መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ውስጣዊ ቍጣ » ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 1

የትምህርቱ ርዕስ | ውስጣዊ ቍጣ / ክፍል 1

“የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና።” ያዕ. 1፡20።

ሱናሚ ከባሕር ወለል ላይ በእሳተ ገሞራ ወይም በመሬት መንቀጥቀጥ የሚከሰት ፣ በከፍተኛ ፍጥነትና ከፍታ የሚበርር የማዕበል ፣ ማዕበል ነው ። አደጋውን ስናየው በባሕር ዳርቻ ላይ ያሉ ከተሞችንና መዝናኛ ቦታዎችን ወዳለመኖር የሚለውጥ ፣ የባሕሩን እንስሳ መሬት ላይ የሚተፋ ፣ የመሬቱን ንብረት ወደ ባሕር የሚከት ድንገተኛ መቅሰፍት ነው ። ይህ ውስጣዊ ማዕበል ፣ የማዕበል ማዕበል የሚል መጠሪያ ተሰጥቶታል ። የሚያደርሰውን ጉዳት በሚዛን ማስቀመጥ አይቻልም ። እሳተ ገሞራና የመሬት መንቀጥቀጥ ሊያመጣው ይችላል ። እንደ ሱናሚ ያለ ውስጣዊ ማዕበል በሰው ውስጥ ይፈጠራል ። ይህ ማዕበልም ከተቀበረ ቍጣ የሚወጣ ፣ ለህልውና ምክንያት በማጣት የሚከሰት ነው ። ራስን አናውጦ በዙሪያ ያሉትን ሰዎችና ንብረትን የሚያወድም ሊሆን ይችላል ። ለውስጣዊ ማዕበል መነሻ የሚሆነው ውስጣዊ ቍጣ ምንድነው ? ስንል ለዘመናት በውስጣችን ሲብላላ የኖረ ፣ ነገር ግን ያልተፈወሰ ሕመም ነው ። ህልውናን መጠራጠር ፣ የሚኖሩበትን ምክንያት ማጣት ለዚህ ማዕበል መፈጠር ምክንያት ይሆናል ።

ውስጣዊ ቍጣ ከላያቸው የተረጋጉ በሚመስሉ ሰዎች ልብ ውስጥ ሲብላላ የሚኖር ነው ። እነዚህ ሰዎች ይህን እሳት ተሸክመው ከላያቸው ግን የውኃ ባሕርይ ተላብሰው ይኖራሉ ። ይህን በእሳት ላይ ያለ ቀዝቃዛ ባሕርይ ሊያመጡ የቻሉት በተለያየ ምክንያት ነው ። የመጀመሪያው ከልጅነት ጀምሮ እርሱ ወይም እርስዋ “ጨዋ ፣ ትዕግሥተኛ ፣ መልስ የማይሰጡ ፣ የእግዜር በግ” እየተባሉ ስላደጉ ከዚህ ውዳሴ ከንቱ ባሻገር ፈውሳቸውን ሊፈልጉ አልቻሉም ። ሁለተኛው ምክንያት ያሉበት ኃላፊነት ራስን ደብቆ መኖርን የሚያስገድድ ሊሆን ይችላል ። በዚህ መንፈሳዊ እውቀትና ኃላፊነት ላይ እንዴት ይቆጣሉ ? እንዳይባሉ ውስጣቸውን አምቀው የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው ። ሦስተኛው ምክንያት የውስጥ እንፋሎታቸውን ቢያወጡ አንታመንም ብለው ማሰባቸው ነው ። እነዚህ ሰዎች መንፈሳዊ ስለተባሉ ፣ ስለሚያገለግሉ ፣ ብዙዎችን ስለሚያጽናኑ ጉዳታቸው አመኔታ የሚያገኝ አይመስልም ። “እገሌ ተጨነቀ ቢባል ማን ያምናል ?” እያሉ ሰዎችም ያዳምቁላቸዋል ። ውስጣዊ ኩርፊያቸውን በቀልድ ሸፍነው የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው ። በዚህ ምክንያት ለውስጣዊ ማዕበል ይዳረጋሉ ። አራተኛው ምክንያት በልጅነታቸው እናታቸውን ወይም አባታቸውን አጥተው ምነው ባገኘኋቸው በሚል ስሜት የወላጆቻቸውን ሥዕል በመሳል የደከማቸው ስለሆኑ ውስጣዊ ቍጣ ይፈጠርባቸዋል ።

ውስጣዊ ቍጣ ያለባቸው ሰዎች የዕለት ታማሚዎች አይደሉም ። ዛሬ በድንገት ቢለወጡብን ምክንያቱ እኛ ሳንሆን የኖረውና የተዳፈነው እሳት ሊሆን ይችላል ። ይህ ውስጣዊ ቍጣ ሲፈነዳ ሁለት ዓይነት አደጋዎች ሊከሰቱ ይችላሉ ። የመጀመሪያው፡- ራስን መጉዳት ነው ። ራስን መጉዳት በኃጢአት ፣ በተለያዩ ልምምዶች ሊሆን ይችላል ። የተከለከሉ ነገሮችን ማነው ተዉ የሚለኝ ? በሚል ስሜት ያደርጋሉ ። እንደ እነርሱ የተጎዱ ሰዎችን ጓደኛ ማድረግ ይሻሉ ። ቍጣው ኃይለኛ በመሆኑ ሁሉንም ነገር ለማድረግ ወደ ኋላ አይሉም ። ለጥፋታቸውም የተለያዩ ሰዎችን ተጠያቂ ስለሚያደርጉ የጸጸት ስሜት የላቸውም ። ትክክል አይደላችሁም የሚላቸው መርህ ቢመጣ እንኳ ሕይወት ከትክክልና ከስህተት ያለፈ ምሥጢር አላት ብለው ያምናሉ ። ሁለተኛው፡- ውስጣዊ ቍጣ ማዕበል ሲፈጥር ሰዎችን መጉዳት ሊከሰት ይችላል ። ክስተቱም ሁን ብሎ ሰዎችን ማጥቃት ፣ ስለ ሰዎች ክፉ ክፉ ብቻ ማሰብ ፣ ማንም ሰው የሚቀርበኝ ሊጎዳኝ ነው ብሎ መጠንቀቅ ፣ የሌላውን ስምና ክብር ማጉደፍ ነው ። አለፍ ሲሉም የትዳር ጓደኛና ልጆች ላይ አደጋ ሊያመጡ ይችላሉ ። ሳይታከም የኖረው ያ ቍጣ ለንብረት ግዴለሽ ፣ ለወጪም የማይሳሳ ሰው አድርጎ ያንን ሰው ብኩን ያደርገዋል ።

አንዳንዳችም ይህን ቍጣ በመንፈሳዊ ቅድስና ስም ሊሸፍኑት ይሞክራሉ ። ቍጣቸውንም ቅዱስ ቍጣ ሊያሰኙት ይፈልጋሉ ። ሰዎችን ለማንቀጥቀጥ በተጠንቀቅ የሚኖሩት እነዚህ ሰዎች መንፈሳዊና ሥነ ልቡናዊ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል ። ከሰላማቸው ጋር ሳይገናኙ መኖር ለራሳቸውም ለቀረቡአቸውም ስቃይ ነውና ።

እኛስ ውስጣዊ ቍጣ ይኖርብን ይሆን ?

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 24 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም