መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » የሉቃስ ወንጌል » የኤማሁስ መንገደኞች

የትምህርቱ ርዕስ | የኤማሁስ መንገደኞች

የኤማሁስ መንገደኞች
“እኛ ግን እስራኤልን እንዲቤዥ ያለው እርሱ እንደ ሆነ ተስፋ አድርገን ነበር ፤ ደግሞም ከዚህ ሁሉ ጋር ይህ ከሆነ ዛሬ ሦስተኛው ቀን ነው ።” ሉቃ. 24፡21
. . .
ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ
ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ
በክርስቶስ ደም ታጥባ
ምድር ፋሲካን/ደስታን ታደርጋለች ።
የአርማትያሱ ዮሴፍ ለክርስቶስ መቃብሩን ለቀቀ ። ክርስቶስ እንደ ድሀ ኑሮ በባለጠጎች መቃብር ተቀበረ ። በቁማቸው የሚላስ የሚቀመስ አጥተው ፣ የሞቱ ቀን በሬ ታርዶ የሚሸኙ ሙታንን ሥቃያቸውን ለመካፈል ክርስቶስ ኑሮው የምስኪን ፣ መቃብሩ የባለጠጎች ሆነ ። በቁማቸው ሲሰደቡ ኑረው ሲሞቱ የሚመሰገኑትን ፤ በቁማቸው መናፍቅ ተብለው ሲሞቱ ታላቅ አባት ተብለው የሚወደሱትን ሕመማቸውን ሊካፈልላቸው ክርስቶስ በባለጠጎች መቃብር ተቀበረ ። የቆመ ደግ ፣ የሬሳ ክፉ አላውቅም የምትለዋን ዓለም ለመኰነን ክርስቶስ በባለጠጎች መቃብር ተቀበረ ። ዮሴፍ ዘአርማትያስ እንደሚሞት እንጂ መቼ እንደሚሞት አያውቅም ነበረ ። በሞቱ ላይ ድራማ የሚሠሩትን ለመኰነን በቁሙ መቃብሩን ከውቅር ድንጋይ አሠራ ። ይህንን መቃብሩን ለክርስቶስ ቅዱስ ሥጋ ለቀቀ ። መቃብራቸውን የሚለቁ ቀርበው የሚገንዙ አይደሉም ፣ በዘመድ መልክ ቀርቦ የገነዘው ፣ ቅዱስ እያለ ሽቱ የቀባው ዮሴፍ ዘአርማትያስ ነበረ ። ጌታችን በሥጋ ዘመኑ ከእናቱ ድንግልናዊ ወተትን ለመነ ። ሁለት ጊዜም ላይጠጣው ውኃ ለመነ ። አንዱ ከሳምራዊቷ ሴት ሲሆን ሁለተኛው በመስቀል ላይ ሁኖ ተጠማሁ በማለት ሆምጣጤ ያመጡለት ሰዓት ነው ። ከልደቱ ቦታ የመቃብሩ ስፍራ ያማረ ነበረ ። ሁለት ዓመት ያህል በቤተ ልሔም እንደ ቆየ ፣ ለሦስት ቀን ያህል በመቃብር ቆየ ። ሟችም ቢሞት ፣ ገዳይም ቢገድል ለሦስት ቀን ነውና ተስፋ አትቍረጡ ሊለን ፈለገ ።
ጌታችን ከሙታን በተነሣ ቀን ልባቸው አዝኖ ወደ ኤማሁስ የሚጓዙ ሉቃስና ቀለዮጳ የሚባሉ ደቀ መዛሙርት ነበሩ ። ዓለም ክርስቶስን በመስቀሏ ታላቅ ተስፋ መቍረጥ ገጥሟቸው ነበረ ። ደግ ገድሎ ደግ ነገር መጠበቅ ፣ ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ የዓለም ጨዋታ ነው ። ሰባኪ ገድሎ ሰባኪ መናፈቅ ፣ ፀሐፊ ቀብሮ ፀሐፊ መሻት ፣ አፍቃሪን አደንዝዞ አፍቃሪ ማሰስ የጥላ ዓለም ጠባይ ነው ። በነጻ የመጣው ከሄደ በዋጋ ፣ ያለ ልፋት የመጣው ከሸሸ በታላቅ አሰሳ አይገኝም ። የፈወሰ እጅ መቸንከሩ ፣ ያጽናና አንደበት ሆምጣጤ መጋበዙ ፣ አልዓዛርን የፈለገ እግር በምስማር መታሠሩ ፣ ዮሐንስ ወልደ ዘብዴዎስን የሸሸገ ጎን በጦር መወጋቱ እንደ ሰው ሰውኛ ሲያዩት ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው ። ክርስቶስ ግን የሞተው በአብ ፈቃድ ፣ በራሱ ውድ ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስምረት ፣ በነቢያት ትንቢት ፣ በአበው ተስፋ መሠረት ነው ። የክርስቶስን ሞት በሥጋዊ አእምሮ ሲያስቡት ዕለቱን ተከስሶ ዕለቱን መሞቱ ፣ ሊሰቀል ታስቦ ቀድሞ መገረፉ ፣ ዳኛው ቀያፋ ምስክሩ ሎሌው መሆኑ በዓለም ተስፋ አስቆርጧቸው ነበር ። ከሕግ አኳያ የክርስቶስን ሞት ሲያዩት ፍርድ አጉዳይ ዓለም አሳዝናቸው ነበር ።
መግደላዊት ማርያም ተኝቶ አገኘዋለው ስትል በአትክልቱ ስፍራ ቆሞ አየችው ። የኤማሁስ መንገደኞች ከጀርባቸው ጥለውት በኀዘን ሲጓዙ አብሮአቸው ይጓዝ ነበረ ። ክርስቶስ የለም እያሉትም ከአጠገባቸው አለ ። ሲክዱት የማይክድ ነው ። ተስፋ መቍረጥ የእግዚአብሔር ሀልወት በአጠገባችን እንዳለ ያስረሳል ። ተስፋ የሚሆኑ ነገሮች ተስፋን አይሰጡም ። ተስፋ ራሱ እግዚአብሔር ነው ። በራሱ እግዚአብሔር ተስፋ ካላደረግን ጭላንጭሎች ወደ ጨለማ ፣ ፀሐይ ወደ ጽልመት ፣ ጨረቃ ወደ መሰወር ፣ ከዋክብት ወደ ደመና ሲገቡ ልባችን መፈራረስ ይጀምራል ። ጭላንጭል አዲስ ወዳጅ ፣ ፀሐይ የንጉሥ ፊት ፣ ጨረቃ ደግ መካሪ ፣ ከዋክብት ትውልድ ናቸው ። አዲስ ወዳጅ ብቅ ጥልቅ ሲል ፣ ንጉሥ ቃሉን ሲያብል/ሲዋሽ ፣ ደግ መካሪዎች አኪጦፌል ሲሆኑ ፣ ትውልድ የሞት ልጅ ሲሆን ልብ ይደክማል ። ተስፋ ግን እግዚአብሔር ነውና አሁንም ይቀጥላል ። ተስፋ ከልብ ሲታጣ ፊት የኀዘን አደባባይ ይሆናል ። አካል ቀፎ ነው ፣ ተስፋ ግን ሞተር ነው ። እግር ካላቸው ተስፋ ቢሶች እግር የሌላቸው ተስፈኞች ይደርሳሉ ። ፍትሕ ከዳኞች ፣ እውነት ከመሪዎች ፣ ጽድቅ ከካህናት ፣ እምነት ከደቀ መዛሙርት ቢጠፋም ገና ተስፋ አለ ። ተስፋ የጋረደንን ደመና ሰንጥቀን መንበረ ሥላሴን ስናይ የሚመጣ ነው ። ሁሉም ነገር ከስፍራው ይታጣል ፣ እግዚአብሔር ግን በማይናወጥ መንግሥት ይኖራል ። የፕሮቴስታንት እምነት መሥራች የነበረው ማርቲን ሉተር የእግዚአብሔርን የተስፋ ቃሎች ለማመን አቅም አጥቶ በትካዜ ተውጦ ሳለ ሚስቱ አየችና የኀዘን ልብስ ለብሳ፡- “ዛሬ የኀዘን ልብስ ለብሻለሁ ፣ ምክንያቱም አምላክህ እንደ ሞተ ያህል ተጨንቀሃል” አለችው ይባላል ። ጭንቀት አምላክን ገድሎ ጠላትን ሕያው ማድረግ ነው ።
ተስፋ በጆሮ ሹክ ሲል ገና ነው ይላል ። ሬሳ እየተጋዘም ገና ነው ። ተስፋ በዓይን ላይ ሲያርፍ ከተራራው ጀርባ ያለውን ያያል ። ተስፋ አፍንጫ ላይ ሁኖ የሕይወትን መዓዛ ያውዳል ። ተስፋ አፍ ላይ ሁኖ “ይህም ያልፋል” ይላል ። ተስፋ እጅ ላይ ሁኖ ድሆችን ከውድቀት ያነሣል ። ተስፋ ደርሶ ወደ ጨለሙ መንደሮች ይገባል ። ተስፋ ሰማይ ቆሞ ምድርን ያስጀምራል ። ተስፋ የአሁኑን ሳይሆን የሚመጣውን ፤ የሆንነውን ሳይሆን የምንሆነውን ያወራል ። ተስፋ ዜና አይሰማም ፣ ተስፋ አንድ ቀን ዜና ነኝ ይላል ። ተስፋ ትዕግሥትን ጣፋጭ ፣ ፍቅርን ብርሃን ፣ እምነትን ቆራጥ ያደርጋል ።
ሁለቱ ደቀ መዛሙርት ሞቱ ላይ ቀርተው ትንሣኤውን አልሰሙም ነበር ። ኀዘን በደስታ መተካቱን ያበሰራቸው አልነበረም ። ሐዋርያ ባይሄድላቸው የተነሣሁ ጌታ ሐዋርያ ሁኖ ሄደላቸው ። ሐዋርያ ተነሣ ይላል ፣ ክርስቶስ ግን ተነሣሁ ይላል ። በብርቱ ስናዝን ራሱ ይመጣል ። አገልጋዩ ሲያጽናና ፌዝ ለሚመስላቸው አልቃሾች ራሱ ክርስቶስ ለልባቸው ሊናገር ይመጣል ። ሉቃስና ቀለዮጳ ከኢየሩሳሌም ወደ ሰሜን አቅጣጫ ቀጥሎ ወደ ምዕራብ አድርገው ወደ ኤማሁስ አሥራ አንድ ኪሎ ሜትሮችን ተጉዘዋል ። መንገዳቸው ግን ፋሲካ በዓል ላይ እንደ ቆየ በደስታና በጉልበት ሳይሆን ዓለም ስለ ሰቀለችው ስለ ክርስቶስ በማሰብ ኀዘን የሞላበት ነበረ ። ስለ ዓለምና ስለ ሰው በጥልቀት ለማወቅ መሞከር በመጨረሻ ተስፋ መቍረጥ ያመጣል ። ገብስ ገብሱን ካላዩ የሰውና የዓለም ነገር ይሰብራል ። ተስፋ ቢቆርጡም የሚያወሩት ስለ ክርስቶስ ነበረ ። ስሙ በተነሣበት ለመቅረት የማያስችለው ጌታ ከእነርሱ ጋር ነበረ ። ሰዓቱ ሠርክ እየተቃረበ ያለበት ፣ አቅጣጫው ወደ ምዕራብ ወደ ፀሐይ መጥለቂያ ነበረ ። የማታው ፀሐይ ዓይናቸው ላይ አርፋ መንገዳቸውን በእምነት እንጂ በማየት እየረገጡ አልነበረም ። አጠገባቸው ያለውንም ጌታ ማየት አልቻሉም ። ፀሐይ ስትጠልቅ የማይጠልቅ የጽድቅ ፀሐይ አለ ። እርሱም ያመነው ክርስቶስ ነው።
የልባቸው ስብራት አርያም ደርሶ ክርስቶስ ሊታደጋቸው አብሮ ይሄድ ነበረ ። ለቀባሪው አረዱት እንደሚባለው ስለ ክርስቶስ ለክርስቶስ ይናገሩ ነበረ ። ጥልቅ ስሜታቸውን ሲገልጡ ጥልቅ እውቀትን ነገራቸው ፤ ልባቸውን ሲቆርሱለት እንጀራ ቆረሰላቸው ። ስለ ቅርቡ የዓርብ ፍርድ ሲያወሩ ስለ ነቢያት ትንቢት ተረከላቸው ። ድብቆች ከክርስቶስ ምንም አያገኙም ። እንደ ሰው ተሸንፈው እንደ መልአክ ለመግደርደር ይፈልጋሉ ። “ደክሞኛል ያዘኝ” ለሚሉት የክርስቶስ እጆች ተዘርግተው ይኖራሉ ። አላዩትም ማለት አላያቸውም ማለት አይደለም ። አላመኑም ማለት አልተነሣም ማለት አይደለም ። እስክናየው ቢጠብቅ እስከ ዛሬም አንድንም ነበረ ፣ እስክናምነው ቢጠብቅ እስከ ዛሬም መልካም አይሆንልንም ነበረ ።
እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ ነው ። በማወቁ አይጠረጠርም ። እግዚአብሔር ግን የማያውቃቸው ነገሮች አሉ ።
1-  ይቅር ያለውን ኃጢአት አያውቀውም ፣
2-  ተስፋ የሌለውን ኃጢአተኛ አያውቀውም ፣
3-  ብቻውን የሚበረታ ፍጡርን አያውቀውም ፣
4-  የፈጠረውን ትንሽ ሰው አያውቀውም ፣
5-  የሠራውን ከንቱ ቀን አያውቀውም ፣
6-  የማይነጋውን ሌሊት አያውቀውም ፣
7-  የማያልፈውን መከራ አያውቀውም ፣
8-  የማይችለውን ኃይለኛ አያውቀውም ፣
9-  ፍቅሩ ያልያዘውን ሰው አያውቀውም ፣
10-         የማይጠገነውን ሰባራ አያውቀውም ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 7/ሀ
ሚያዝያ 17 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም