መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » ኤፌሶን ትርጓሜ » በኤፌሶን ላሉት ቅዱሳን

የትምህርቱ ርዕስ | በኤፌሶን ላሉት ቅዱሳን

ኤፌ. 1፡1

አማኒ በክርስቶስ የፍቅር ባሕር ውስጥ ጠልቆ የሚኖር ነው ። ዓሣ ከውኃ ከተለየ ሕይወት እንደሌለው ክርስቲያንም ከክርስቶስ ተለይቶ መኖር አይችልም ። አማኝ በክርስቶስ ግንድነት ላይ የበቀለ ቅርንጫፍ ነው ። ቅርንጫፍ ከግንዱ ከተለየበት ቅጽበት ጀምሮ ይጠወልጋል ። አማኝም ከክርስቶስ ከተለየበት ሰዓት ጀምሮ ይሞታል ። ክንድ በአካል ላይ ይኖራል ። ከአካል ከተለየ ወዲያው መበላሸት ይጀምራል ። አማኝም አካል በሆነው በክርስቶስ ላይ በእምነት የተገጠመ ብልት/የአካል ክፍል/ ነው ። ከክርስቶስ ከተለየ ሕይወት ወዲያው ይለየዋል ።

እነዚህ ኤፌሶናውያን አካላዊ አድራሻቸው ኤፌሶን ሲሆን መንፈሳዊ አድራሻቸው ግን ክርስቶስ ነው ። በኤፌሶንም በክርስቶስም ላሉት ይላል ። በኤፌሶን ያሉ በክርስቶስ የሌሉ አሉ ። በክርስቶስ ያሉ በኤፌሶን የሌሉ አሉ ። በኤፌሶን ያሉ በክርስቶስ የሌሉ የእምነት ልብ ፣ የምስጋና ቃል የሌላቸው ሲሆኑ በክርስቶስ ያሉ በኤፌሶን የሌሉ ለአገራቸው ለወገናቸው ግድ የሌላቸው ቸልተኛ አማኞች ናቸው ። ኤፌሶናውያን እንደ ዜግነታቸው ምድራዊ አድራሻ አላቸው ። እንደ አማኝነታቸው ደግሞ አድራሻቸው ክርስቶስ ነው ። ስለዚህ በኤፌሶንም በክርስቶስም ላሉት ተባለ ።

በኤፌሶን ናቸውና መንግሥታቸውን ማክበር ፣ ግብር መክፈል ፣ ከጎረቤቶቻቸው ጋር በሰላም መኖር ፣ የሌሎችን ደስታና ኀዘን መካፈል አለባቸው ። በክርስቶስ ናቸውና ለእግዚአብሔር መንግሥት አሥራት በኵራቱን ማውጣት ፣ ክርስቶሳውያንን መውደድ ፣ የአማኞችን መከራ እንደ ራስ መከራ ማየት ይገባቸዋል ። ይልቁንም አማንያን አንድ አካል ናቸውና ደስታቸውም ኀዘናቸውም የጋራ ነው ።

ለሚኖሩበት ኤፌሶን ብርሃንና ጨው መሆን ይገባቸዋል ። የመልካምነት ምሳሌ ፣ ለተጨነቁት አጽናኝ ፣ ለወደቁት የትንሣኤ ምክንያት መሆን ያስፈልጋቸዋል ። በክርስቶስ ያመነ ለሚኖርበት አገር አስተዋጽኦ አለው ። ሰማይን የሰጠው እግዚአብሔር የምድር አገሩንም ሰጥቶታል ፤ የሰማይ አገሩንም የተቀበለው በምድራዊት አገሩ ላይ ሁኖ ነው ። ምድራዊት አገሩ በክርስቶስ ምክንያት ብታሳድደው እንኳ እርሱ ግን ለአገሩ ብርሃንና ጨው መሆን አለበት ። ከዚህ ዓለም እንዳይጠብቅ ዓለሙ ጨለማና ምንም ጣዕም የሌለው አልጫ ነው ተባለ ። ስለዚህም ክርስቶስ ምእመንን ብርሃንና ጨው አድርጎ ሾሞታል ። ብርሃን ጨለማን ፣ ጨው አልጫን ይለውጣል ፤ ብርሃንና ጨው ተጽእኖና ለውጥ አምጪ ናቸው ። ትንሽ ብርሃን ጨለማን ታሸንፋለች ፣ ትንሹ ጨውም ያጣፍጣል ። ቤት ብንሠራ ፣ ወርቅ ብንደረድር ያለ ብርሃን ዋጋ የለውም ። ሥጋውን ቅቤውን ብንጨምር ጨው ከሌለው ጣዕም የለውም ። ፍትሕ ያለበት ዓለም ፣ ተስፋ ያለው ኑሮ እንዲመጣ ክርስቲያኖች ተሹመዋል ። በአገር ላይ የምናያቸው ብዙ ችግሮች ክርስቲያኖች ግዴታቸውን ባለመወጣታቸው የመጡ ናቸው ። በኤፌሶን ላሉ ፣ በክርስቶስ ላሉ የሚለው “የቄሣርን ለቄሣር ፣ የእገዚአብሔርን ለእግዚአብሔር” የሚለውን ያስተውሰናል ። የቄሣርን ለቄሣር ለመስጠት መማር ፣ መሥራትና ማትረፍ ይገባል ። የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የምንሰጠውም በሮጥነው ምድራዊ ሩጫ ነው ። ቄሣር የምድሩ ገዥ ነውና ሃይማኖትን ካዱ እስካላለ ድረስ መታዘዝ ፣ እግዚአብሔርም የነፍስና የሥጋ ገዥ ነውና ያለ ገደብ ልንገዛለት ይገባናል ።

ኤፌሶን ሥጋዊ ፈንጠዝያ የሞላባት ፣ ዓለም አቀፍ ጣዖት የሚመለክባት ፣ ዝሙት ተራ ወግ የሆነባት ፣ ሰዎች በግፍ የሚወዳዱሩባት ከተማ ናት ። በኤፌሶን ግን ቅዱሳን ነበሩ ። በዓመፀኛው ዓለም መካከል ኖኅ ፣ በከነዓን ጣዖታውያን መካከል አብርሃም ፣ በሰዶም ሎጥ በቅድስና ነበሩ ። የቤተ ክህነቶቹ ሐናና ቀያፋ ክርስቶስ ላይ መስቀል ሲጭኑ ፣ የቀሬናው ስምዖን ደግሞ መስቀሉን ያግዘው ነበር ። ሔዋን በገነት ስትበድል ፣ ሙሴ በግብጽ ለእግዚአብሔር ይገዛ ነበር ። ቅዱሳን ሲል ክርስቲያኖች እያለ ነው ። ክርስቲያን ማለት ክርስቶሳውያን ማለት ነው ። ቅዱሳን ማለትም ለክርስቶስ የተለዩ ፣ በመሥዋዕትነት ፍቅር ሊከተሉት የጨከኑ ማለት ነው ። በቸርነቱ ክርስቲያን እንደ ተባልን ፣ በቸርነቱ ቅዱሳን እንባላለን ። ቅዱሳን የሚለው መጠሪያ በቅድስና ኑሮ መደገም አለበት ። በሰማይ ያሉት ቅዱሳን መላእክትና አባቶች ተጋድሎአቸውን ፈጽመው በክብር ያሉ ናቸው ። የእኛ ቅዱሳን መባላችን ግን በቅድስና ኑሮ ተደግፎ በሰማይ ማኅተም የሚያገኝ ነው ።

የኤፌሶን ትርጓሜ /3

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 25 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም