የትምህርቱ ርዕስ | አይዞህ መሞት የለም

“ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ። እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል አለው።” ዮሐ. 14 ፡ 6-7 ።

ንጉሥ ዳዊት ወደ ሥልጣን ከመምጣቱ በፊት ብዙ ትግል አሳልፎአል ። ዳዊት ያጽናናው ንጉሥ ሳኦል ካልገደልኩህ ብሎ አሳዶታል ። ከሞት የተረፈው ሰው ከጉድጓድ ያወጣውን ዳዊትን አልይህ ብሎ ጠልቶታል ። የእኔ ሕይወት ያለው የዳዊት መቃብር ላይ ነው በማለት ሳኦል አምኗል ። ሳኦል የዳዊት እርግጠኛ ጠላቱ ሲሆን የሳኦል ልጅ ዮናታን ደግሞ የዳዊት እርግጠኛ ወዳጁ ነበር ። ጨርሶ አይጨልምም ፣ ሁሉ ጠላት ሁሉ ወዳጅ አይሆንም ። ለዳዊት በእረኝነት አቅም የንጉሥ ጠላትን መሸከም ከባድ ነው ። ሰው ግን የተሰጠውን አልችልም አይልም ። ሳኦል የነገውን የዳዊት ክብር አይቶ ፈራ ፣ ዳዊት ደግሞ የዛሬውን ትግል አይቶ ተስፋ ቆረጠ ። መድረሻችን ከእኛ ይልቅ ለሚጠሉን ይታያቸዋል ። ዮናታን ምንም እንኳ አልጋ ወራሽ ቢሆንም ዳዊት እንዲነግሥ ይፈልግ ነበር ። ፍቅር ለወዳጁ ንግሥናንም ይለቃል ። እነዚህ ቡሩካን በብሉይ ኪዳን የሐዲስ ኪዳንን ኑሮ የኖሩ ነበሩ ። ዮናታን ዳዊት ተስፋ እንዳይቆርጥ ሊያበረታታው ሲሞክር ፣ ዳዊት ግን ሁሉም ነገር አብቅቷል የሚል ስሜት ውስጥ ገብቶ ነበርና እንዲህ አለ፡- “በእኔና በሞት መካከል አንድ እርምጃ ያህል ቀርቶአል ብሎ ማለ ።” /1ሳሙ.20፡3 / ምሎ ተስፋ ቆረጠ ፣ የሞትን ድምፅ ሰማ ።

ሕይወት ሳይሆን ሞት የሚሸተው ፣ በአቅሜ የማልመልሰው ጠላት መጥቶብኛል ፣ መደበቅ እንዳልችል ሠራዊት ያስሰኛል ፣ ዘመን እንደ ገደል ከድቶኛል እያለ የሚጨነቅ ሰው ብዙ ነው ። “አዲሱ ሬሳ የቆየውን አስነሣ” እንዲሉ ከልጅነቱ ጀምሮ ያሳለፈውን ትግል እያሰበ ፣ የዛሬን ማዕበል እየደመረ እኔ ለደስታ አልተሠራሁም ፣ እንባ ቀለቤ ፣ ልቅሶ ኑሮዬ ነው የሚል ዕለት ዕለት እየጨመረ ነው ። በሞትና በእርሱ መካከል አንድ እርምጃ የቀረ የሚመስለው ሰው ብዙ ነው ። ያዕቆብ በዚህ ስሜት ውስጥ ሆኖ የጭንቀት ሌሊትን ፣ የፍርሃት አዳርን አስተናግዶ ነበር ። ወንድሜ ይገድለኛል ብሎ በመፍራት የምጥ ሌሊት አሳለፈ ። የነደፋቸው ስልቶች ዕረፍት አልሰጡትም ። ለሚስቶቹና ለልጆቹ ለማማከር ልቡ አላዘዘውም ። ብቸኛው ያዕቆብ ካልባረከኝ አልለቅህም ብሎ ሙሉ አዳር በእንባ ጸለየ ። ሲነጋ ግን እንደ ፈራው አልነበረም ፣ ወንድሙ በፍቅር ተቀበለው ፤ የዘመናት ፍርሃቱ ከንቱ ነበር ። ቦታው ላይ ሲደርስ ሁሉም ነገር እንዳሰበው አልነበረም ። ዳዊትም አብቅቶልኛል ፣ ካልተገናኘን ስላደረግህልኝ በጎነት ሁሉ አመሰግናለሁ ብሎ ዮናታንን ቢሰናበትም እውነቱ ግን ያ አልነበረም ። ዮናታን ቀድሞ ሞተ ፣ ዳዊት በሳኦል ዙፋን ተቀመጠ ። እንደውም የምንሞት ሲመስለን ልንኖር ተፈቅዶልናል ማለት ነው ። ጠላት የሞትን ድምፅ ሲያውጅብን ከዘማሪው ዳዊት ጋር በመሆን “አልሞትም በሕይወት እኖራለሁ እንጂ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እናገራለሁ” ልንል ይገባናል ። /መዝ. 117፡17/።

ድባቴዎች እየተጫጫኑ ሲመጡ ሰውነት መዛል ፣ ተኝተን ስንነሣም የድካም ስሜት ፣ ደጁን መፍራት ፣ ከሰዎች ጋር መገናኘት አለመፈለግ ፣ ካለንበት ዞን ላለመውጣት መጣር ፣ እሞታለሁ የሚል ፍርሃት እየተጫነን ይመጣል ። ከብዙ ውጣ ውረዶች ፣ ጠብቀናቸው የነበሩት ነገሮች ካለ መሳካታቸው የተነሣ ፣ በዙሪያችን የሚያረካ ነገር ፈልገን በማጣት ወደዚህ ስሜት ልንገባ እንችላለን ። ድባቴዎች እንደ ድንጋይ የሚጫኑ ፣ የራሳቸው ሙቀት ያላቸው እስር ቤቶች ናቸው ። ፈጥኖ መጸለይ ፣ ቃለ እግዚአብሔር መስማት ፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ ፣ ከወዳጆቻችን ጋር መጫወት አስፈላጊ ነው ። የሚሰማን የሞት ድምፅ ከሰማይ የመጣ ሳይሆን ድባቴ ያስከተለው መሆኑን በመገንዘብ መንቃት አለብን ። ሞት ሌባ ነውና ማንም ጋ መጣሁ ብሎ መጥቶ አያውቅም ። ከሁሉ በላይ በውስጣችን የሞት ድምፅ ስንሰማ ክርስቶስ እኔ ሕይወት ነኝ ያለውን ማስታወስ ይገባል ። በባሕሩ ማዕበል እየተወዘወዘ ያለው ጳውሎስ ፣ የቁም እስረኛ ሆኖ ወደ ሮም የሚወሰደው ሐዋርያ፡- “ብዙ ቀንም ፀሐይን ከዋክብትንም ሳናይ ትልቅ ነፋስም ሲበረታብን ጊዜ፥ ወደ ፊት እንድናለን የማለት ተስፋ ሁሉ ተቈረጠ” ብሏል ። /የሐዋ. 27፡20/። ክርስቲያን ተስፋ ቆርጦ አይቀርም እንጂ ተስፋ መቍረጥ ሊሰማው ይችላል ። ጳውሎስን ያበረታው ግን በሮም መናገሻ በቄሣር ፊት ወንጌልን ትሰብካለህ ያለው የጌታ ቃል ይፈጸማልና በባሕር ውስጥ አልቀርም የሚለው እምነቱ ነው ። ሰው ቃል እያለውም ይፈራል ፣ ተስፋ ይቆርጣል ።

የእኔ ነገር አብቅቷል የሚሉ ድምፆች እየተበራከቱ ነው ። ዙሪያውን ሲያይ ጨለማ ፣ ጆሮውን ቢቀስር የመርዶ ድምፅ የበዛበት ሰው ይደክመውና አብቅቷል ብሎ ለራሱ ይናገራል ። ይህ ድምፅ ብዙ ጊዜ በአፍ የማይናገሩት ለራስ ግን የሚነግሩት ነው ። ደቀ መዛሙርቱ ሁሉም ነገር አብቅቷል ፣ ጌታም ሊያዝና ሊሰቀል ነው ፣ እንዴት ነው የምንኖረው ( ጅምሩ ለምን አላልቅም አለ ( በሚል ተስፋ መቍረጥ ውስጥ ገብተው ፣ ሰዉ ሁሉ አድካሚ ሆኖባቸው ሳሉ ጌታችን እኔ ሕይወት ነኝ አላቸው ።

አዎ በራሳችን ፈቃድ አልመጣንምና በራሳችን ኃይል መኖር አንችልም ። ክፉ ጠረን ያለው የሞት ሽታ ሲመጣብን ክርስቶስ የሕይወት ሽታ መሆኑን ማመን አለብን ። ዓላማችን ቢጠፋንም እግዚአብሔር ግን በእኛ ላይ ዓላማ አለው ። ተረስተን በምድር ላይ የቀረን ፣ የማይኖር ኑሮ የተሰጠን አይደለንም ። ለቀኑ የሚሆን ኃይል ከሰማይ ይመጣል ። ክርስቶስ ለቆሰለው ሥጋችን ፣ ለዛለው መንፈሳችን ሕይወትን ይሰጣል ። መጠውለጋችንን ሊያለመልም እርሱ ወደ እኛ ይመጣል ።

አላበቃም ሕይወት ክርስቶስ ነው ። ትሞታለህ የሚለውን የጠላት ድምፅ አትስማ ፣ ክርስቶስ ሞትን የሚያሸነፍ ሕይወት ነው ። ጨለማ የራሱ ህልውና የለውም ፣ የብርሃን አለመኖር ጨለማን ይፈጥራል ። ሞትም ህልውና የለውም ፣ ክርስቶስ ሕይወት ካልሆነልን የሚበረታብን ነው ። ክርስቶስ ሕይወት በሆነበት ሞት የለም ። አይዞህ ወዳጄ መሞት የለም !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 28 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም