የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ያመነ አይፈረድበትም

“ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና። በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል”
                                             /ዮሐ. 3፡17-18/።
የእግዚአብሔር ቃል በእያንዳንዱ ቊጥር ላይ አብረቅራቂ አልማዝ ነው። እጅግ ረቂቅ ነው ። ታሪኩም ፣ ፍልስፍናውም ፣ ሥነ ልቡናውም ቅዱስ ነው ። የእግዚአብሔር ቃል ሰፈፍ የሌለው ወለላ ፣ ገለባ የሌለው ፍሬ ፣ ግርድ የሌለው ምርት ፣ ነቊጥ የሌለው ጽሩይ ነው ። ከእግዚአብሔር ቃል የምንጥለው ምንም ነገር የለም ። ምግብ አንዳንድ ጊዜ በልተነው ይጣላናል ። ወደነው ብንበላውም ሕመም ይሆንብናል ። የእግዚአብሔር ቃል ግን ልንጣላው እንጂ ሊጣላን አይችልም ። የእግዚአብሔር ቃል መልክአ ሥላሴ ነው ፣ የአግዚአብሔርን መልክ የሚያሳየን ነው ። እግዚአብሔር ማለት እኛ እንዲሆንልን የፈለግነው ሳይሆን ራሱ ራሱን የሆነው እግዚአብሔር ነው ። እግዚአብሔርን በቃሉ ማወቅ ቀዳሚው ነገር ነው ። የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነውና ሰው ማወቁ የሚታወቀው ፈሪሃ እግዚአብሔር ሲኖረው ነው ። ከዚህ ቅዱስ ፍርሃት ውስጥ ፍቅር ይመነጫል ። ከዚህ ፍቅር ውስጥም እምነት ይመጣል ። ስለዚህ ሰው በመጣ ቀን አያምንም ማለት ነው። በመጣ ቀን ግማሹ ጓደኛውን ግማሹ እጮኛውን ፈልጎ የመጣ ነው ። ሳኦል አህያ ፈልጎ መጥቶ ንግሥና ይዞ እንደ ተመለሰ ሰውና ቊሳቊስ ፈልጎ የመጣም እግዚአብሔርን ይዞ ይመለሳል ። ስለዚህ በቤቱ የሚቀበለን ማመናችን ሳይሆን እግዚአብሔር ታማኝ መሆኑ ነው ። የእኛ ፍቅር አንዳንዶችን የሚመለከት ነው ። የእግዚአብሔር ፍቅር ግን ዓለሙን በሙሉ አድራሻ ያደረገ ነው ።
መዳናችን ትልቅ ዋጋ የተከፈለበት ነው ። የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ የሆነበት፣ የውርደት ሞት ለእኛ የሞተበት ነው ። ብዙ የምናከብራቸው የነጻነትና የድል ታሪኮች አሉ ፣ የክርስቶስ ሞት ከእነዚህ እንዳያንስብን መጠንቀቅ ያስፈልገናል ።
በእርሱ የሚያምኑ የዘላለም ሕይወት እንደሚያገኙ ተነግሯል ። የዘላለም ሕይወት የመጨረሻው ስጦታ ነው ። እግዚአብሔር የተወዳጀን የመጨረሻውን ሰጥቶን ነው ። የሰው ፍቅር አዳጊ በመሆኑ የክርስቶስ ፍቅር ሊያስደነግጠው ይችላል ።  የዘላለም ሕይወት ማለት ዘላለም መቆየት ብቻ ሳይሆን ሞት የማያሸንፈው ህልውና ማግኘት ነው ። የዘላለም ሕይወት የሞትና የሲኦልን ኃይል የሚሽር ነው ። ዛሬ ከመሬት ባሻገር ስላሉ ነገሮች አሰሳ ይደረጋል ። ከሞት ባሻገር ስላለው ማንም አያጠናም ። ያ ክርስቶስን በማመን የሚገኝ ነው ።
–    ሁሉም ስለ ተራራው ይናገራል ።
–    ባለ ራእይ ከተራራው ጀርባ ስላለው መስክ ይናገራል።
–    ከሞት ጀርባ ስላለው ክርስቶስ ብቻ ተስፋ ይሰጣል ።
 ሩጫ ስንጀምር ከጀመርንበት ተቆጥሮ በፍጻሜው እንሸለማለን ። የዘላለም ሕይወትም ካመንበት ቀን አንሥቶ የሚጀምር ነው ። የዘላለም ሕይወት ግን የሩጫው መጨረሻ ሽልማት ሳይሆን የሩጫው ማስጀመሪያ ኃይል ነው ። የዘላለም ሕይወት የዘላለም ፍቅር ፣ የዘላለም ኅብረት ማለት ነው ። ወደ ሰማይ ከመሄዳችን በፊት ሰማይ ወደ ሕይወታችን መምጣት አለባት ። በሰማይ የሚቀጥል እንጂ የሚጀምር ነገር የለም ። የሰማይ ግብዣችን ዛሬ የምንካፈለው ፍቅርና ኅብረት ነው ። ነገር ግን ፍቅሩም ሆነ ኅብረቱም ፍጹም አይደለም ። ፍጹም አለመሆኑ ሰማይን እንድንናፍቅ ያደርገናል ። ፍጹም ነገር በዓለም ላይ የለም ። ፍጹም ነገር ብናገኝ እንኳ እኛ አባል ስንሆንበት ፍጹምነቱ ያበቃል ። ምክንያቱም እኛ ራሳችን ጎዶሎዎች ነንና ። ያለ ዘላለም ሕይወት ተስፋ ክርስትና አይጀመርም። ብዙ ቃል ኪዳኖች ቢኖሩም አዲስ ኪዳን ግን ከሁሉ ይበልጣል። ምክንያቱም የዘላለም ሕይወትን ይሰጣልና።
 ክርስቶስ የመጣው እንዳንጠፋ ነው ። መጥፋት መደምሰስ አይደለም ። ኵነኔ ማለትም ተፈጥሮ እንዳልተፈጠረ መሆን ማለት አይደለም ። መጥፋት ከባለቤቱ እጅ ወጥቶ በሌባ እጅ መውደቅ ነው ። ዛሬ ገንዘብ ቢሰረቅብን ለእኛ የወር ወጪ ሲሆን ለሌባው ግን የቀን ወጪ ነው ። ባለቤት አይደለምና ያድፋፋዋል ። መጥፋት ማለት በጠላት እጅ መድፋፋት ነው ። ክርስቶስ ግን የመጣው ለዘላለም እንድንበረክት ነው ። ሰዎች ስጦታ ሲሰጡን ስጦታነቱ ለእኛ ሲሆን ክፍያው ግን ለእነርሱ ሆኖ ነው ። ማንኛውም ነጻ ስጦታ እዚያ ጋ ክፍያ አለው ። እግዚአብሔርም የዘላለም ሕይወትን ሲሰጠን ፍቅሩን ከፍሎበት ነው ። የዘላለም ጌታ የሞተው የዘላለም ሕይወትን ሊሰጠን ነው ። አንድ በሞት አፋፍ ላይ ያለ ሰው ቢድን እንደነቃለን፣ መሞት የሚገባው በመዳኑ ሐኪሞች ሳይቀር ከእውቀታችን በላይ ነው ይላሉ ። መሞት የሚገባው መዳኑ ሲያስደንቅ መሞት የማይገባው ክርስቶስ መሞቱ ግን ከሁሉ በላይ ያስገርማል ። እኛ ለቤት ሠራተኛችን ደም ለመለገስ እንኳ ፈቃደኛ አይደለንም ። እንኳን ልጃችንን የልጃችንን ልብስ መስጠት አንሻም ። እኛ ለበደለን ሰው የምናደርግለት የመጨረሻው ደግነት ህልውናውን መርሳት ነው። ጌታ ግን ለበደለው ሰው ሞተ ። በፍቅሩ ፊት ፍቅራችን ወራዳ ነው ። በሞቱ ያገለገለንን በጊዜያችን ማገልገል አቅቶናል ። በደሙ ሰላም የሰጠንን ጌታ ዛሬ ቤቱን በነገር እናምስበታለን ። እግዚአብሔር አብ ሕያው ቃሉን ወይም ልጁን እስከ ዛሬ ሙት የሚል ትእዛዝ አልሰጠውም ነበር ። ቃለ አብ ኢየሱስ ለልዩ ትእዛዝ ታዘዘ ። የላከ አብ ቡሩክ ነው ፣ የተላከም ወልድ ቡሩክ ነው ፣ ያሰመረ መንፈስ ቅዱስም ቡሩክ ነው ።
 አንድ ልጅ እንኳን ለሞት ለማየትም ያሳሳል ። እግዚአብሔር ግን ልጁን ለሞት አሳልፎ ሰጠ ። ከባዱ ነገር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ መሞቱ እንጂ እኛ ስለ እርሱ መዳናችን አይደለም ። መንግሥተ ሰማያትን ቢቸረን ታላቅ ባለጠጋ ስለሆነ ነው ። ልጁን ቢሰጠን ግን እግዚአብሔር ፍቅር ስለሆነ ነው ። ተራራ ከሩቅ ይታያል ፣ ሥሩ ስንቆም ግን አይታይም ። ዛሬ በእግዚአብሔር ቤት ስላለን ያገኘነው ከፍታና ጸጋ አይታየንም ይሆናል ። ሌሎች ግን ከሩቅ ያዩታል ። አንድን ሰው ልባችንን ካልሰጠነው ቊልፋችንን አንሰጠውም ። የሚበልጠውን ልብ ካገኘ በኋላ የሚያንሰውን ቊልፍ ያገኛል። እግዚአብሔርም ከሁሉ በላይ የሚሆነውን አንዱን ልጁን ሰጠን ። የልቡን መልእክተኛ ልጁን የሰጠ ጸጋውንና መንግሥቱን እንደሚሰጥ እርግጥ ነው ። እምነት በእግዚአብሔር መደላደል ነው ። ለዘላለሙ ያመነውን እግዚአብሔር ለጊዜያዊ ጉዳይ እንዴት እንፈራዋለን? ማመን ቀላል አይደለም ፤ ላመነ ሥራ ቀላል ነው ። እምነት በሌለን ነገር ማረፍ ሲሆን ምግባር ደግሞ ባለን ነገር መሥራት ነው ። ብዙ የምንወደው ሰው ሊኖር ይችላል ፣ የምናምነው ግን ጥቂት ነው ። ማመን በእኛ ፍቅር ብቻ ሳይሆን ሌሎች ለእኛ ባላቸው ፍቅርም እርግጠኛ መሆን ነው ። ይህንን መታመን ሊሸከም የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው ።
“ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና። በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል” ይላል /ዮሐ. 3፡17-18/። ባሉበት ቦታ የሚወረወር ቀስት እርሱ ፍርድ ነው ። ሰውዬው ካለበት ድረስ የሚሄድ ግን ፍቅር ነው ። ሰውዬው በሌለበት ፍርዱ ይታያል። ፍቅር ግን ሰውዬውን ማግኘት ይፈልጋል ። ለፍርድ ዙፋን ሲያስፈልግ ፣ ለፍቅር ግን በረትና መስቀል አስፈላጊ ሆነ ። እግዚአብሔር ዓለሙን ሁሉ ሊቀጣ ቢፈልግ በዙፋን ልዕልናው ሆኖ መቅጣት ይችል ነበር ። የበረት ትሕትናው ግን ለመዳን የተከፈለ ዋጋ ነው ። ልዕልና ይፈርዳል ፣ ትሕትና ግን ከውድቀት ሥር ገብቶ የጠለቀውን ሰው ያድናል ። አንድ በውኃ ውስጥ የሰጠመን ሰው ለማዳን እርሱ ባለበት ውድቀት ልክ መሆን አይበቃል ። ከእርሱ ውድቀት በታች መሆን ያስፈልጋል ። እግዚአብሔር ወልድም ያለ ልክ ተዋረደ ። እግዚአብሔር ዓለሙን ቢፈርድበት ሕጋዊ ነበር፣ ዓለሙን በማዳኑ ግን መሐሪ ነው ። እኛም ባሕርዩን ተካፍለናልና ፍቅርም ፍርድም አለን ። ሁለቱም ያለው እግዚአብሔር ግን ፍቅርን አስቀደመ ። ፍርድን በሚመለከት እግዚአብሔር የሚርቀው ግዛት የለም ። የጌታችን ዓላማ ግን መፍረድ ሳይሆን ማዳን ነው ። እግዚአብሔር የመፍረድ ሥልጣኑን ቢጠቀም መላው ዓለም እስር ቤት ፣ መላው የሰው ዘር እስረኛ ይሆን ነበር ። አሳሪው ሁሉ አብሮ ታሳሪ ፣ ፈራጁ ሁሉ ራሱ ፍርደኛ ይሆን ነበር ። ማዳን የእግዚአብሔር ነው ። በእግዚአብሔርነት ሥልጣን የሚፈጸም ነው ። ማዳን ትልቅ ተግባር ነው ። በእውነት እግዚአብሔር እስር ቤቶችን ሲያይ ምን ይል ይሆን ? በእርሱ ቅድስና ፊት የማይታሰር የለምና ። አዎ ማዳን ሰውዬው ያለበት ድረስ መሄድን ይጠይቃል ፣ መደበኛ በሽታዎች በሐኪም ቤት ይታከማሉ ፣ ወረርሽኝ ግን በሽተኞቹ ያሉበት ድረስ መሄድ ይፈልጋል ። አዳምንና ዘሩን የበከለውን የኃጢአት ወረርሽኝ ለማዳን ራሱ ሐኪም ራሱም መድኃኒት ሁኖ ጌታችን መጣ ።
አዎ ጌታችን የመዳን ጽኑ ምክንያት እንደሆነ ሁሉ የኵነኔም ጽኑ ምክንያት ነው። ወይ ጥያቄአችን ወይ መልሳችን ነው ። ከእርሱ ጋር በምሕረት ካልተገናኘን በፍርድ መገናኘታችን ግድ ነው ። በእርሱ የሚያምን ግን አይፈረድበትም ። ሲያምን ዕዳው የተከፈለበትን ደረሰኝ ስለሚቀበል ነው። ጌታችን ጋ ስንመጣ ስለ ኃጢአታችን ይጠየቅልናል ፣ ራሳችን ጋ ስንሆን በኃጢአታችን እንጠየቃለን ። እምነት ማለት ከኃጢአቴ ይልቅ ማመኔ ያስመልጠኛል ብሎ መተማመን ነው ። ማንም ሊያስውል ይችላል ፣ ሁሉም ግን አያሳድርም ። በቀን የሚያምኑትን በጨለማ አያምኑትም ። ከቤት የተጣላ ልጅ ቀን ላይ ረስቶት ይውልና ሲመሽ ግን መጨነቅ ይጀምራል ። ታዲያ የእናቱና የአባቱ ጽኑ ወዳጅ የሆኑት ሰው ደጅ ላይ ያንዣብባል ። እነርሱም ምን ሆነሃል? ብለው ይጠይቃሉ ። ልጁም መጣላቱንና ለመመለስ ድፍረት ማጣቱን ከገለጠ በኋላ ይዘውት ወደ ወጣበት ቤቱ ይመጣሉ ። ታዲያ እኒያ አስታራቂ እናት ልጁን ከኋላ በቀሚሳቸው ከልለው ለቊጣው ራሳቸውን አሳልፈው ሰጥተው ይገባሉ ። የተበሳጨው ወላጅም ብዙ ቊጣውን ያወርዳል። ሲጨርስ አስታራቂዋ እናት “ስለ እኔ ብላችሁ ተቀበሉት ፣ በሞቴ ፣ እኔ እክሳለሁ” ብለው ይማለላሉ ። ስለ ማንነቱ ሳይሆን ስለቀደመለት ወዳጅ ያ ልጅ ይመለሳል። ኢየሱስም ቀን የጨለመብንን የእኛን ቊጣ ተሸክሞ እኛን በጽድቅ ከልሎ አስገባን ። ያ ልጅ ከወላጁ ቅጣት ይዞት በመጣው ሰው ምሕረት ያምናል ። ማመን ቀላል ሳይሆን ብርቱና አስደሳች ነገር ነው ። ታዲያ እኒያ ቊጣችንን የተሸከሙልን እናት ከእናታችን በክብር የሚያንሱ አይደሉም ። እኩያ ናቸው ። ኢየሱስም ቊጣችንን በመሸከሙ ከአባቱ አያንስም እንደውም እኩያ ነው ። እኩያ ባይሆን ሕርቁም ባልተገኘ ነበር ።
በእርሱ የማያምን አሁን ተፈርዶበታል ይላል ። የሚያምን ደግሞ አሁን ከኵነኔ ድኗል ። ጳውሎስ ሐዋርያ ፡- “እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኵነኔ የለባቸውም” ይላል /ሮሜ . 8፡1/። በጌታ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ እንደ ሰው ሁሉ የእኔ ዕጣ የሚለው በምጽአት ቀን ነው ብሎ ያስብ ነበር ። ስለዚህ ፡- “ጌታ ሆይ፥ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ አለው። ኢየሱስም፦ እውነት እልሃለሁ፥ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ አለው” /ሉቃ .23፡42-43/። ጌታችን አርሞ ሰማው ። እምነት አሁን ነው ።
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ