የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እውነተኛ ፍቅር

“የትእዛዝ ፍጻሜ ግን ከንጹሕ ልብና ከበጎ ሕሊና ግብዝነትም ከሌለበት እምነት የሚወጣ ፍቅር ነው” 1ጢሞ. 1፡5
አይሁዳውያን በአንድ እግርህ ቆመህ የምትናገረው የሚል አባባል አላቸው ። በአንድ እግር ቆመው የሚናገሩት እግዚአብሔርን በፍጹም ልብ መውደድና ባልንጀራን እንደ ራስ መውደድ ነው ። “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ” የሚለውን ቃል ደግማችሁ አስቡት ። ባልንጀራን እንደ ራስ የምትወዱ ከሆነ እግዚአብሔርን ከራሳችሁ በላይ መውደድ አለባችሁ ማለት ነው ። እግዚአብሔርን አልጠላም ማለት እግዚአብሔርን መውደድ አይደለም ። እግዚአብሔርን የምንወዳቸውን ያህል መውደድም እግዚአብሔርን ትልቅ ለማለት መፈተን ነው ። እግዚአብሔርን የራስ ያህል መውደድም ራስንና እግዚአብሔርን ማምለክ ነው ። እግዚአብሔርን ከራስ በላይ መውደድ እርሱ እውነተኛ አምልኮ ነው ። የሮማን ፍሬ አንድ ነው ፤ በውስጡ ግን ብዙ ፍሬዎችን ይዟል ። የምንጠራው ግን አንድ ሮማን ብለን ነው ። ፍቅርም እንደ ሮማን ፍሬ ነው ። በውስጡ ብዙ የሕግና የትእዛዝ ፍጻሜዎች አሉ ። ፍቅርን ገንዘብ ያደረገ ሁሉንም ትእዛዛት ፈጸመ ። ፍቅር አባ ጠቅል ነው ።

ሕግ ማለት የአታድርግ መመሪያ ነው ። ትእዛዝ ግን የአድርግ መመሪያ ነው ። ባለማድረግ መቀደስ አለመስረቅ ፣ አለመግደል ነው ። በማድረግ መቀደስ ግን መስጠት ፣ ለሌሎች ቸርነት ማድረግ ነው ። ሐዋርያው ስለ ሕግ እየነገረን አይደለም ። ሕግን የጨዋ ልጆችም ይጠብቃሉ ። አይገድሉም ፣ አይሰርቁም ፣ አይሳደቡም ። ከክርስቲያን ከዚያ ላቅ ያለ ነገር ይፈልጋል ። በእውነት ክርስትና ከጨዋነት በላይ ነው ። ክርስቲያን የሆነው ፖሊስ ላለማስቸገር አይደለም ። የዓለምን ሕመም ለመቀነስም ነው ። የዓለምን ሕመም የምንቀንሰው የሚያለቅሱትን እንባቸውን በማበስ ፣ ያዘኑት በማጽናናት ፣ የወደቁትን በማንሣት ነው ። በፍቅር ሕግን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ትእዛዛትን መፈጸም እንችላለን ።
ፍቅር ከሦስት ምንጮች ከተቀዳ ያን ጊዜ እውነተኛ እየሆነ ይመጣል ። ትእዛዛትንም ይፈጽማል ። እነዚህ ምንጮች ንጹሕ ልብ ፣ በጎ ኅሊናና ግብዝነት የሌለበት እምነት ናቸው ።
በየዕለቱ ልባችን እየደፈረሰ ተቸግረናል ። አንደኛውን ስህተት ይቅር ለማለት ታግለን እንደ ምንም ይቅርታ ካደረግን በኋላ የዚያኑ ቀን ሰዎቹ ሌላ ጥላሸት ይቀቡናል ። እንደ ገና ይቅርታ ባይገባቸውም ለራሳችን ሰላም ስንል ያንን ጥቁር ቀለም ለማጥፋት በጸሎት ፣ በቃሉ ፣ በምክር ፣ ያልበደሉንን ሰዎች በማሰብ ፣ የቀደመውን ጥሩ ጊዜ በማስታወስ ለማጽዳት እንሞክራለን ። ሰዎቹ ግን መልሰው አሁንም ልባችንን ያቀልሙታል ። ተሰብረን ስለምንኖር ይሰብሩናል ። ካልፈቀድንላቸው ግን አይሰብሩንም ። ሞተን ካልጠበቅናቸው አይገድሉንም ። ሞተን ስንጠብቃቸው ግን ገደልን ብለው ይፎክራሉ ። ንጹሕ ልብ በየቀኑ የምንቸገረው ነገር ሁኗል ። ያለፉት ዘመናት የጣዖትና የዓለማዊነት ትዝታዎችም ድቅን እያሉብን ንጹሕ ልባችንን እንከስራለን ። የምናየውና የምንሰማውን ስለማንመርጥም ልባችን ይቆሽሻል ። ሁልጊዜ በተግባር አንበድልም ። በአሳብ ግን ስንበድል እንኖራለን ። አሳባችን ሁሉ ቢከናወን አወይ ሰው ነኝ ለማለት ባልበቃን ነበር ።
እጅ እግር የሌለው ፣ ተግባር የጎደለው ፍቅር በዓለም ላይ አለ ። ይህ ፍቅር ንጹሕ ልብ ስለሌለው ነው ። በጥርጣሬ የሚታመስ ፍቅር በጎ ለማድረግ ይዘገያል ። “እባብ ያየ በልጥ ይደነብራል” እንዲሉ በትላንት ገጠመኙ የዛሬ ፍቅሩን የሚለካ ሰውም አፍቅሮም ፈሪ ነው ። ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል ማለት ብከዳ ፣ ብጎዳ አይልም ማለት ነው ። ምክንያቱም ምንጊዜም ተጎጂው አፍቃሪው ሳይሆን ፍቅርን የገፋው ሰው ነው ። ልቅሶ ቦታ ተለዋውጦ እንጂ ማልቀስ ያለበት ከዳተኛው ነው ። ከንጹሕ ልብ የማይወጣ ፍቅር በጎነት የለውም ። በእጁ አይሰጥም ፣ በእግሩ አይደርስም ። ንጹሕ ልብ የሌለው ፍቅር አካለ ጎዶሎ ነው ።
ፍቅር ማለት ቃላት ሳይሆን ተግባር ነው ። እውነተኛ ፍቅርም ከስሜት ይልቅ ለተግባር የሚያደላ ነው ። ሰዎች ተግባራዊውን ፍቅር አይወዱትም ። ከዚያ ይልቅ የሚያቆላምጣቸውንና የሚያጫውታቸውን ዱርዬ ይወዳሉ ። እውነተኛ ፍቅር ግን ተግባራዊ ነው ። እግዚአብሔር ከረዳን የቃልና የስሜትን ፍቅር ትተን ተግባራዊውን ፍቅር መከተል አለብን ። ወላጆቻችን አንድ ቀንም እወዳችኋለሁ ብለውን አያውቁም ። ፍቅራቸው ግን ተግባራዊ ነው ። ቀላል ልብ ያለው ሰው በድለላ ይሸፍታል ። ዛሬ እስቲ እናስተውል በተግባር የሚወዱን እነማን ናቸው ? ብለን እናስብ ። እኛም በተግባር የምንወዳቸውን ለማሰብ እንሞክር ። እውነተኛ ፍቅር ተግባራዊ ነው ። “እንደምትወደኝ አትንገረኝ ፣ እንደምትወደኝ አሳየኝ” የሚል አባባል አስታውሳለሁ ።
ፍቅር ተግባራዊ እንዳይሆን ሁለተኛው መሰናክል “በጎ ኅሊና” ማጣት ነው ። ዛሬ በዓለም ላይ ትልቁ የሰላም ምሥጢር በጎ ኅሊና እንደሆነ ታምኗል ። የዘወትር ጸሎታችንም ሊሆን የሚገባው፡- አቤቱ፥ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ፥ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ” የሚለው ነው መዝ. 50፡10 ። ደጋግመን እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ እንደምንለው ደጋግመን ይህን ጸሎት መጸለይ ይገባናል ። የቀና መንፈስ ፣ ቀናነት ፣ ለነገሮች በጎ ትርጉም መስጠት የደስታ መሠረት ነው ። ቀናነትን በተፈጥሮ የታደሉ ጥቂቶች ናቸው ። ቀናነትን ለማግኘት ብዙ ተጋድሎ ያስፈልጋል ። ንጹሕ ልብ ለራስ ሲሆን ቀናነት ግን ሰዎችን የምናይበት መነጽር ነው ። በሰለጠነው ዘመን “ሰዎች ለምን ክፉ ሆኑ ? ምን ዓይነት ጉዳት ቢደርስባቸው ነው ?” ተብሎ ታሪካቸው ይጠናል ። እርዳታ ለማድረግ ይሞከራል ። ክርስትናችን ግን ከሥልጣኔ አንሶ ቅንነት አልባ ሁኗል ። በጎ ኅሊና ከምቹ ትራስ ይልቅ ዕረፍት እንደሚሰጥ ይነገራል ። አዎንታዊነትን ማዳበር ከክርስትና አልፎ ዘመናዊነት እየሆነ ነው ። ፍቅር ተግባራዊ እንዲሆን በጎ ኅሊና አጋዥ ነው ።
ግብዝነት የሌለበት እምነት ለተግባራዊ ፍቅር ወሳኝ ነው ። ተዋንያን በሰዓት ሲሠሩ በሃይማኖት ስፍራ ያሉ ግብዞች ግን ለዘመናት የመተወን አቅም አላቸው ። ተውኔት በመድረክ እንጂ በሕይወት ሲሆን ከባድ ነው ። ከእውነተኛነት ግብዝነትን የሚያከብር ማኅበረሰብ ቢፈጠርም እውነት ግን ከእግዚአብሔር ጋር የምታገናኝ ድልድይ ናት ። ጽድቃቸውን ከሚነግሩን ድካማቸውን የሚነግሩን እውነተኞች እነርሱ ተስፋ ይሰጡናል ። መጽሐፍ ቅዱስ ኃጢአተኞችን የሚረዳ መጽሐፍ የሆነው ስለ ሰዎች ፍጹምነት ሳይሆን ስለ ድካማቸው ስለሚነግረን ነው ። የዳዊትን መግደልና ምንዝርና ፣ የጴጥሮስን መካድ ፣ የጳውሎስን ፀረ ክርስቲያንነት የሚነግረን ፤ ውድቀት መጨረሻ አለመሆኑን ተረድተን እንድንነሣ ነው ።
“በፍቅር ኃጢአቶቻችን ሁሉ ይቅር ይባሉልናል ።” ፍቅር ካለንም የሌሎችን ኃጢአት ይቅር እንላለን ። እውነተኛ ፍቅር ሦስት ምንጮች አሉት ። ንጹሕ ልብ ፣ በጎ ኅሊናና ግብዝነት የሌለበት እምነት ናቸው ። እኛ የጎደለን የቱ ይሆን ? 
1ጢሞቴዎስ /10/
ኅዳር 15 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ