የትምህርቱ ርዕስ | ሁሉን ይነግረናል

“ሴቲቱ፡- ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል አለችው ። ኢየሱስ፦ የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ አላት” /ዮሐ. 4፥25/ ።
በዕብራይስጥ ፣ በአራማይክ ፣ በዐረቢኛ መሢሕ ሲባል በግሪክ ደግሞ ክርስቶስ ይባላል ። ትርጉሙ የተቀባ ወይም የከበረ ማለት ነው ። ይህን ስያሜ ያገኙ የነበሩ እስራኤልን በዙሪያቸው ካሉ ጠላቶች የሚታደጉ ነጻ አውጪዎች ሲሆኑ በቅዱስ ዘይት የከበሩ ነቢያት ፣ ነገሥታትና ካህናትም እንደ መሢሓውያን ይታዩ ነበር ። እስራኤል ሁሉ ይጠብቁት የነበረው አንድ መሢሕ ግን አለ ። እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። ነገር ግን በተስፋ የናፈቁትን ፣ በትንቢት ያከበሩትን ፣ በሱባዔ ያሰሱትን ክርስቶስ በመጣ ጊዜ አልተቀበሉትም ። ምክንያቱ ምንድነው ? ስንል ይጠብቁት የነበረው ከምድራውያን ጠላቶቻችን ተዋግቶ ነጻ ያወጣናል ። ዙፋኑንም በኢየሩሳሌም አጽንቶ ያከብረናል ብለው ነው ። እንደ ጠበቁት ስላልተገለጠ ሊቀበሉት አልቻሉም ። ክርስቶስ ምድራዊ መንግሥትን ይይዛል የሚል አሳብ በደቀ መዛሙርቱ ልብ እስከ ዕርገቱ ቀን ድረስ ነበረ /የሐዋ. 1፥6/ ። በመካከላቸውም የነበረው ክርክር በዚያች መንግሥት ከፍተኛው ሹመት ለማን ይሰጣል ? የሚል ነበረ ። ይህንን ምኞታቸውን ያምኑትና እርስ በርሳቸው ይጣላሉ ። ጌታችን ኅብስት አበርክቶ ሺህዎችን በመገበ ጊዜም ሊያነግሡት ፈልገው ነበረ /ዮሐ. 6፥15/ ። ሆሳዕና በአርያም እያሉ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ያጀቡት ከፊት ለፊቱ መስቀል እንዳለበት አልተገነዘቡም ። በዚህ ምክንያት ሊቀበሉት አልተቻላቸውም ።
ሐዋርያት በስብከታቸው ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ መሆኑን ይናገሩ ነበር /የሐዋ. 5፥42/ ። ሌላ አትጠብቁ ነጻ አውጪው መጥቷል ማለታቸው ነው ። አይሁድ ኢየሱስ መባሉን ተቀብለዋል ። ክርስቶስ መባሉን ግን አልተቀበሉም ። ክርስቶስ መዐርግንና ትንቢት ፈጻሚነትን የሚያመለክት ስም እንደሆነ ያውቃሉ ። ሐዋርያት በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያጠምቁ እንደ ነበር ተጽፏል /የሐዋ. 10፥48/ ። የጥምቀት ትእዛዙ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው /ማቴ. 28፥20/ ። እነርሱ ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያጠምቁ የነበረው አይሁድ አንዱን አምላክ በአርያም ያለውን አብን መቀበል አልቸገራቸውም ። ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ መሆኑን ማመን ግን ከብዷቸው ነበር ። ጥምቀትም በክርስቶስ ካላመኑ ጥቅም የለውም ። ምክንያቱም ከእርሱ ሞትና ትንሣኤ ጋር መተባበር ነውና ። ስለዚህ በክርስቶስ ማመናቸውን ለማስረገጥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያጠምቁ ነበር ። አንዳንድ ጊዜም አጥማቂው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሲል ተጠማቂው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እያለ ይጠመቃል ።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው ከኃጢአትና ከሞት ባርነት ነጻ ሊያወጣን ነው ። ከኃጢአትና ከሞት ባርነት ነጻ ሊያወጣ የከጀለ ብርቱ ማንም አልነበረም ። ሁሉ በኃጢአትና በሞት ተይዞ ነበርና ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ከኃጢአት ሊያድነን መጣ ። በምድር ላይ ያሉ ጠበብቶች ቢሰባሰቡ ኃጢአትን ማከም አይችሉም ። የኃጢአትንም ዋጋ መክፈል አይቻላቸውም ። ጌታችን ግን ከኃጢአታችን ያዳነን መሢሕ ነው ። የኃጢአትን አስከፊነት ስናውቅ የእርሱ አዳኝነት ምን እንደሆነ ይገባናል ። እግዚአብሔር የኃጢአትን አስከፊነት የገለጠው መስቀል ላይ ነው ። አንድ ልጁ ለሞት ተላልፎ መሰጠቱ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ያለው የፍቅር መግለጫ ነው ። ይህ ብቻም አይደለም ለኃጢአት ያለው የመረረ ጥላቻም ነው ። በየትኛውም ዘመን ኃጢአተኞችና እግዚአብሔር ይታረቃሉ ። ኃጢአትና እግዚአብሔር ግን አይታረቁም ። ጥንትም አሁንም ወደፊትም ኃጢአት ኃጢአት ነው ። ሐዋርያው ፡- “ለገዛ ልጁ ያልራራለት ነገር ግን ስለ ሁላችን አሳልፎ የሰጠው ያው ከእርሱ ጋር ደግሞ ሁሉን ነገር እንዲያው እንዴት አይሰጠንም?” ይላል /ሮሜ. 8፥32/ ። እግዚአብሔር በልጁ ጨክኖ ለእኛ ራራ ። ልጁን ለሞት አሳልፎ መስጠቱ ግን በኃጢአት ላይ ያለውን ጽኑ አቋም ሊገልጥልን ነው ። ቀራንዮ የፍቅር ትርጉም ብቻ ሳይሆን የኃጢአት ትርጉም ምን እንደሆነ የምናውቅበት ነው ። ኃጢአት በጥንት ዘመን ሕግን ማፍረስ ነው ። አሁን ግን ክርስቶስን ለሞት ካበቃው ምክንያት ጋር መተባበር ነው ። ወዳጁ በተገደለበት ዕቃ ሥራ የሚሠራና የሚደሰት ማነው ? ክርስቶስ ለሞት በበቃበት ኃጢአት ኑሮን ማደላደል ደግሞም ደስታን መፈለግ አይገባም ።
ጌታችን እስራኤል እንደ ተመኙት ከሮማውያን ነጻ አውጥቶአቸው ነፍሳቸውን ግን ትቶ ቢሆንስ ? የዓለም መድኃኒት አይሆንም ነበር ። ቤዛ ኩሉ ዓለም በመሆኑ ቅኝ ገዢዎቹንም ተገዢዎቹንም ነጻ አወጣ ። በኃጢአት ባርነት ያልተያዘ የለምና ። የመግዛትና የመገዛዛትን አስተሳሰብ የሚወልደው የነፍስ ነጻ አለመውጣት ነው ። የበላይነት መንፈስ ምንጩ የበታችነት መንፈስ ነውና ። ሰው የበታችነት ሲሰማው የበላይ መሆንና ሌሎችን መግዛት ይፈልጋል። ጌታችን የቅኝ ግዛትን ሥሩን ሊቆርጥ መጣ ። ነጻ የወጣች ነፍስ ስግብግብነት ፣ ጨቋኝነት የለባትም ። በዓለም ላይ ታላላቅ ጭካኔዎችን ፈጽመው የሄዱ ሰዎች ውስጣቸው የነበረው ይህ ነጻ አለመውጣት ነው ። ጌታችን ከነፍስ ባርነት ነጻ ሊያወጣን መጣ ።
ነፍስ የጽድቅና የኰነኔ መነሻ ናት ። ሥጋ ግን ጉዳይ አስፈጻሚ ነው ። ለዚህ ነው በአዲስ ኪዳን ስለ ምኞት ስለ ቊጣ በአጠቃላይ ከውስጥ ስለሚወጡ ነገሮች የተነገረው /ማቴ. 15፥19 ፤ 5፥21 እና 28/ ። ረቂቅ ምኞት ግዙፍ ዝሙትን ፣ ረቂቅ ቊጣ ግዙፍ መግደልን ያመጣል ። ነፍስ ከሥጋ ስትለይ ቅጣቱንም ዕረፍቱንም ከሥጋ ቀድማ የምትቀበለው ዋነኛ ወሳኝ ስለሆነች ነው። በትንሣኤ ሙታን ግን ሥጋም ተባብሯልና አብሮ ሊከብር ወይም ሊቀጣ ይነሣል ። ነፍስ ትልቅ አቅም ያላት ናት ። ፍቅሯ እንኳ ኃይለኛ ነው። በነፍስ ኃይል መውደድ የሚገባን እግዚአብሔርን ነው /ማር. 12፥30/ ። ምክንያቱም ይህን ፍቅር መሸከም የሚችል እርሱ ብቻ ነው ። ሰዎችን እንደ ራሳችን መውደድ ይገባናል ። ሰዎችን በነፍስ ኃይል ስንወዳቸው እስረኛና መከረኛ እናደርጋቸዋለን ። እኛም ተንቀሳቃሽ ሬሣ እንሆናለን ። ልጆቻቸውን በጣም በመውደዳቸው ከትምህርት ቤት እስኪወጡ ትምህርት ቤት ደጃፍ ላይ የሚውሉ ወላጆች አሉ ። የትዳር አጋራቸውን በጣም በመውደዳቸው ቢሞትብኝስ እያሉ ለአእምሮ ጭንቀት የሚዳረጉ አሉ ። በነፍስ ኃይል መውደድ ሁልጊዜ የሚገኘውን እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ደግሞም ይገባዋል ።
ሳምራዊቷ ሴት የንስሐውን ጥሪ ለማስቀየስ ባቀረበችው የሃይማኖት ክርክር የአዲስ ኪዳን አምልኮ ተብራራ ። እግዚአብሔር ድንቅ ነው ። ለኒቆዲሞስ ስለ ዳግመኛ መወለድ ለዚህች ሴት ስለ አምልኮ ምልአት ነገራት። መሆን የነበረበት አምልኮ ለኒቆዲሞስ ፣ ዳግም ልደት ለሳምራዊቷ ሴት ቢነገር ነበር ። እግዚአብሔር ግን እውቀቱ ከሰው የተለየ ነው ። ኒቆዲሞስ ዘመደ እግዚአብሔር ለመሆን ከባዶ መጀመር አለበት ። ብዙ ነገር እንዳለው ያስባልና ። ይህች ሴት ምንም የላትምና ጌታችን በማራቆት አይሰብካትም ። አለሽ እያለ ተስፋ ይሰጣታል ። ለማን ምን እንደሚነገር የሚያውቀው የፈጠረን እርሱ ነው ።
መሢሑ እንደሚመጣ የተፋፋመ ወሬ ነበረ ። ይህ ወሬ በኢየሩሳሌም ብቻ ሳይሆን በሰማርያ ፣ በቤተ መቅደስ ብቻ ሳይሆን በመሸታ ቤት ይወራ ነበር ። ይህች ሴት መሢሑን የምትጠብቀው ለንግሥና አይመስልም ። እርስዋና ወዳጆቿ ከኃጢአት ነጻ ያወጣናል ብለው ይጠብቁት ነበር ። መሢሑ የመገለጥ ወይም የአስተርእዮ ፍጻሜ መሆኑን ተናገረች ። “ሴቲቱ፡- ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል አለችው ።” በእውነትም በመጀመሪያው ምጽአቱ ላይ ሁኖ የዳግም መምጣቱን ነገር ነግሮናል ። እርሱ ሁሉን ነግሮናልና አዋቂ ፍለጋ መንከራተት የለብንም። ሐዋርያው ፡- “ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን” ያለውን ሳምራዊቷ ሴት ቀድማ ተናገረች /ዕብ. 1፥1-2/ ። እግዚአብሔር በሕልም በራእይ በትንቢት ሳይሆን በአንድ ልጁ ከተናገረን ይህ የመገለጥ ዳርቻ ነው።
እስከ ክርስቶስ መምጣት ድረስ የተሰወሩ መንፈሳዊ ምሥጢራት በክርስቶስ መምጣት ተገልጠዋል ። የሥላሴ ምሥጢር ፣ ዳግም ልደት ፣ መንፈሳዊ አምልኮ በእርሱ ተብራርተዋል ። ፍጹም ትምህርት ፍጹሙን መምህር ሲጠብቅ ኑሯል ። የምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ምሥጢረ ሥጋዌ ነው ። የምሥጢረ ሥጋዌ መሠረትም ምሥጢረ ሥላሴ ነው ። ምሥጢረ ሥላሴ በክርስቶስ ተገለጠ ። ሁሉን የነገረን ጌታችን ስሙ የተመሰገነ ይሁን ። የሁሉ መሠረት ስለሆነው ሥላሴነት የነገረን በሁሉ የተመሰገነው እርሱ መሢሑ ነው ፡፡
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም