የትምህርቱ ርዕስ | ችሎታ አይደለም

“ክፉ መናገርና ቂጣ መጋገር አያቅትም።”

“ጮኻ የማታውቅ ወፍ የጮኸች ዕለት ፣ ዕለቁ ዕለቁ ትላለች” ይባላል ። አንደበትን ዘወትር በልኩ መጠቀም ቃላትን ለመምረጥ ፣ አሳብን ለመግለጥ ፣ ፍሰትን ለመጠበቅ ፣ ጣዕምን ለማምጣት ፣ ጆሮን ለማስከፈት ፣ ልብን ለመማረክ ፣ መልካምን ነገር ለማወጅ ይጠቅማል ። ዝም ብለው ተቀምጠው ድንገት የሚናገሩ ሰዎች የድምፃቸው ነጎድጓድ ጆሮን ይገርፋል ። ከማስረዳት መቆጣት ፣ ከማስረጽ እልህ ውስጥ መክተት ፣ ከመማረክ መገፍተር ይቀናቸዋል ። የተናገሩት መልካም ቢሆን እንኳ ያወጡበት ድምፀት ፣ የተናገሩበት ቃና ፣ የመጠኑት ድምፅ መልእክታቸውን ይገድለዋል ። ሰዎች ቃላችንን ብቻ ሳይሆን ድምፃችንን ይለኩታል ። በድምፃችን ውስጥ ያለው ልኬት ቍጣን ፣ ትዕቢትን ፣ ልግመኛነትን ፣ በእሺታ ውስጥ ያለውን እንቢታ ይናገራል ። እንዲሁም የድምፃችን ልኬት ትሑት ልባችንን ፣ የፍቅር ቅላፄአችንን ፣ የመታዘዝ ጉልበታችንን ያሳያል ። ሰዎች ቀጥሎ የሚያዩት ተግባራችንን ነው ። ተግባር የልብ ወደብ ነው ። ተግባር ሰዎች እኛን የሚለኩበት የመጨረሻው ሚዛን ነው ። እግዚአብሔር ከምኞታችን እስከ ተግባራችን ያለውን ያያል ። በልቡ የተመኘ አመነዘረ ያለው ጌታ የልባችንን ንጹሕነት ፣ የምኞታችንን ቅድስና ፣ የምንጩን ጥራት እንደሚፈልግ ያሳያል ። ሰው በምኞትም መቀደስ የተፈቀደለት በመሆኑ ደካማ ነኝ ብሎ መቀመጥ የለበትም ። እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ሊፈጸም የማይችል ትእዛዝ አልሰጠውምና ። እግዚአብሔር የልባችንን አሳብ ያደምጣል ፣ በመጨረሻ ተግባራችንን ይፈልገዋል ። የመጨረሻ ቀን ጥያቄ ስለ በጎ አድራጎት ድርጅት የነበረን እቅድ የሚጠየቅበት ሳይሆን ብራብ አብልታችሁኛል የሚል መጠይቅ ያለበት ነው ። ሰዎችም የልባችንን ማወቅ ባይችሉም ፣ ልብ በተግባር ይጎላልና በተግባራችን ልባችንን ያዩታል ። ድምፅ ፣ ቃል ፣ ተግባር ተናባቢ ናቸው ።

የንግግር ችሎታ ተፈጥሮ ሳይሆን ልምምድ ነው ። አፍ የፈታነው የሚያለማምዱን ሰዎች ስለነበሩ ነው ። እነርሱ ቋንቋን ሲያሳውቁን ከአደጋ የሚጠብቁ የጥንቃቄ እውቀቶችንም አስጨብጠውናል ። ምግቡን ብቻ ሳይሆን የቀረበበትን ሰሐን ማየት ግዳችን ነው ። እንዲሁም ቋንቋ ፣ የንግግር ጥበብ አሳብን የምናቀርብበት ገበታ ወይም ሰደቃ ነው ። በየዕለቱ በልኩ መናገር ፣ ተገቢና ገንቢ አሳቦችን መሰንዘር አስፈላጊ ነው ። አንደበት ለመናገር ተፈጥሮአልና ካልተናገሩበት ተፈጥሮ ባክኗል ማለት ነው ። ጨዋነት ዝምታ ሳይሆን የሚናገሩትንና የሚናገሩበትን ቦታ ማወቅ ነው ። ከንግግር የሚሻል ዝምታ እንዳለ ሁሉ ከዝምታ የሚሻልም ንግግር አለ ። ሁሉም በቦታው ሲሆን ዝምታም ጌጥ ፣ ንግግርም ወርቅ ይሆናል ።

ንግግር ዘር ነው ። የተዘራ ነገር መብቀሉና መታጨዱ አይቀርም ። አንደበት የፍርድ ምክንያት ነው ። ሰዎች ፍርድ ቤት ሲከስሱን ሰድቦኛል ፣ ዝቶብኛል ፣ ክብሬንና ማንነቴን አዋርዷል ብለው ነው ። ክፉ አንደበት ያስከስሳል ። ነቢዩ ለአፌ ጠባቂ አኑር ብሎ መጸለዩ ተገቢ ነው ። ንጉሥ ሳለ ሁሉን ገዝቷል ፣ አንደበቱ ግን አልገዛ እያለው ተቸግሯል ። በአንደበቱ ላይ የበላይ የሆነ ሌሎች ኃጢአቶች አያሸንፉትም ። አንደበት ኃጢአት የሚወጣበት ብቻ ሳይሆን የሚገባበትም ነው ። የፈረድነው ፣ የሳቅንበት ነገር መልሶ ፈተናችን የሚሆነው አንደበት የኃጢአት መግቢያ ስለሆነም ነው ። ። በአንደበቱ መልካም የዘራ መልካም ፍሬ ያጭዳል ። መልካም መናገር አሳብን ማላቅ ፣ ቃላትን መምረጥ ፣ ስፍራውን መለየት ፣ ቆራጥና ትሑት መሆን ይፈልጋል ። ክፉ መናገር ግን ማፍረስ በመሆኑ ሙያ አይጠይቅም ። አንድ ቤት ሲሠራ ብዙ ሊቃውንቶች ይተባበሩበታል ። ንድፉ ፣ ግንባታው ፣ ውበቱ በተለያዩ የመስኩ ባለሙያዎች ይጠናል ። ሲፈርስ ግን ባለሙያዎች አያስፈልጉትም ። በብዙ ሺህ የመዶሻ ምቶች የተሠራው ቤት በአንድ የቦምብ ፍንዳታ ይፈርሳል ።

ሴትዬዋ ራሱዋን ለማሞገስ “ተናድጄ ጮክ ብዬ ከተናገርሁ በኋላ ውስጤ ባዶ ነው” አለች ። ሰባኪውም ሲመልስላት፡- “ጥይትም ከተተኮሰ በኋላ ቀለሃው ባዶ ነው ፣ ነገር ግን ሰው ገድሏል” አላት ይባላል ። እኛ ተናግረን አርፈን ይሆናል ፣ በእኛ ንግግር ግን ሰዎች እንቅልፍ ያጣሉ ። እኛ ተናግረን ይቅር ብለን ይሆናል ፣ ሰዎቹ ግን ለቀጣይ ጊዜያት ውስጣቸው በቂም ተመርዟል ። ክፉ መናገር እውቀት ፣ ቂጣ መጋገር ችሎታ አይጠይቅም ።

ቆጥበን መናገር ፣ ቆጥበን መጣላት አልቻልንም ። የምንናገረው እስከ መጨረሻው ፣ የምንጣላውም ለእርቅ እንዲያስቸግር አድርገን ነው ። የተሰማንን ሁሉ እንዳንናገር ሕሊና የሚባል ማንጠሪያ አለ ። ብስጭታችንን ሁሉ እንዳናፈስሰው ልቡና የሚባል መርሕ ተሰጥቶናል ። ለሚያልፍ ስሜታችን የማያልፍ ንግግር መናገር ተገቢ አይደለም ። ትላንት የነበረው እንደተለወጠ የዛሬውም ይለወጣል ። ዓለም በተለዋዋጭ ሕግ ውስጥ ናት ። ለስሜታችን ሳይሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ መሆን ይገባናል ። ምንም ነገር ከመናገራችን በፊት “ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ቦታ ቢሆን ምን ይናገር ነበረ” ብለን ማሰብ ይገባናል ። ራሳችንን ወክለን አንኖርምና የምንናገረው ነገር የክርስቶስ እንደራሴነታችንን የጠበቀ ሊሆን ይገባዋል ።

ትችትን መሰንዘር ፣ ሰውዬው ለዓመታት የደከመበትን ነገር በአንዲት ቃል ለመጣል መነሣሣት ፣ ማድነቅን አለመልመድ ፣ ሁሉንም ነገር በጥቁር መነጽር ማየት ፣ ጨለምተኛነት ፣ ስለ ሰው ሁሉ የምንናገረው ክፉ አለማጣት ይህ እውቀት አይደለም ። ከዚያ ይልቅ ያ ሰው እኔ ብሆን የማልሠራውን በመሥራቱ ፣ ይህን ያህል ጊዜ ለዚያ ነገር በመድከሙ ፣ ያልሠራውን ሳይሆን የሠራውን አትኩሮ በማየት ማድነቅ ይገባናል ። በጉዞው አንድ ደረጃ እየወጣ ከሆነ ስናደንቀው ሦስት ደረጃ በአንድ ጊዜ ይወጣል ። ትላንት ክፉ ይናገሩ የነበሩ ዛሬ ተጸጽተዋል ። እኛም ለነገ ጸጸት እንዳናኖር ጠንቃቃ መሆን ይገባናል ። ደጉን ምክራችንን ያልሰሙ ሰዎች ክፉ ንግግራችንን ግን ሊሰሙት ይችላሉና ክፋትና አረም በሚለማበት በዚህች ምድር ለአፌ ጠባቂ አኑር ብለን መጸለይ ያሻናል ። “ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው ፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል ፤” ተብሏል ። 1ጴጥ. 3 ፡ 10 ።

ልዑል አምላክ ሆይ ፣ በደግ ቃል እየባረክህ ባርከን !

የብርሃን ጠብታ 19
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 28ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም