የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ሰላምና አንድነት

 

“በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ ።” ኤፌ. 4፡3።

ሰላም ማሰሪያ ፣ አንድነት ጥበቃ ይፈልጋል ። ሰላም የስብሳባ ውሳኔ ፣ የአንድ ወገን ጥረት ፣ የመልካም ምኞት መግለጫ አይደለችም ። ሰላም ታስራ የቆመች ናት ። ማሰሪያው ሲላላ ብዙ መናጋት ይከሰታል ። ሕፃናቱ ፣ ወጣቶቹ ፣ ጎልማሶቹ ፣ ሽማግሌዎቹ የተሳሰሩበት ገመድ አለ ። ሕፃናቱ አብረው አፈር ፈጭተው ፣ ቡሄ ጨፍረው ማደጋቸው እንዲተሳሰሩ ያደርጋል ። ወጣቶች ችቦ ለቅመው ፣ ኳስ ተጫውተው አብረው መኖራቸው ሰላምን እንዳትሄድ አስሮ ይይዛታል ። ጎልማሶቹ ማኅበራቸውን ማጠናከራቸው ፣ ስለ ሀገር ማሰባቸው ሰላምን ይጠብቃታል ። ሽማግሌዎቹ ማስታረቃቸው ፣ መገሠጻቸው ለሰላም ማሰሪያ ነው ። ሕፃናቱን ከተፈጥሮ ለይተን አፈር እንዳይፈጩ ስንከለክላቸው በሽታ የማይችሉ ፣ የሚኖሩበትን ዓለም በጭምብል የሚጨብጡ ሆኑ ። እርስ በርሳቸው እንዳይጫወቱ ብለን የሰጠናቸው መጫወቻ ዕቃ ወዳድ እንዲሆኑ ፣ ለሰው ፍቅር የሌላቸው ፣ ዓይናቸው ለረጅም ሰዓት ቴሌቪዥንና ስልክ ላይ በማፍጠጥ ታማሚ እንዲሆን አደረግን ። ዘመድ እንዳይመጣ በር በመቆለፋችን ሰው የማይለምዱ ፣ ብቸኝነት የሚያጠቃቸው ሕፃናትን አተረፍን ። ሰላም በብዙ ማሰሪያ የተያዘች ናት ። ሰንበቴው ፣ ማኅበሩ ፣ በዓላቱ ፣ መስቀሉ ፣ ጥምቀቱ ሰላም የታሰረችበት ገመዶች ናቸው ። ልሂድ ስትል ተብትበው ስለያዙአት ሰላም ቆይታለች ። እነዚህ ገመዶች መላላት ሲጀምሩ ደግሞ ሰላም እየጠፋ መጣ ። 

ሰላም ገመድ ትፈልጋለች ፣ ሰላም ራስዋም ገመድ ናት ። ሰላም በብዙ ማሰሪያዎች ተይዛ ያለች ናት ። ብዙ የሚፈልጋት ስላለ ሰላም ልሂድ እያለች ታስቸግራለችና አስረን ማቆየት ያስፈልገናል ። አብረን ለመኖር ዋጋ  መክፈል ፣ ማኅበራዊነት እንዲጸና የተቻለንን ሁሉ ማድረግ ፣ በሰርግም በልቅሶም መተባበር ያስፈልገናል ። አንደኛውን ስናመልጥ አንደኛው ገመድ እንዲይዘን አድርገን ሰላምን መተብተብ አለብን ። ሰላም ራስዋም ገመድ ናት ። አስራ ትይዘናለች ። እንዳንለያይ ፣ እንዳንበታተን ፣ እንዳንወድቅ ትይዘናለች ። 

“የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ” ይላል ። አንድነት ጥበቃ ይፈልጋል ። ጥበቃውም ትጋት ያለው መሆን አለበት ። ብዙ ዓይነት አንድነት አለና “የመንፈስን አንድነት” አለ ። የሥጋ አንድነት አለ ፣ ዘረኝነት ፣ የሀብት እኩያነት ያጠላበት አንድነት አለ ። የአእምሮ አንድነትም አለ ፣ በሰው ቍስል እንጨት የሚሰድ ፣ ድሀ ከምድር መወገድ አለበት ብሎ የሚያስብ ፣ ምድርን የጥቂቶች ብቻ ለማድረግ የሚመክር አንድነት አለ ። ይህ አንድነት ቢፈርስ የተሻለ ነው ። ሐዋርያው በትጋት ጠብቁ ያለው የመንፈስን አንድነት ነው ። ጥበቃና ትጋትን እስቲ እናስባቸው ። ጥበቃ በቀንና በሌሊት የማያቋርጥ ነው ። አንድነትም ያለማቋረጥ ልንጠብቀው ይገባል ። አብረን ሆነን መናቆራችን የሚያስከፍለን ዋጋ ቢኖርም መለያየት ደግሞ ከዚህ በላይ ዋጋ ያስከፍለናል ። በመለያየት ውስጥ መጠፋፋት ብቻ ይኖራል ። በመለያየት ውስጥ ማነስን እንወልዳለን ። ኃይላችን ይባክናል ። በአንድነት ውስጥ በጥቂት መሣሪያ ስናሸንፍ ፣ በመለያየት ውስጥ ግን ብዙ ቢኖረንም ድል የለንም ። ጥበቃ የቀኑን ፀሐይ ፣ የሌሊቱን ቍር የሚታገሥ ነው ። አንድነትንም ከስሜት እሳት ፣ ዘመናዊነት ከሚያመጣብን ቀዝቃዛነት በላይ ልንጠብቃት ይገባል ። አንድ የሆንነው በእግዚአብሔር እንጂ በፍላጎታችን አይደለም ። የእግዚአብሔርን ማሰሪያ እንቍረጥ ስንል እንጎዳለን ። አንድነት ጥበቃ ያስፈለጋት የቀን ወራሪ ፣ የሌሊት ሰባሪ ስላለባት ነው ። 

የአንድነት ምልክቶቻችንን አጥብቀን መያዝና ለዚያም መገዛት ያስፈልገናል ። የሚጠብቁ በትጋት ግን የማይጠብቁ ንብረት ያዘርፋሉ ። ዘረፋ ሲፈጸም የሰረቀው ብቻ ሳይሆን የተዘናጋው ዘበኛም ይጠየቃሉ ። ሌባ መዝረፍ እንደ ሥራው ነው ። ሌባ እንዳይመጣ ማድረግ አንችልም ። ተግተን ከጠበቅን ግን አንድነታችንን ማትረፍ እንችላለን ። አብረው የነበሩ ሕዝቦች ዛሬ  የተለያዩትን ብናስብ ምንም ትርፍ አላገኙም ። በመለያየት ውስጥ የሚጠቀሙት የሚጠሉን እንጂ የሚወዱን አይደሉም ። በመለያየት ውስጥ ግዛታችን ያንሳል ። አንድ የሆኑ ሕዝቦችን ለሁለት ከፍለን እንደ ተነፋፈቁ ሳይገናኙ እንዲሞቱ እናደርጋለን ። አንደኛው ለአንደኛው ስጋት ይሆናል ። ሰሜን ኮሪያ በጦር መሣሪያ ስታይል ፣ ደቡብ ኮሪያ ደግሞ በኢኮኖሚ አይላለች ። አንዳቸው ለአንዳቸው ግን ስጋት ናቸው ። አንድ የነበሩ ሕዝቦች ስለሚተዋወቁ አይከባበሩም ። የሚያነሱት ጦርነትም የሞኝነት ሁኖ ብዙዎችን ያስፈጃል ። በመለያየት ውስጥ ልጆቻችንን ጠላትህ እገሌ ነው በማለት ስለምናሳድጋቸው አእምሮአቸው ሰላም አይኖረውም ። 

ሰላም ከሄደች በኋላ መመለስ ከባድ ነው ። ጤና ሳለ ቀላል ፣ ከሄደ በኋላ ግን ብዙ ሕክምና አይተን የማናገኘው ነው ። አንድነትም ብዙ ሰራቂ አለበትና በትጋት ልንጠብቀው ይገባል ። እኛ ያልጠበቅነውን አንድነትም ማንም ሊጠብቀው አይችልም ። ማሰር ፣ መጠበቅ ፣ መትጋት የሚሉት ቃላት ሰላምና አንድነትን ለሚፈልጉ ሁሉ ወሳኝ ናቸው ። ቤተ ክርስቲያን አንድነትዋን ባጸናች ዘመን ቄሣሮች ሁሉ ይፈሯት ነበር ። አንድነትዋ ሲናጋ ግን እየተደፈረች መጣች ። ምዕራብና ምሥራቅ ተብላ በተከፈለች ጊዜ ሌሎች ሃይማኖቶች ተነሡ ። በአንድነት ለ400 ዓመታት የኖረች ቤተ ክርስቲያን 1600 ዓመታት ደግሞ በመለያየትና በመነቃቀፍ ትኖራለች ። ከተለያየን በኋላ አንድ ለመሆን ጊዜ ይፈጃል ። በቤተ ክርስቲያን መከፈል ያላመነውን ወደ እምነት የማምጣት ተልእኮን ዘንግተናል ። ያለው አገልግሎት በግ የመሰራረቅ እንጂ ፍየሎችን በግ የማድረግ አይደለም ። 

ሰላም ማጣት ያስንቀናል ፣ አንድነት ማጣትም ያሳንሰናልና እንንቃ። 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 13 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ