የትምህርቱ ርዕስ | መለኮታዊ ምስጋና

“በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ ፤ እርሱም የርስታችን መያዣ ነው፥ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ ፥ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል።” አፌ. 1፡13-14 ።

ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ለመታተም በክርስቶስ የመዋጀት ሥራ ማመን ያስፈልጋል ። ለማመንም መስማት ግድ ነው ፣ የሚሰሙትም ቃለ እግዚአብሔርን ፣ የድኅነት ወንጌልን ነው ። መንፈስ ቅዱስ ከአብና ከወልድ ጋር እኩል የሚሰገድለት ፣ አካላዊና መለኮታዊ ነው ። ክርስትናን ከሌሎች ሃይማኖቶች ልዩ የሚያደርገው በሦስት አካላት በአንድ አምላክነት በተገለጠው እግዚአብሔር የሚያምን መሆኑ ነው ። በሦስት አካላት ተገለጠ ስንል እንደ አሕዛብ ብዙ አማልክትን እያነሣን አይደለም ። በአንድ አምላክነት ተገለጠ ስንልም እንደ አይሁድና እስልምና አንድ ገጽ እያልን አይደለም ። ሦስቱ አካላት በመለኮት አንድ ሁነው ለዘላለም ይኖራሉ ። ይህንንም በክርስትና ተቀበልነው እንጂ አልፈለሰፍነውም ።

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የአብና የወልድ ሕይወታቸው ፣ የፍጥረታትም የመገኘታቸውና የመንቀሳቀሳቸው ኃይል ነው ። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን መለኮታዊነት የሌለው ፍጡር የሚል እሳቤን እንደ አርዮስ ፣ አካል የሌለው ህፁፅ የሚል ኑፋቄን እንደ መቅዶንዮስ የሚያራምዱ መናፍቃንን ቤተ ክርስቲያን ታወግዛለች ። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አበውን በተስፋ ያስደሰተ ፣ ለነቢያት በትንቢት መነጽር የሺህ ዓመትን ክስተት የገለጠ ነው ። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በተፈጥሮ ክህሎት ተብሎ የሚጠራውን ጥበብ የሚሰጥ ፣ ለአማንያንም የአገልግሎት ጸጋን የሚናኝ ነው ። ስጦታው ብዙ ፣ መዝገበ ሙሉ ፣ ሀብቱ የማይጎድል ፣ የባሕርይ አምላክ ነው ። ከአብና ከወልድ ጋር የኖረው በጥገኝነት ሳይሆን በእኩያነት ፣ በዘመንም ሳያንስ በአቻነት ነው ። በክንድ ውስጥ ያለ ኃይል የራሱ አካል እንደሌለው እንዲሁም መንፈስ ቅዱስ ኃይል ነው ሲባል የራሱ አካል የለውም ማለት አይደለም ። በአካል ልዩ ሁኖ በመለኮት ግን ከአብና ከወልድ ጋር አንድ ነው ። መንፈስ ቅዱስ ለሥጋና ለነፍስ ሕይወትና ፈውስ የሚሰጥ ነው ። ሁከትንም ገሥጾ ሰላምን ይሰጣል ፣ ልጅነትን አትሞ እስከ መንግሥተ ሰማያት ይመራል ። በጨለማ ውስጥ ብርሃንን ፣ በፍርሃት ውስጥም ተስፋን ያድላል ። በዚህም ቡሩክ መንፈስ ቅዱስ ይባላል ። ኃጢአትን ይቅር የሚል ፣ በአማካሪዎችና በካህናት አድሮ ኑዛዜን የሚሰማ አጽናኝ መንፈስ ነው ። በጭንቀት ውስጥ ለሚያልፉ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ ጽኑ ረዳታቸው ነው ።

ኃያላንን ያስቻለ መንፈስ ነው ። እነዚህ ኃያላን ዓለምን የናቁ ናቸው ። ነገሥታት ዘውድን አስቀምጠው እንዲመንኑ ፣ ጻድቃን በገዳም ፣ ሰማዕታት በደም እንዲጸኑ ያደረገ ፣ ለደናግል ንጽሕናን ፣ ለጳጳሳት የቅን ፍርድን ያስተማረ መንፈስ ነው ። ይህን ቡሩክ መንፈስ የሚያገኙ ቃለ እግዚአብሔርን ሰምተው በክርስቶስ የሚያምኑ ሁሉ ናቸው ። ሐዋርያው ይህን ቅዱስ መንፈስ የተስፋ መንፈስ ይለዋል ። በብሉይ ኪዳን ክርስቶስ ይመጣል ብሎ ተስፋ የሰጠ ነው ። ተስፋ ያረጋጋል ። በጣዖት ቤት ከመቅበዝበዝ ፣ በፍርሃትም ከመጥፋት በተስፋ ያረጋጋቸው መንፈስ ቅዱስ ነው ። በክርስቶስ አምነው ብዙ መከራ እየተቀበሉ ያሉትን የዛሬ አማኞች መንፈስ ቅዱስ ያረጋጋል ። በፍርድ ቤት ሲነገር የምንሰማው የጥፋተኝነት ውሳኔና የቅጣት ውሳኔ የሚባል አለ ። ጥፋተኛ ነው አይደለም የሚለው በጥፋተኝነት ውሳኔ ይረጋገጣል ፣ ይህን ያህል ቅጣት ይገባዋል የሚለው ደግሞ በቅጣት ውሳኔ ይበየናል ። እንዲሁም አማኙ በክርስቶስ አምኗል ተብሎ የመጀመሪያ ብይን ይሰጠዋል ። እርሱም ድኅነቱን በተስፋ ይቀበላል ። ሁለተኛው ደግሞ መዳኑን የሚወርስበት የምጽአት ውሳኔ ይጠብቃል ። እስከዚያው ድረስ ምእመናንን በተስፋ የሚያጸናቸው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው ። አንድ ሰው ጥፋተኛ ነው አይደለም ተብሎ ውሳኔ በሚሰጥበት ቀን ታላቅ ፍርሃትና ተስፋ አለ ። እንዲሁም ያመነ አሁን በድኅነት ጥላ ውስጥ ሲሆን የማያምንም አሁን በኵነኔ ውስጥ ነው ። ምጽአት በጎችና ፍየሎች የሚለዩበት እንጂ በግና ፍየል የምንሆንበት አይደለም ።

ተስፋው የተሰጠው ወይም የተስፋው የበላይ ጠባቂ እውነት የሆነው ፣ የእውነት መንፈስ ተብሎም በተጠራው በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው ። ድኅነታችን በአምላክ እንደ ተፈጸመ ፣ ተስፋችንም አምላክ በሆነው በመንፈስ ቅዱስ ይጠበቃል ። በአስተማማኝ እጅ ያለ በመሆኑ ደስታችን ወደር የለውም ። መንፈስ ቅዱስን ማኅተም ይለዋል ። ማኅተም ሥልጣናዊ ምልክት ነው ። ሰው ቢያውቅ ቢመራመር እንደ ደብዳቤ መጻፍ ነው ። ማኅተም ሲርፍበት ግን ያ ደብዳቤ ሥልጣን ይኖረዋል ። ማመንም ማኅተመ መንፈስ ቅዱስን የሚያስገኝ ነው ። ማኅተም ያለበት ዕቃ የተቆጠረና ለሌላ ግዳጅ የማይውል ነው ። እንዲሁም ማኅተመ መንፈስ ቅዱስ ያረፈበት ከቤተ እግዚአብሔር የማይወጣ ፣ የተቆጠረ ፣ ሲጠፋም ፈላጊና ተቆርቋሪ ያለው ነው ። መንፈስ ቅዱስ የርስታችን መያዣ ወይም ዐረቦን ነው ። ዐረቦኑን የሰጠ ሙሉውን ክፍያ እንደሚሰጥ መተማመኛ ነው ። ዐረቦኑ ዛሬ የምናገኛቸው ጸጋዎች ናቸው ። በእግዚአብሔር ቤት ያገኘነው ሰላምና ደስታም ዐረቦን ነው ። በሙላት የሚገኘው በላይኛው ማደሪያችን ነው ።

ክርስቶስ በደሙ ከሞት ግዛት ዋጀን ፣ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ከዓመፃ ግዛት ይዋጀናል ። ሁሉም የተጠሩት የሰው ልጆች እስኪመጡ ድረስ መንፈስ ቅዱስ ይጠብቃል ። ወልድም ቢያድን ፣ መንፈስ ቅዱስም ቢዋጅ ለአንዲት መለኮታዊ ምስጋና ነው ። “ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል።”

ቡሩክ እግዚአብሔር ሆይ ምስጋና ይድረስህ !

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /24

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም