አካል ስለሆነ ነው ። በሰማይ ያሉት ቅዱሳንም ስለ እኛ በማሰባቸው አንድ አካል መሆናችንን ይገልጣሉ ። እጸልይልሃለሁ እያለ የሚናገር ሰው በሰማይ የሚያድሩት ቅዱሳን መጸለያቸው ክርስቶስን ይጋርዳል ብሎ ካሰበ አስቸጋሪ ነው ።

በእርሱ ያመኑ ሕያዋን ናቸውና የሕያውነት ሥራ ይሠራሉ ። ያረፉ ቅዱሳን ሙታን አይደሉም ። ይህ ክርስቶስን የሙታን አምላክ ብሎ እንደ መናገር ነው ። እርሱም በቃሉ፡- “እኔ የአብርሃም አምላክ ፥ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ ነኝ የሚል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እናንተ የተባለውን አላነበባችሁምን ? የሕያዋን አምላክ ነው እንጂ የሙታን አይደለም ።” ማቴ. 22፡31-32። ይህ ቃል ሲነገር አብርሃምና ይስሐቅ ከሞቱ ሁለት ሺህ ዓመት ሁኗቸዋል ። እነርሱ ግን ሕያዋን ናቸው ። የአብርሃም አምላክ መባልን የወደደ የድንግል ልጅ ስንለው ይበልጥ ደስ ይለዋል ። በክርስቶስ ሆነው የሞቱም በዕረፍት አሉ ። ክርስቶስ ለኑሮአችን ትርጉም ፣ ለሞታችንም አድራሻ ነው ።

አቤቱ በሃይማኖት ሁነው ያረፉን አባቶቻችንን አስብ ። እኛንም አምነን ለመሞት የበቃን አድርገን ። አሜን ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /14

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 25 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም