መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ቅዱስ ቂርቆስ ሰማዕት

የትምህርቱ ርዕስ | ቅዱስ ቂርቆስ ሰማዕት

“እኔ ክርስቲያን ነኝ”

በኢትዮጵያ ፣ በቢዛንታየን ፣ በካቶሊክና በኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት የታወቁና ክብር የሚሰጣቸው ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣ በዚህ ቀን ይታሰባሉ ፤ እነዚህ የ4ኛው ክፍለ ዘመን ሰማዕታት በጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ትልቅ አርአያ ተደርገው ይወሰዳሉ ። ሕፃኑ ቂርቆስም ሠለስቱ ደቂቅን/ሦስቱን ወጣቶች የሚያስታውስ ሐዲስ ሰማዕት ነው ። ቅድስት ኢየሉጣ እግዚአብሔርን በመፍራት የኖረች ሴት ናት ። እግዚአብሔርን መፍራትዋ ከሰማይ ክብርን ሲያስገኝላት በምድር ግን ስደትን አምጥቶባታል ። እርስዋም ዋጋን ከምድር ሳትጠብቅ ከሞቀው ኑሮዋ ከሮም ከተማ ተሰደደች ። በስሜ ትሰደዳላችሁ ያለው ጌታ ቃሉ በእርስዋና በቤተሰብዋ ላይ ሲፈጸም በማየትዋ ዕድለኛ ነኝ ብላ ተደሰተች ። የቅዱሳን ደስታቸው መንገዱ አልጋ ባልጋ መሆኑ ሳይሆን ቃሉ በኑሮአቸው ተዳሳሽ ሲሆን በማየት የሚገኝ ነው ። ሰው ገድለው በሚሸሹበት ዓለም ስለ ክርስቶስ ስደተኛ መሆን ትልቅ ሐሤትን የሚሞላባቸው እውነት ነው ። ስለ እኔ ትሰደዳላችሁ ያለው ጌታ ቃሉ እውነት የሚሆነው በክርስቲያንነት ሲሰደዱ ብቻ ነው ። ስደት ከተማችንን አገራችንን ልቀቁ የሚል የክፋት አዋጅ ነው ። ጌታ ክርስቶስ ፣ ቤት ብቻ ሳይሆን አገርንም የሚለቁለት ፣ አገርን ቢከስሩም አሁንም ትልቅ ማትረፊያ የሆነ ንጉሥ ነው ። እርሱ ክርስቶስ ቤትና የቤት ራስ ፣ አገርና ንጉሥ ነው ። በምድር ላይ ተመላልሶ ያስተማረን ምቾትን ሳይሆን ትግልን ነው ። ደግሞም ሰው በበሽታ ተበጣጥሶ በሚሞትበት ዓለም ስለ እርሱ ሰማዕት መሆን ቅዱሳን ሁሉ ሲለምኑት የኖሩት ዕድል ነው ።

ቅድስት ኢየሉጣ በተሰደደችበት አገርም መኖር አልቻለችም ። ክርስቲያንነትዋ ሊደበቅ አልቻለም ። በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሰወር አይቻላትምና ። ጴጥሮስን ከቃሉ የተነሣ የክርስቶስ ወገን ነህ እንዳሉት ኢየሉጣንም እንዲሁ አወቅዋት ። ወደ አገረ ገዥው አምጥተው ለጣዖት እንድትሰግድ ቢጠይቋት ዓይን እያለው ለማያይ ፣ ጆሮ እያለው ለማይሰማ አልሰግድም ። የዚህን እውነት የሦስት ዓመቱ ልጄ ቂርቆስ ይንገርህ ብላ አመለከተች ። ቅድስት ኢየሉጣ ለመሰደድ የሚበቃ ቆራጥ የክርስትና አቋም ነበራት ። በገዥዎች ፊትም ለመመስከር የምታምነውን ክርስቶስ የምታውቅ ሴት ነበረች ። ደግሞም ልጅዋን ገና በሕፃንነቱ ስለ ክርስቶስ ጌትነት እየነገረች ያሳደገች ናት ። ከዚህች ቅድስት እናት የምንማረው ብዙ ነገር አለ ። ልጆችን ገና በሕፃንነት ስለ ክርስቶስ ፍቅር እያስተማሩ ማሳደግን ነው ። ልጆች ከተማሩ በኋላ ወደ ኋላ ብንል እንኳ መልሰው ያበረቱናል ። ቅዱስ ቂርቆስ እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን “አትፍሪ” እያለ ሲያበረታታት ነበር ። ልጆቻችንን ፣ ደቀ መዛሙርትን ማስተማር በደከመን ጊዜ የሚያበረታታ ለማግኘትም ነው ። በዕለተ ሆሳዕና በአፈ ሕፃናት የከበረው ጌታ በቅዱስ ቂርቆስም አንደበት ጌትነቱ ተመሰከረ ። የሰሙት ሁሉ የዕድሜውን ለጋነትና የሚናገረውን እውነት ማጨባበጥ አልቻሉም ። ቅዱስ ቂርቆስ የሚታወቅበት ንግግሩ “እኔ ክርስቲያን ነኝ” የሚለው ነው ።

ክርስቲያንነት በተራራም በሸለቆም ፣ በከፍታም በዝቅታም የሚሸፈን አይደለም ። ባላፈረብን ክርስቶስ ማፈር አይገባም ። እኛ ወደ ኋላ ብንል እግዚአብሔር ሕፃናትን ያስነሣል ። ልጆቻችንን ለክርስቶስ መኖርን ብቻ ሳይሆን መሞትንም ልናስተምራቸው ያስፈልጋል ። ክርስትና ከሰማዕትነት የተለየ አይደለምና ። ቅዱስ ቂርቆስም በመንፈስ ቅዱስ ረዳትነት ወንጌልን ሰበከ ። የሰሙት ሁሉ አመኑ ። ብርሃናዊ ፊቱንና የሕይወት ቃሉን ሰምተው “በእውነት ክርስቶስ ጌታ ነው” ብለው ሰገዱ ። አገረ ገዥውም አንዲትን ሴት አስክዳለሁ ብሎ ሕዝቡን ሁሉ ከሰረ ። የሮማ ባለሥልጣናት ቄሣሮችንና ጣዖታትን የሚያስመለኩ እንቢ ያለውንም የሚሠዉ ነበሩ ። በዚህ ምክንያት ቅዱስ ቂርቆስ በጥር 15 ቀን ሰማዕትነትን ሲቀበል በማግሥቱ ጥር 16 ቀን እናቱ ቅድስት ኢየሉጣም ሰማዕትነትን ተቀብላለች ። ሕፃኑ እናቱን በሰማዕትነት ቀደመ ። ሕፃናት በፍቅረ ኢየሱስ ካደጉ በሰማዕትነት ይቀድሙናል ። ዛሬ ላሉት ሕፃናት የምንጨነቀው ክርስቶስን እንዲያውቁ ነው ወይስ የፈረንጅ ቋንቋ እንዲያውቁ ነው ? ቅዱስ ቂርቆስን ስናስብ የሕፃናት አገልግሎት ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ሊበረታታ እንደሚገባው ነው ። በሕፃንነቱ የገባ እስከ ማታ ይቆያል ። ብንወድም ባንወድም ነገ የዛሬዎቹ ሕፃናት ናት ። ቤተ ክርስቲያን ተተኪ ሕፃናትን ማስተማር ለሰማዕትነትም ማዘጋጀት ይገባታል ። ክርስቶስ የምንኖርለት ብቻ ሳይሆን የምንሞትለትም ነው ።

በዓለ ሰማዕታት የሚዘጋጀው በረከት ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ምእመናን የሰማዕትነት ልብ ይዘው ዛሬ ገንዘብን ፣ ነገ ሰይፍን እንዲንቁ ለማድረግ ነው ። ዛሬም ሰማዕትነት በደጅ ደርሶ እያንኳኳ ነው ። ብዙዎች ቀድመውናል ። የማይቀረውን ሞት ለክርስቶስ ሰጥተው ባለ አክሊል ሆነዋል ። ቀጣይ ዘመንም ለቤተ ክርስቲያን ሜዳ ሳይሆን አቀበት ነውና ምእመናን ጣዕመ ዓለምን በመናቅ ፣ ለሰማዕትነት ክብር በመዘጋጀት ሊኖሩ ያስፈልጋል ። በቤዛነት የጀመረው ክርስትና በሰማዕትነት ይቀጥላል ። የምንሰደደው አገራችን በምድር ስላልሆነ ነው ። የማንከበረው ሰው ያለ አገሩ ስለማይከብር ነው ። ዘመነ ሰማዕታት ክርስቲያኖችን የሚያፋቅር ነው ፣ የምቾት ዘመን የሚያጣላ ነው ። በተገፋን ቍጥር ወደ ክርስቶስ እንቀርባለን ። በተገፋን ቍጥር ወደ ሰማይ እናድጋለን ። እሳቱ አፈሩን ይበላዋል ፣ ወርቁን ያወጣዋል !

ለሕፃናት ገና ከአራስ ቤት ጀምሮ ፍቅረ ኢየሱስን እየነገርን ካሳደግን የማያሳፍሩን ፣ እኛን የሚያበረታቱን ቆራጥ አማንያን ይሆናሉ ። ሰማዕታት ሁሉ ሰማዕት የሆኑት ስለ ክርስቶስ በመመስከር ነው ። ሰማዕት ማለት ትርጉሙ ምስክር ማለት ነው ። በቃልም በጽናትም የመሰከሩ ሰማዕታት ተብለው ይጠራሉ ። እኛስ ስለ ክርስቶስ ለመመስከር ፣ ብሎም ስለ እርሱ መከራ ለመቀበል ፈቃደኞች ነን ? ስለ ክርስቶስ መከራ የሚቀበሉ ስማቸው በወርቅ ቀለም ተጽፎ ይኖራል ። የዘመን አቧራ ሊሸፍናቸው በፍጹም አይችልም ። ለዚህም ይህ ቀን ምስክር ነው ። ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ የተደረገውን አትረሳም !

ከሰማዕቱ ከቅዱስ ቂርቆስ ረድኤት በረከት ያሳድርብን !

ዲያያን አሸናፊ መኮንን
ጥር 15 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም