መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » “ማን ያንከባልልልናል ?”

የትምህርቱ ርዕስ | “ማን ያንከባልልልናል ?”

 “እርስ በርሳቸውም፡- ድንጋዩን ከመቃብር ደጃፍ ማን ያንከባልልልናል ? ይባባሉ ነበር” ማር. 16፡3
ክርስቶስ ሲቀበር ደስታቸው የተቀበረ ፣ ተስፋቸው የወደቀ ብዙዎች ነበሩ ። ያድነናል ያሉት ሲሞት ፣ እስራኤልን ይቤዣል ያሉት በግፈኞች እጅ ሲወድቅ የብዙዎች ልብ ንቃቃት አበጅቶ እንባና ደም ማፍሰስ ጀምሮ ነበር  ። ቅዱሳን ሴቶች ኀዘናቸውን ለመጨረሻ ጊዜ ለመግለጥና የክርስቶስን ትዝታ በልባቸው ለማኖር ወደ መቃብሩ ገስግሰዋል ። እርሱ ግን ዛሬም ሕያው ነውና የትዝታ አምላክ አይደለም ። ሉቃስን ቀለዮጳ ተስፋ ቆርጠው ፣ ዓለም ጥንትም ለደግ አትሆንም ብለው ወደ ኤማሁስ እየገቡ ነበር ። ከተስፋ መቍረጣቸው ጋር ያድሩ ዘንድ አልፈለገም ። ተስፋ መቍረጥ ለደቂቃ እንኳ ከባድ ነው ። በራሳቸው ሳይሆን በአምላካቸው ተስፋ መቍረጣቸው ደግሞ የበለጠ አስጨናቂ ነው ። እህል ቢያንቅ በውኃ ይውጡታል ፣ ውኃ ቢያንቅ በምን ይውጡታል ? ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡታል ? ሐዋርያትም ተስፋ ቆርጠው ማኅበሩን በትነው ወደ ጥብርያዶስ ሊጓዙ ፣ ማኅበረ ወንጌል የኅብረት ሥራ ማኅበር ሊሆን ተቃርቦ ነበር ። ትንሣኤው ግን ሴቶችን ከመቃብር ስፍራ ወደ ሕያዋን ሰፈር ያሮጠ ፣ ሉቃስና ቀለዮጳን ከኤማሁስ በምሽት ወደ ኢየሩሳሌም የመለሰ ፣ ማኅበረ ሐዋርያትን ያጸና ነው ። በትንሣኤ ድል የተነሣው ተስፋ መቍረጥ ነው ። ክርስቲያን ያዝናል ፣ ስሜት አለውና ። እንዳዘነ ግን እንዳይቀር ክርስቶስ አለው ። የክርስቲያን አንድነት ይነቀነቃል ፣ እንዳይበተን መንፈስ ቅዱስ ይታደገዋል ። እንዳዘንን ፣ እንደ ተበተንን ፣ ተስፋ እንደ ቆረጥን ብንቀር ምን እንሆን ነበር ?

ሴቶች በዚያ ማለዳ ወደ መቃብሩ የገሰገሱት ቅዱስ ሥጋውን ሽቱ ቀብተው ለመሰናበት ነበር ። እርሱ ግን የሚሰናበቱት ሳይሆን አብረውት የሚኖሩት ሕያው ነው ። ሴቶችን ያስጨነቃቸው አብረዋቸው ወንዶች ስለሌሉ ድንጋዩን ማን ያንከባልልልናል ? ብለው ነው ። ከዚያ የበለጠ ነገር ሆኗል ። ሞት ድል ተነሥቷል ። ሲነሡ የፈሩት ሲደርሱ የለም ። በርቀት ሁሉም ነገር አስፈሪ ነው ፣ ሲደርሱበት ግን ቀላል ነው ። ከብዙ ዓመታት በፊት ይህች ቀን አስፈሪ ነበረች ፣ እንደርሳለን የሚል አሳብ አልነበረንም ። እግዚአብሔር ግን ያየልንን ፍርሃታችንም አይነጥቀንም ። ወንዶች የሚያንከባልሉት ድንጋይ ሲያስጨንቃቸው ነገሥታት የማያንከባልሉት ሞት ተንከባለለ ። አቅማቸውን አስበው ቢቀሩ ኑሮ ድንጋዩም ሞትም ተንከባሎ አያዩም ነበር ። አልችልም ብሎ ከመቅረት መጀመር መልካም ነው ። እስራኤል በጌሤም እያሉ ቀይ ባሕር አልተከፈለም ፣ ሲደርሱ ግን ተከፈለ ። የካህናቱ እግር ዮርዳኖስን ሲረግጥ ፈሳሹ ቆመ ። የነገው ባሕርም የሚከፈለው ዛሬ ላይ ሳይሆን ነገ ላይ ነው ። ከቀኑ በፊት አሳብና የአሳብ ፍልሚያ ነው ፣ በሰዓቱ ግን ለሰዓቱ የሚሆን ኃይልና ብርታት ይመጣል ። እነዚያ ሴቶች ድንጋዩን ሲጠብቁ ተንከባልሎ አገኙት ። ወደ መቃብሩ ዘልቀው ሽቱ መቀባትን ሲያስቡ መነሣቱን ሰሙ ። ትንሣኤ እግዚአብሔር ለልጆቹ እንግዳ ሥራ እንዳለው የሚያመለክት ነው ።
“ሰንበትም ካለፈ በኋላ መግደላዊት ማርያም የያዕቆብም እናት ማርያም ሰሎሜም መጥተው ሊቀቡት ሽቱ ገዙ ።” ሰንበት የሚያልፈው ቅዳሜ ሠርክ ላይ ነው ። ቀን ላይ እንዳይገዙ ሰንበት ያግዳቸዋል ። ሰንበቱ እንዳለፈ ግን ወዲያው በምሽት ሽቱውን ገዙ ። በሕሊናቸው የአይሁድን ቍጣ ፣ የወታደሮቹን ክልከላ አላሰቡም ። ድንጋዩን ማን ያንከባልልልናል ብለው ተጨነቁ ። ሐዋርያት ደግሞ ድንጋዩን ሳይሆን አይሁድና ወታደሮቹን ፈሩ ። አንዱ የሚበረታበት የአንዱ ድካሙ ነው ። ችግራችን ለየራስ መሆኑ ለመረዳዳት መልካም ነው ።በብዙ ያመኑ በጥቂት ነገር እጅ ይሰጣሉ ። የሚያስፈራው ቀን ያላስፈራቸው በማያስፈራው ቀን እጅ ይሰጣሉ ። ብዙ ሰው የጸሎታቸው መልስ በሚወለድበት ቀን ይሞታል ። መግደላዊት ማርያም ሰባት አጋንንት የወጣላት ሴት ናት ። ከምን እንደ ዳነች ታውቀዋለች ። የያዕቆብ እናት ማርያም የሥጋ ዘመድ ናት ። ሰሎሜም የዮሐንስ ወንጌላዊ እናት ናት ። ያዕቆብም መልእክት ጽፏል ። የሰሎሜም ልጅ በአዲስ ኪዳን አምስት መጻሕፍት የጻፈ ነው ። እነዚህ ሴቶች ማንም በማይገኝበት ሰዓት የተገኙ የክርስቶስ ወገኖች ናቸው ። ለአገር የሚሞት ፣ ለልጅ አደባባይ የሚቆም ፣ ለቤተሰቡ ዋጋ የሚከፍል ብዙ አለ ። ለክርስቶስ ቀንበር የሚሸከም ፣ የጨለማውን መንገድ በድፍረት የሚጓዝ ግን በጣም ጥቂት ነው ። እኛስ ብንሆን ለሰው የኖርነውን ያህል ለእግዚአብሔር አለመኖራችን ሐቅ አይደለም ወይ ?
ድንጋዩ የተንከባለለው ክርስቶስ እንዲነሣ አይደለም ። መላእክት መቃብሩ ባዶ መሆኑን ለማሳየት አንከባለሉት እንጂ ። እርሱ በዝግ መቃብር ተነሥቷል ። ድንግል ማርያም የመልአኩን ብሥራትና የልጇን ቃል አምናለችና ከሙታን መካከል አልፈለገችውም ። የቅርብ ቤተሰብ በሌለበት ወደ መቃብር መሄድ አልተለመደም ። በቀራንዮ የነበረችው ድንግል ማርያም በመቃብሩ ስፍራ አልነበረችም ። በልጇ መነሣት አምናለችና ። ወታደሮች ሲጠብቁ መላእክትን ያዩት ሴቶች ፣ ወታደሮችን በድን ሁነው ፣ መቃብሩ ባዶ ሁኖ ሲያዩ ልባቸው ስንጥቅ ብሎ ነበር ። ስጋት የነበረው የአይሁድ ቍጣ ፣ የወታደሮች ጥበቃ ፣ የድንጋዩ ክብደት ሁሉም የሉም ። ክርስቶስ ሲነሣ እነዚህ ሁሉ ፍርሃቶች ድል ተነሡ ። እግዚአብሔር ሲነሣ የፈራናቸው ይፈሩና ያልፈራነው እግዚአብሔርን መፍራት እንጀምራለን ። መልአኩ እግዚአብሔር ኃያል ነው ለማለት በጎበዝ ምሳሌ ተገለጠላቸው ። እግዚአብሔር ወልድ በሥጋ ተሰውሮ እንደ ተገለጠ ፣ መልአኩም በመልአክ አርአያው ሳይሆን በጎበዝ ምሳሌ ተገለጠ ። ሰው የሚችለው ጥቂት ነገር ነው ፣ ሰውን ይቅር በለኝ ስንለው እንኳ የበደልነውን ዝርዝር ነገር መንገር የለብንም ። ምክንያቱም የሰው አቅም ያለፈውንም ጉዳት ለመሸከም ደካማ ነውና ።የመጀመሪያውን ብሥራት ለድንግል ማርያም የነገረ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነበረ ፣ አሁንም ትንሣኤውን ለሴቶች መልአክ አበሰረ ። መልአክ ቢወድቅ አምላክ መልአከ ሁኖ አላዳነውም ፣ ሰው ቢወድቅ ግን አምላክ ሰው ሁኖ አዳነ ። መላእክት ግን በዚህ ቅር አላላቸውም ። ፈቃዱ ፈቃዳቸው ፣ ፍቅሩ ፍቅራቸው ነውና ይወዱናል ። መልአኩም የክርስቶስን መነሣት አበሰረ ።
አትደንግጡ ፤ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ትፈልጋላችሁ ፤ ተነሥቶአል ፥ በዚህ የለም ፤  እነሆ እርሱን ያኖሩበት ስፍራ ። ነገር ግን ሄዳችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ለጴጥሮስም፦ ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፤ እንደ ነገራችሁ በዚያ ታዩታላችሁ ብላችሁ ንገሩአቸው አላቸው።”
የመልአኩ ክስተት ፣ የድንጋዩ መንከባለል ፣ የመቃብሩ ባዶ መሆን ያስደነግጣል ።ያልጠበቁት ደስታም ከጠበቁት ኀዘን በላይ ክው ያደርጋል ። መቃብሩ ባዶ መሆኑን በእምነት ተቀበሉ አላለም ፣ በዓይን እዩ አለ እንጂ ። እኛ ግን ዛሬ እናምናለን ፣ ነገ እናያለን ። ለጴጥሮስም ንገሩ አለ ። ለካደው ሐዋርያ መልአኩ ከሥላሴ መልእክት ይዞ መጣ ። ጴጥሮስ በሰማይ ይታወቃል ። መላእክት በውድቀቱ አዝነዋል ። ሰይጣን ደስ ብሎት ነበረ ። አሁንም የሰይጣን ማፈር ለሴቶች ተገለጠ ። ንስሐ እንዲህ አድርጋ ሰይጣንን ጉድ ትሠራዋለችና ጠላት አይወዳትም ። ጌታችን በብሥራቱና በትንሣኤ ቅድሚያ የሰጠው ለሴቶች ነው ። ሔዋን የስህተት በር በመሆኗ እጅግ አዝናለችና ። ደም የሚመልስ ልጅ ክርስቶስን ወለደች ። በአንድ ሌሊት ሦስት ጊዜ ለካደ ጴጥሮስ ፣ ሰባት አጋንንት ለነበሩባት መግደላዊት ማርያም ትንሣኤ ተገለጠ ። እግዚአብሔር ንስሐን የሚያከብር ፣ ወድቀው በተነሡ የሚደሰት አምላክ ነው ። ጠላቶቹ ሥጋውን ገደሉ ፣ ፍቅሩን ግን መግደል አልቻሉም ። የማይሞተው ፍቅሩ ጴጥሮስን እንደ ገና አሰበው ።
ወደ ክርስቶስ ለመገስገስ ስናስብ ብዙ ድንጋዮች ከፊት ለፊታችን ይታዩናል ። እንዴት እንደሚነሡ ባይገባንም ጉዞውን ግን ማቆም የለብንም ። የአምላክ ዝምታ የሌለ ያህል ይመስላል ። እግዚአብሔር ደክሞ ፣ ሰው የበረታ ይመስላል ። ግፍ ዛሬም ቀጥሏል ። ምስኪኖች ይበልጥ እየደኸዩ ፣ ግፈኞች እየናጠጡ ነው ። በእኛና በክርስቶስ መካከል ድንጋይ ሁነው የጋረዱን ፣ ጸሎታችንን ከደመና በታች ያስቀሩብን እልከኝነቶች ፣ ራስ ወዳድነቶች ፣ እኔ ብቻ ያልኩት ይሁን ባይነቶች ፣ ለጎረቤት መቃብር የመቆፈር ሴራዎች ፣ አታላይነቶች ናቸው ። በእጃችን ሽቱ ይዘናል ፣ ለሕያውነቱ ሳይሆን ለሞቱ ልንቀባው ፈልገናል ። እግዚአብሔርን የትላንት አምላክ ብቻ ማድረግ ያንን ሽቱ ያስታውሳል ። እግዚአብሔር ድሮ ይሰማኝ ነበር እያሉ መኖር ያን ሽቱ ይገልጣል ። ብቻ ብናመነታም መቆም የለብንም ። ስንደርስ ወታደሮች ወድቀው መልአክ ቆሞ ፣ ድንጋዩ ተንከባሎ በላዩ የእግዚአብሔር የሠራዊት አለቃ ተቀምጦ እናገኘዋለን ።
ለዛሬው ዘመን፡- በሽታ ትልቅ ቋጥኝ ሁኖ እያስጨነቀ ፣ የልጆች ጠባይና ዱርዬነት ወላጆችን ፈሪ እያደረገ ፣ በትዳር ውስጥ ቋንቋው መደባለቁ እያታከተ ይገኛል ። ለሁሉም ጥያቄዎች መልሳችን ጭንቀት ብቻ መሆኑ ፣ የማንሰማውን ምክር ስንጠይቅ መዋላችን ፣ ለምሬት እንጂ ለቅድስና ምንም ጊዜ ማጣታችን ፣ ብሉ ተብለን ለመንፈሳዊ ነገር መለመናችን ትንሣኤን እንዳናይ እያደረገን ነው ። እኛ ድንጋዩ ያሳስበናል ፣ እግዚአብሔርን የሚያሳስበው ድንጋዩ ልባችን ነው ። ሰበር እንበል ። ትንሣኤ ዛሬም አለ ።
ጸሎት
ክብርህ የሚያበራ ፣ ችሎታህ የማይለካ ጌታ ፣ አንተ ካስጨነቀን ነገር በላይ ነህ ። እኛ ይህን አልፈን ወደ ሩጫችን ለመግባት እናስባለን ። እግዚአብሔር ምን እያለኝ ነው ብለን ከልባችን ለመጻፍ እንሰንፋለን ። አንተ ግን የሞተውን ውስጣችንን አስነሣልን ። ስንጓዝ እግራችንን የሚያሳጥሩትን ፣ አንተን ስናስብ የሚጋርዱንን ቋጥኞች በትንሣኤህ ገላግለን ። አመንሁ እያልን እንዳንፈርስ ፣ ቆምሁ እያልን እንዳንወድቅ ለዘላለም ደግፈን ። በሚያበራው ኃይልህ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ 6
ሚያዝያ 14 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም