የትምህርቱ ርዕስ | ተፈውሳችኋል

“በመገረፉ ቍስል ተፈወሳችሁ ።” 1ጴጥ. 2፡25።

ቍስል የመገረፍ ውጤት ነው ። ግርፊያ አደጋ አይደለም ፣ የታቀደ ቅጣት ነው ። ግርፊያ አንድ ጊዜ የሚከናወን አይደለም ፣ የሚደጋገም ልምጥ በትር ነው ። ግርፊያ ጠል መሬትን እንደሚያረሰርስ ሕመም ውስጥ ዘልቆ እንዲሰማ የሚያደርግ ነው ። ግርፊያ ዓላማው መግደል አይደለም ፣ መከራን ማራዘም ነው ። ግርፊያ ሥልጣን ካላቸው አካላት የሚታዘዝ ነው ። ግርፊያ ገራፊው ሲገርፍ ፣ አስገራፊው ደግሞ “ድገም” እያለ የሚያዝዝበት ነው ። ጌታና ሎሌ የተስማሙበት ነው ። ግርፊያ ላይ አራት ወገኖች ይታያሉ፡- የመጀመሪያው የፈረደው ባለሥልጣን ፤ ሁለተኛው አስፈጻሚው ወታደር ፣ ሦስተኛው ተመልካቹ ሕዝብ ፤ አራተኛው ተገራፊው ናቸው ። የፈረደው ሹም ካባ ለብሶ ያዝዛል ፣ ገራፊው እጁን ሰብስቦ ፣ ልብሱን አስቀምጦ ይገርፋል ፣ ሕዝቡ በንጹሑ ስቃይ እንዲፈራ ይደረጋል ። ሕዝብም የሰጡትን የሹም ዳቦ ለመግመጥ ዝግጁ ነውና “አንድ ጥፋት ባይገኝበት እንዲህ አይቀጣም ነበር” እያለ ላሸነፈ ድጋፉን ይሰጣል ። ተገራፊው አካልም ዕርቃኑን በአደባባይ ቆሞ ይገረፋል ። ተገራፊው አካል ንጹሕ ከሆነ በፍርድ መዛባት ያዝናል ፣ ለምን በማይሉ ፍርድ አስፈጻሚዎች ጭካኔ ልቡ ይሰበራል ። በሕዝቡ መነዳትም ይገረማል ።

ግርፊያ ክብረ ነክ ነው ። ተገራፊው ልብሱን ይገፉታል ፣ ዕርቃኑን ይቆማል ። “ዓይን ይብላህ” ብለው ይጨክኑበታል ። በ “በለው” ድምፅ መንፈሱን ለማድቀቅ ያነሣሡበታል ፤ ግርፊያው ሲጀምር ቀዩ ገላ ይቀላል ፣ ጥቁሩ ይነጣል ። ሲቀጥል ቆዳው መሳሳት ፣ መሰንጠቅ ይጀምራል ። ከዚያ በኋላ ደም ይዘንባል ። ግርፊያ ሲቆም ቍስሉ ይፋፋማል ። ለሰዓታትና ለሳምንታት ጥዝጣዜው ያሰቃያል ።

ልብሰ መንግሥቱን ተገፍፎ ስለ ተገረፈ ንጉሥ አልሰማን ይሆናል ። ብንሰማና ብናይም በዚህች ዓለም እጅግ እናዝንባታለን ። የራሳችን መጨረሻም ያሳዝነናል ። ጨካኝ ንጉሥ ሲዋረድ ብናይ ፡-

አንተም ጨካኝ ነበርህ ጨካኝ አዘዘብህ ፣
እንደ ገና ዳቦ እሳት ነደደብህ ፤

እንል ይሆናል ። ክርስቶስ ግን ደግ ሳለ ተገረፈ ። የፈወሳቸው እጆች በጥፊ መቱት ፣ የሠራቸው ክንዶች ጅራፍ አወረዱበት ። በንጽሕናው ተቀጣ ። ሌሎችን በማዳኑ ቆሰለ ። ያ የሮማውያን አለንጋ ጫፉ ላይ ድቡልቡል ብረቶች አሉት ። የተሰባበሩ አጥንቶችም አዘርዝረዋል ። ብረቱ ሥጋውን ሲቀጠቅጥ ፣ ያዘረዘሩት ሹል አጥንቶች አካልን መቅደድ ይጀምራሉ ። ሲደጋገም ሥጋ እየተቦጨቀ ይነሣል ፣ ደም እንደ ጎርፍ ይወርዳል ። በጌታችን ላይ የሆነው ይህ ሁሉ ነው ።

አካላቸው በበሽታ ፣ ልቡናቸው በኀዘን የታመመባቸው ብዙዎች ናቸው ። እነርሱን ሊፈውስ ክርስቶስ ተገረፈ ። ወላጆች ልጆቻቸውን የሚገርፉት “እንዳይለመድህ” እያሉ ነው ፣ ጌታ ክርስቶስም “እኛን መውደድ እንዳይለመድህ” ተብሎ ተገረፈ ። እርሱ ጅራፍ የማያስቆመው ፍቅር ነበረውና መውደድን አልተውም ብሎ ተሰቀለ ። ቢጠላን ዓለም እርስዋን መስሏልና በጅራፍ ትለቅቀው ነበር ። እንቢ ብሎ በማፍቀሩ ተሰቀለ ። በመገረፉ ቍስል ተፈወስን ። ቍስል ማንንም የመፈወስ አቅም የለውም ። ወዳጃችን ቢቆስልልን የበለጠ ያመናል ። የአምላክ ልጅ በመቍሰሉ ግን ተፈውሰናል ። የብዙዎች አምላካቸው የሚያቆስል ነው ፣ የእኛ አምላክ ግን ለፍቅር የቆሰለ ነው ።

ብዙ በሽታዎች ተራብተውብናል ። የማያቃስት ሰው የለም ። የሥነ ልቡና ስብራት በዝቷል ። ሰው በሰው ተጎድቷል ። እናውቃለን በሚሉ ሰዎች በመጎዳታቸው ብዙዎች ልባቸው ቂም አርግዟል ። ሥጋንም ነፍስንም የሚፈውስ አንድ ቍስል አለ ። እርሱ የጌታችን የመገረፉ ቍስል ነው ። እናቶች ልጆቻቸው ሲታመሙ ይታመማሉ ፣ ግን ልጆቹ አይድኑም ። አንዳንድ ሰው ዓይኑ የታመመ ወገን ሲያይ አብሮ ይታመማል ፣ ጥርሱን ያመመው ሰው ሲያይ ታሞ ያድራል ። የሌላውን ስቃይ ይዘው የሚገቡ ሰዎች አሉ ። ታማሚውን ግን አያሳርፉትም ። እንደውም ሁለት በሽተኛ ይሆናሉ ። በመገረፉ ቍስል የፈወሰን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ነው ።

በኑሮ በአገልግሎት የተገረፍን ፣ የቆሰልን ነን ። በመገረፉ ቍስል ግን ተፈውሰናል ። የተገረፈ ብቻ የተገረፈን ያድናል ። ቅምጥሎች ሳይሆኑ የቆሰለው እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ መልስ ይሆነናል ። እርሱ በየዕለቱ አይገረፍልንም ፤ አንድ ጊዜ በሆነው መገረፉ ፈውሳችንን በእምነት እንቀበል ። የፈውስ ዘመን ይሁንልን !

ዕለተ ብርሃን 9

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 14 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም