መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሰማይ ድምፅ » የምናይበት መስተዋት

የትምህርቱ ርዕስ | የምናይበት መስተዋት

“ሁሉ ለንጹሖች ንጹሕ ነው ፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የሆነ ምንም የለም፥ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል።” ቲቶ. 1፡15
ሐዋርያው ጳውሎስ ከአይሁድ ወገን የሆነው ጢሞቴዎስን የኤፌሶን ጳጳስ ሲያደርገው ፣ ከአሕዛብ ወገን የነበረውን ቲቶን ደግሞ የቀርጤስ ጳጳስ አድርጎ ሾሞታል ። ቲቶ ጳጳስ ቢሆንም ከመንፈስ አባቱ ከጳውሎስ የሚደርሰው ምክርና ማበረታቻ አልተለየውም ነበር ። ምክር ከሌለ ጉዞው ሁሉ ዋጋ የሚያስከፍል ይሆናል ። ምክር ካለ ለመፈጸም አቅም ቢጠፋ እንኳ አስቦ የሚመክረኝ አባት አለኝ የሚል ስሜት ውስጥን ያስደስታል ። የትኛውም መዐርግና ክብር ላይ ብንቀመጥ ምክር ያስፈልገናል ። መካሪ ከሌለ ዕድሜ ያጥራል ። ምክር ሰባት ጊዜ ተፈትኖ እንደ ተጣራ ብር ንጹሕ ሲሆን ወደ ክብር ማማ ያሸጋግራል ። በሰይጣን ዓለምም ክፉ ምክር ትልቅ ዋጋ ይሰጠዋል ። ኃጢአት ወደ ዓለም የገባው በክፉ ምክርና በክፉ መካሪ ነው ። አቤሴሎም በሚወደው አባቱ ላይ የዘመተው በአኪጦፌል ክፉ ምክር ነው ። ምክር በብርሃንና በጨለማው ዓለም ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ነው ። አብዛኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍልም ምክር ነው ።
ሐዋርያው ጳውሎስ ለቲቶ የሹመት መስፈርቶችን እየጻፈለት ነው ። ሹመት መስፈርት ያስፈልገዋል ። እውቀት ከመንፈሳዊነት ጋር ያሻዋል ። አሊያ ከሁለቱ አንዱ እንዲኖረው ይገደዳል ። እውቀት ባይኖረው መንፈሳዊ መሆን አለበት ፤ ምክንያቱም የእውቀት ግቡ መንፈሳዊነት ነውና በመንፈሳዊነቱ ይሾማል ። አሊያ አዋቂ መሆን አለበት ፣ ለራሱ ባይኖረውም ለሌላው መንገድ ያሳያልና ። እስከ ዛሬ ስረቁ ያለ ቄስ አልታየም ። ከሁለቱ ንጹሕ የሆነ ሰው ግን መሾም የለበትም ። ሹመት መስፈርቱ ጎሣ ፣ ትውውቅ ፣ ውለታ ፣ ኮታ ፣ ወረፋ ፣ ተረኛ መሆን የለበትም ። ሕይወቱ ደካማ ፣ ብዙ የክስ ፋይል ያለውን ሰው መሾም ለመያዝ ይረዳል ብለው ብዙዎች ያስባሉ ። ባለጌ ግን በምንም አይያዝምና ሙከራው ከንቱ እንደሚሆን በታሪክ ታይቷል ። ከጨዋ መጣላት ክብሩን ስለሚፈልግ አያዋርድም ፣ ባለጌ ግን ክብር የማይፈልግና ክብር የማይሰጥ በመሆኑ ያዋርዳል ። ሥርዓት ለሌለው ሰው የሚሰጥ ሹመትም ፍጻሜው ሹዋሚውን ጥቁር ድንጋይ የሚያሸክም ነው ። ላልተማረ ሰው ሥልጣን መስጠት ለእብድ ሰይፍ መስጠት ነው እንዲሉ ።
መስፈርት የሌለው አገር ፣ መስፈርት የሌለው ቤተ ክርስቲያን ፣ መስፈርት የሌለው ማኅበረሰብ አስፈሪ ነው ። መስፈርት ሲጠፋ ሰዎች ቦታ ተለዋውጠው ይቀመጣሉ ። መስፈርት ሲጠፋ ባለቤት ደባል ፣ ደባልም ባለቤት ይሆናል ። መስፈርት ሲጠፋ አማኝ ይወገዛል ፣ አላዋቂ ይነግሣል ። መስፈርት ሲጠፋ ያልተማሩ የተማሩትን ያርማሉ ። መስፈርት የጠፋበት ዘመን አስፈሪ ነው ። ጌታ ሆይ መስፈርት ከሌለው ዘመንና ትውልድ አድነን!
ሐዋርያው ጳውሎስ በቲቶ መልእክቱ የወቀሳቸው ሰዎች ሁሉን የሚያረክሱ ፣ ምንም እንዳይጥማቸው ሁነው የተሰለፉ ናቸው ። ሁሉን መተቸት ፣ ሁሉን ማውገዝ ፣ ሁሉን ማጣጣል መንፈሳዊ በሽታ ነው ። “ሁሉ ለንጹሖች ንጹሕ ነው ፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የሆነ ምንም የለም፥ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል።”
በቆሻሻ መስተዋት የሚያይ ሁሉም ነገር ቆሻሻ ሁኖ ይታየዋል ። ንጹሕ ባልሆነ አእምሮም የሚያስብ ሰው ለእርሱ ሁሉም ነገር የረከሰ ነው ። ይህ ሰው የሚያስፈልገው አካባቢውን ማስተካከል ሳይሆን የሚያይበትን መስተዋት ማጽዳት ነው ። ንጹሕ ላልሆኑ ሰዎች ፍቅር ማስመሰል ፣ ቸርነት ውደዱኝ ማለት ነው ። ንጹሕ ልብ ያላቸው ሁሉን ንጹሕ አድርገው ያያሉ ። አንድ ወዳጄ “ዛሬ አምሮብሃል” ስለው “በቀና ዓይንህ ስላየኸኝ ነው” ይላል ። የቀና ዓይን ካጣን ያማሩት ያስጠሉ ይመስለናል ። “የተማረ ሁሉን ይቀደስ ፣ ያልተማረ ሁሉን ያረክስ” ይባላል ።
ጌታ ሆይ ንጹሕ አድርገኝና ሁሉም ንጹሕ ሁኖ ይታየኝ ። ሰይጣን ሁሉን አርክሶብን ሁሉም ነገር ያጠራጥረናል ። እባክህን የማየውን ሳይሆን የማይበትን ልብ ንጹሕ አድርግልኝ ። በደጉ ስምህ አሜን ።
የሰማይ ድምፅ 2
ሐምሌ 26 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም