መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ህልውናዬን ዘምርበት

የትምህርቱ ርዕስ | ህልውናዬን ዘምርበት

ምእመኑ በታላቅ ምሬትና የነፍስ ዝለት ሁኖ አምላኩን ጠየቀ ፡-
ጌታ ሆይ በሰዎች ላይ የማየው በጎ ነገር “ምነው የእኔ ቢሆን” እላለሁ ። የእኔ አልታይህ እያለኝ በሌሎች ዕድል እጓጓለሁ ። ፍለጋ አያልቅም ወይ ? ትላንት የማልደርስበት የመሰለኝን ዛሬ አልፌ ሄጃለሁ ፣ በጥቂት ስጸልይ በብዙ ተቀብያለሁ ። ጌታ ሆይ ታዲያ የልብ ሙላት የሚሆነኝ ምንድነው ?
እግዚአብሔርም መልስ ሰጠ ፡-
ልጄ ሆይ ራበኝ ለሚለው ጥያቄህ እንደራራሁ አልረካሁም ለሚለው ጥያቄህም ራራለሁ ። መላው የሰው ዘር ራበኝና አልረካሁም በሚል ጥያቄ ለሁለት ተከፍሏል ። ስለ ተራቡ ሰዎች የእርዳታ ተቋማት ፣ የመንግሥታት ስብሰባ አጀንዳ አላቸው ። አልረካሁም ለሚሉ ግን ሁሉ ይፈርድባቸዋል ። ልጄ ሆይ በሰማይ ላይ ያለውን ውብ ቀስተ ደመና ወደ ታች ስበህ በሠዓሊው ሸራ ላይ ማተም አትችልም ። በሌሎች ላይ የምታየውን ውበት ነጥቀህ የራስህ ማድረግ በፍጹም አትችልም ። ሰማያዊውን አምላክ ግን በልብህ መጋበዝ ፣ የክርስቶስን ውበት በዘመንህ መግለጥ ትችላለህ ። ከቀስተ ደመና ውበት ከቆነጃጅትም ድምቀት ይልቅ በጎነት የበለጠ ያምራል ። ቀስተ ደመና ይሰወራል ፣ ቁንጅናም ከንቱ ነውና ይረግፋል ። የእኔ ጽድቅ ግን ለዘላለም ይኖራል ። አንተ ጋ ያለውን በጎ ዕድል ሌላው ይመኘዋል ። ያልበሰለው ማንነትህ የያዘውን እያሳነሰ እንደ ሕፃን በሰው እጅ ባለው ያለቅሳል ። ላንተ የሰጠሁህ የማይኮረጅ ጥበብ ፣ የማይገኝ ልዕልና ነው ። የእኔ በረከት የማይደገም ልዩ ነው ። የሰው አለመርካት በሦስት ነገር ተሸፍኗል ፡- በጥርስ ፣ በልብስና በቤት ። እኔ ግን እያረሩ የሚስቁትን አዝንላቸዋለሁ ። ጥሩ ለብሰው ውስጣቸው የሚበርዳቸውን አለሁ እላቸዋለሁ ። ባማረ ቤት ውስጥ ያለውን ድብቅ ልቅሶም ዘንበል ብዬ እሰማለሁ
ልጄ ሆይ ወደ ራስህ በጣም አትኩረህ አትይ ። በመስተዋት ራሱን በጣም የሚያይ ሞኝ እየሆነ ይመጣል ። ዞር ያለበት እስኪመስለውም የምናብ ዓለም ውስጥ ይገባል ። ራስህን ያለ እኔ ጽድቅ አትየው ። ያልተዘጉ ፋይሎችህ እንደሚያውኩህ አውቃለሁ ። በንስሐና በቃል ኪዳን ዝጋቸው ። አልችልም ብለህ ከመቀመጥህ ይልቅ እችላለሁ ብለህ መውደቅህ ያስደስተኛል ። የልብ ሙላትን የምታጣው ነፍስህ እውቀት ፣ መንፈስህ አምልኮት ፣ አካልህ በጎ ምግባር ሲራብ እንደሆነ እወቅ ። ባዶነት የነፍስ ጠኔ መሆኑን ብዙ ጊዜ አልነገርኩህምን ? ነፍስ በእንጀራ እንደማትጠግብ አላስተማርኩህምን ? ደግሞም ልብህ ከፍቅር ሲባረድ ፣ ይቅር ማለት ሲያቅትህና ይቅር ያልከውን መልሰህ ስታስታውስ እንደምትጎዳ የነገርኩህን ረሳኸውን ? ስለሞላም ስለሚሞላም ደስ አይበልህ ። እኔ አምላክህ ስለሆንሁ ብቻ ደስ ይበልህ ። የሙት ልጆች ማደጊያ ውስጥ ያሉ ደህና ቁርስ ይበላሉ ፣ ወላጅ ካላቸው የድሀ ልጆች ይልቅ በጥሩ ይያዛሉ ። እነርሱ ግን ምነው ወላጅ በኖረኝ ይላሉ ። መዓዛ ካለው ምግብ ይልቅ እኔ እበልጣለሁ ፣ ከጥሩ ውኃ ይልቅ እኔ አረካሃለሁና አይዞህ ልጄ ሆይ ንቃ ፣ ተነቃቃ ።
ምእመኑም ትንፋሹን ወደ ውስጡ አስገብቶ ተረጋግቶ መጠየቅ ጀመረ ፡-
ጌታ ሆይ አንተ ስትናገረኝ እጽናናለሁ ፣ መጽናናቴ ግን ዕድሜ ያጣና ወደ ተውኩት ጉዳቴ እመለሳለሁ ። በሌሎች ላይ የማየውን ኀዘንና ሰቆቃ ከማዘንና ከመርዳት ወደ ራሴ አምጥቼ እታመመዋለሁ ። የሚጠዘጥዘው ሰው ሳይ ሲጠዘጥዘኝ ያድራል ። ደግሞ እንዲህ ብሆንስ እያልሁ ራሴ ያመለጠኝ መስሎኝ በግምት እሰቃያለሁ ። ጌታ ሆይ አታረጋጋኝም ወይ ?
እግዚአብሔርም በጽድቅ መለሰ፡-
ልጄ ሆይ ልደትና ሞት በቅጽበት ነውና ለደቂቃም መረጋጋትህን ውደደው ። እኔ እየሸነገልሁ አልናገርም ፣ ከዓለም ማባበል የእኔ ተግሣጽ ሕይወትን ያሳርፋል ። እኔ የመልሶች መልስ ነኝ ። የውዶችም ውድ ነኝ ። ሁሉ በእኔ ምክንያት ይወደዳሉ ፤ እኔ ግን ስለ ራሴ የምወደድ ነኝ ። መጽናናትህ ዕድሜው አጭር ሲሆን አትደንግጥ ፣ ዘላለማዊ ስጦታ እኔ ብቻ እንደሆንሁ ታውቅ ዘንድ ይህ መናወጥ ባንተ ውስጥ ሆኗል ። ያለኸው የመምጣቴ ዋዜማ ላይ ነውና ቃሎቼ መፈጸም ስላለባቸው ሁከትና ሽብር ይሆናል ። አስቀድሜ ነግሬህ እንዲህ የታወክህ ባልነግርህ ምን ልትሆን ነበር ? የሌሎችን ስቃይ ተውሰው ሲሰቃዩ የሚያድሩ እንዳሉ አውቃለሁ ። የእነርሱ ስቃይ ግን ቤዛ አይሆንምና ሌሎች አያርፉበትም ። እኔ ግን የዓለም ቤዛ ነኝና በቁስሌ ፈውስን ፣ በሞቴ ሕይወትን ሰጥቼሃለሁ ።
ልጄ ሆይ የሰዎችን ችግር ባታስቀር መቀነስ ግን አንተ የምትኖርበት ዓላማ መሆኑን እወቅ ። ሰይጣን እንዲህ ብትሆንስ እያለ ሲያስፈራራህ “እግዚአብሔር ይገሥጽህ ፣ በማይላሉ እጆች ተይዣለሁ” በለው ። ተኝተህም ነቅተህም የምጠብቅህ እኔ ነኝና አትፍራ ። ስሜ ባንተ ላይ ስለ ተጠራ እንዲሁ አልተውህም ። በዋጋ ገዝቼ በነጻ አልለቅህም ። አንተ በጥዋት የፀሐይ ጮራ ደስ ይልህ ይሆናል ። እኔ ግን ባንተ ደስ ይለኛል ። አንተ አቁሳይ ልጅ ነኝ ብትልም ፣ እኔ ግን የደስታ መደምደሚያዬ እልሃለሁ ። አንተ በራስህ ላይ ያለህ ዓላማ ቢጠፋህ እኔ ግን ልገለጥብህ እየሠራሁህ ነው ። የሚመጣውን ጊዜ ትዋጅ ዘንድ ዛሬ በቤተ ሙከራ ውስጥ እያሳለፍኩህ ነውና ልጄ ሆይ በርታ ። እኔ አልታዘብህምና ሁሉንም ንገረኝ ። የድንጋይ ሸክምህን አቅልዬ ንጉሣዊ ህለተ ወርቀ አስጨብጥሃለሁ ። ማቅህን ቀድጄ ወርቅ አለብስሃለሁ ። አንተን ሳይሆን ባንተ ላይ ያለውን የእኔን ፍቅር አያለሁ ። መንገዱን አትፍራ ፣ የምድረ በዳ ወዳጅህ ይኸው አጠገብህ ነኝ ። ይህን ድምፄን ስማና ህልውናዬን ዘምርበት ።
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 5
ተጻፈ አዲስ አበባ
መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም