መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ሰላም ለኪ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን

የትምህርቱ ርዕስ | ሰላም ለኪ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን

ደጆችሽ ለምሕረት የተከፈቱ ፣ ሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ የሚታከሙብሽ ፣ ለአማንያንና ለዐላውያን የምትማልጂ ፣ የተፈጥሮ ወዳጅ ፣ ወቅታት ሲፈራረቁ የምስጋና ርእስሽ የምታደርጊ ፤ ለዝናባት ፣ ለወንዞች የምትለምኚ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላም ለኪ !

ክርስቶስ በደሙ የገዛሽ ፣ ዐፅመ ሰማዕታት አጥር የሆነሽ ፣ በመስቀል ምጥ ተወልደሽ ፣ በመስቀል ጎዳና የምትሄጂ ፣ የተጠራሽ ፣ የተመረጥሽ አቅሌስያ ሆይ ሰላም እልሻለሁ ። በበረሃው ዓለም ላይ ጥላ ፣ ጭው ባለው ምድረ በዳ የምስጋና ድምፅ ያለሽ ፣ ሥሉስ ቅዱስን የምትቀድሺ ፣ ሥጋ ወልደ እግዚአብሔርን የምትመግቢ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላም እልሻለሁ ። በመስቀል ተወልድሽ ፣ በመስቀል አድገሽ ፣ በመስቀል የምትፈጽሚ ፣ ያለ አገርሽ ያለሽ አገር ሆይ ሰላም እልሻለሁ ። ድንበር የሌለሽ ፣ መስፈርትሽ እምነት ብቻ የሆነ ፣ ቤተ ፍርድ ሳይሆን ቤተ ምሕረት የሆንሽ ፣ የኃጢአት መቃብር ፣ የምሥጢር ዋሻ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ በዓልሽ ነውና ሰላም እልሻለሁ ።

ተመራማሪዎች ሳይሆኑ አማኞች የሚገናኙብሽ ፣ “ለምንና እንዴት” የሚል ጥያቄ የታገሠላቸው የሚዘምሩብሽ ማኅደረ መለኮት ሆይ ሰላም እልሻለሁ ። ድሆች የሚጽናኑብሽ ፣ ምስኪኖች እንጀራ የሚጠግቡብሽ ፣ አካላቸውን ያጡ ሊቅ የሚሆኑብሽ አምሳለ ኢየሩሳሌም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላም እልሻለሁ ።

ፍጹምነትን ግብ ፣ የክርስቶስን መልክ የውበት ዳርቻ አድርገው ፣ ምእመናን በመንፈስ ቅዱስ የሚኳሉብሽ የሚዋቡብሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። “ይባላል ፣ ሊሆን ይችላል” የሚሉ የጥርጥር ንግግሮች የማይሰሙብሽ ፣ ቃለ አሚን ፣ ቃለ ክርስቶስ የሚነገርብሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። መፈቀርና መፈራት ፣ መወደድና መከበር ገንዘቡ የሆነ የመድኃኔ ዓለም ሙሽራይት ሆይ እያፈቀርን የምንፈራሽ ፣ እየወደድን የምናከብርሽ አዲስ ዓለም ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። እሳቱ ዓለም ሲፈጀን የምንቀዘቅዝብሽ ፣ ወደ ባሕሩ ዓለም ለመግባትም አየር የምንስብብሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ።

ሙሴ በናባው ተራራ ላይ ምድራዊት ኢየሩሳሌምን በርቀት አይቶ ተሳለመ ፣ ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን የምናይብሽ ፣ የፀሐዩ ክርስቶስ ልጅ ፣ የጨለማ መብራት ጨረቃ ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። አንቺ አካለ ክርስቶስ ፣ አንቺ የነፍሶች መዋቅር ፣ አንቺ የሕያዋን ስብስብ ፣ አንቺ ጉባዔ ሥላሴ ፣ አንቺ ክርስቶስ በምድር ሰላምታ ይገባሻል ። ፅውዕት ኅሪት የሆንሽው በምድር ያለሽ ሰማይ ፣ በጦርነት ዘመን ቅዳሴ ያለሽ መቅደስ ፣ ግንቦችን አፍርሰሽ ድልድይ የሆንሽ ፣ ከነገድ ከቋንቋ የተዋጀሽ ፣ ሁሉ የእኔ የሚልሽ ፣ የሁሉ የሆንሽ ፣ የልብ ስፋት የተሰጠሸ ፣ የክርስቶስ ብርሃን የሚታይብሽ የእኛ ታቦር ፣ የአማንያን ጉባዔ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። መስቀል ጌጥሽ ፣ መስቀል መታወቂያሽ ፣ መስቀል ስብከትሽ ፣ መስቀል ሸክምሽ የሆነ ፣ የገደሉ ዘመን ከለላ ፣ የጨለማ ዓለም ፋና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ።

በአንድ አካልነትሽ አንዱ እረኛ ፣ አንዱ መንጋ ፤ በአንድ ሕንፃነትሽ አንዱ ሠራተኛ አንዱ ጡብ የሆኑብሽ ፤ ሁሉም ልጆችሽ በግ ፣ ሁሉም የሚከወኑ/የሚሠሩ ቤቶች የተባሉብሽ ፣ ቤተ ፍጹማን ሳይሆን ቤተ ሕሙማን ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። ባንቺ መወለድ ብዙዎች ተወልደዋል ። በተወለዱ ቀን ቋንቋ የሚያውቁ ልጆች በዓለም ላይ የሉም ። በተወለድሽ ቀን ሰባ ሁለት ቋንቋ የተናገርሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። ከኢየሩሳሌም እስከ ሰማርያ ፣ ከሰማርያ እስከ አንጾኪያ ፣ ከአንጾኪያ እስከ ምድር ዳርቻ ምስክር የሆንሽ አፈ ክርስቶስ ፣ የምእመናን አንድነት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ሰላምታ ይገባሻል ። ሙሽራው ሊመጣ ነውና ተዘጋጂ ። ሙሽራው ወደ ቤቱ ሊወስድሽ ፣ ቀጠሮው ተሰብሮ የእርሱ ልትሆኚ ነውና እንኳን ደስ ያለሽ ! በዘላለም ርስቱ ሊያሳርፍሽ በደጅ ቀርቦአል ፣ የሙሽራው ዜማ ተሰምቷልና እልል በይ ! አንቺው ዜማ አውራጅ ፣ አንቺው እልል ባይ ሆይ ፣ በሚጠላሽ ዓለም ላይ የሚወድሽ ክርስቶስ አለና ደስ ይበልሽ ! በፊልጶስ ቂሣርያ ክርስቶስ ወልደ ዋሕድ – አንድ ልጅ መሆኑ በተመሰከረበት ቃለ አሚን ላይ ተመሥርተሻልና ወጀብ ማዕበሉን አይተሸ ሰምተሸ እንዳትፈሪ ። በዓልሽ በዓሌ ነውና ሰላም እልሻለሁ !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሰኔ 21 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም