መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ቀባሪ በፈጣሪ

የትምህርቱ ርዕስ | ቀባሪ በፈጣሪ

ዮሐንስ መጥምቅ የዘወትር ተግባሩ ንስሐን መስበክ ነው ። የንስሐ ሰባኪ የሚያኖረውም የሚቀብረውም ያጣል ። ስለዚህ አገልግሎቱ በዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ ባለው በምድር በዳ ሆነ ። ሲጠማው ከዮርዳኖስ ወንዝ ይጠጣል ። ሲርበው ፍጹም ደሀ የሆኑ በረኸኞች የሚመገቡትን አንበጣና የበረሃ ማር ይበላል ። ማን ይቀብረኛል ? ብሎ ሲሰጋ ፣ ቀና ብሎ ሙሴ የሞተበትን የናባውን ተራራ ያያል ። “ቀባሪ በፈጣሪ” ብሎ ይደሰታል ። ሙሴ ሚሊየን ሕዝብ መርቷልና ሚሊየን ቀባሪ ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል ። መሪ ሲሞት ሁሉም ሊቀብር ይወጣል ። አንደኛው ወሬ ለማየት ነው ። ሁለተኛው በመደንገጥ ቀጥሎ ምን ይከሰት ይሆን ? በማለት ነው ። ሦስተኛ ክፉ እንደሆነ ተመልሶ እንዳይመጣ በመስጋት ነው ። ሙሴ ግን በቁሙ የተወቀሰ ሲሞት የተመሰገነ መሪ ነው ። ብዙ አዋቂዎችና ባለ ራእዮች “ስሞት አትቅበሩኝ” ይሉናል ። ሰውን በቁም አሳቡን መረዳትና ማገዝ ከመቅበር በላይ ነው ። የእግዚአብሔር ሰዎች ለኑሮአቸው እንጂ ለቀብራቸው አልተጨነቁም ። በቀብሩ ድምቀት የተነሣ ሟች ታውቃላችሁ ? አብዛኛው ቀብር አያሌ ሰዎች የሚተዉኑበት መድረክ ነው ። ለሙሴ መርዶ ሚሊየን ሕዝብ ሠላሳ ቀናት አልቅሶለታል ። ሙሴ ግን አንድም ሰው ያልቀበረው ፣ መላእክት ሥጋውን በክብር ያሳረፉት መሪ ነው ። ለቀብራቸው ሥነ ሥርዓት ለሚጨነቁ ሰዎች ትልቅ ትምህርት ነው ።

የሙሴ መቃብር ሰይጣንም አላወቀውም ። አዋቂ የሚመስለን ሰይጣን በፍጡርነቱ እውቀቱ ውስን ነው። የጌታ ሞት ለእርሱ ዘላለማዊ ሽንፈት መሆኑን ቢያውቅ ኖሮ እንዳይሞት ይንከባከበው ነበር ። የሙሴ መቃብር ስለተሰወረበት ቅዱስ ሚካኤልን ለመጠየቅ ሞክሯል (ይሁዳ ቍ. 9) ። ሰይጣን እንኳን ወድቆ ጥንትም መልአክ ሆኖ ሳለ እውቀቱና ኃይሉ ውስን ነው ። ፈሪሀ እግዚአብሔር ሳይሆን ፈሪሀ ሰይጣንን የሚሰብኩ ፣ ለሁሉም ነገር ሰይጣን ነው የሚሉ ሊያስተውሉ ይገባል ። ኃይል የእግዚአብሔር ነው !

ባሕታዊው ዮሐንስ በምድረ በዳ የሚጮኸው ሰው ድምፅ ፣ በመላው እስራኤል ተሰማ ። ዓለምን ፣ ዓለምን በመናቅ ማስጨነቅ ይቻላል ። ዓለም የሚያከብራትን ትንቃለች ፣ የሚንቃትን ትፈራለች ። ከገሊላ እስከ ይሁዳ ፣ ከገበሬ እስከ ዓሣ አጥማጅ ፣ ከጨዋ እስከ ካህን ፣ ከንጉሥ እስከ ወታደር ሁሉም ድምፁን ሰማ ። በቤቱም ፣ በእልፍኙም ፣ በመድረኩም ፣ በቤተ መንግሥቱም ፣ በባሕሩም በየብሱም ተረጋግቶ መቀመጥ አልቻልም ። ጦር ሳይዝ ጦር የያዙትን ያስጨነቀው ባሕታዊው ዮሐንስ መጥምቅ ነው ። አትሮኖንስ ከጨበጡት ፣ በሐር በተጨበጨበ መቅደስ ከሚያገለግሉት ይልቅ በምድረ በዳ የሚጮኸው ሰው ድምፅ ኃይል ነበረው ። ቃሉ ምቾት የማይሰጥ ነው ። የእግዚአብሔር ቃል በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ነው ። ዮሐንስም እንደ ቃሉ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ፣ በሽንገላ ለመያዝ የማይመች ሰው ነበር ። “እግዚአብሔርን የምትወድዱ ምእመናን ….” እየተባሉ በሽንገላ የኖሩ ሰዎች ፣ ኃጢአት ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ጦርነት መግጠም መሆን ተረዱ ። መስተዋት ቆሻሻን ስላሳየ አይሰብሩትም ። ዮሐንስን ግን ሰበሩት ።

የተሰበሩት ሁሉ ምናልባት ቆሻሻን ስላሳዩ ሊሆን ይችላል ። መስተዋትን ያመሰግኑታል እንጂ አይሰብሩትም ።

ወደ ዮሐንስ ዘንድ ለመሄድ እመቤታችን አላስፈለጋትም ፣ ንጽሕት ናትና ። ዮሐንስ መጥምቅ ዘመድዋ ቢሆንም እንዴት እንዳደገና የት እንደ ኖረ ልትጠይቅም አልሄደችም ። እርስዋ የተባረከች ፣ ሁሉንም በልብዋ የምትጠብቅ ናት ። በናዝሬት መኖሪያዋ የዮሐንስ መጥምቅን ዝና ሰምታለች ። ልጇ ኢየሱስ የዮሴፍን የአናጢ ሱቅ ከፍቶ እየሠራ ፣ እባክህን ወንበሩን ፣ ጠረጴዛውን አድርስልን እያሉ እየጠየቁት ሳለ የዮሐንስን ዝና እንደ አላዋቂ አድርገው ነገሩት ። እርሱም ዘመኑ እንደ ደረሰ አውቋልና ሱቁን ዘግቶ ፣ እናቱን ተሰናብቶ ዓለሙን በሙሉ ሊያገለግል ወጣ ። ንስሐ የሌለበት ወደ ንስሐ ሰባኪው ሄደ ። ንጹሕ ቢሆንም የዮሐንስን ተግሣጽ ቆሞ ሰማ እንጂ እኔን አይመለከተኝም አላለም ። ንጹሕ ብትሆኑም ተግሣጽ አትናቁ ሲለን ነው ።

በዓለ ጥምቀቱን ስናከብር ወጣቶች በበዓሉ ላይ የዝሙት ማስታወቂያ ፣ የአደባባይ ነውር ሲሠሩ ለንስሐ ማብቃት አለብን ። በቅዱሱ ቀን እንዳይረክሱ መገሠጽ ያስፈልገናል ።

ይቀጥላል

#ዲያቆን #አሸናፊ #መኰንን
ጥር 20 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም