የትምህርቱ ርዕስ | ክርስቶስ መንገድ  ነው

“ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ። እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል አለው።” ዮሐ. 14 ፡ 6-7 ።

መንገድ የጠፋው ሰው ይባዝናል ፣ ይንከራተታል ፣ ይንቀዋለላል ፣ ይፈራል ፣ ይጨነቃል ፣ ያገኘውን ሁሉ ይጠይቃል ፣ የነገሩትን ሁሉ ያምናል ፣ እየለፋ ይመለሳል ፣ ፀሐዩ ሲያዘቀዝቅ ዱር ላድር ነው ፣ አውሬ ሊበላኝ ነው ብሎ ይሸበራል ። መንገድ የጠፋው ሰው እዚህ ነኝ ብሎ ለማመልከትም ፣ ያለበትን አድራሻ ለመግለጥም አይችልም ። መንገድ ሲጠፋ የወደፊቱ ብቻ ሳይሆን አሁን ያሉበትም አይታወቅም ። መንገድ ሲጠፋ ብዙ ነገር ይባክናል፡- ጊዜ ፣ ጉልበት ፣ ገንዘብ ፣ ሕይወት ። መንገድ የጠፋው እናውቃለን ባዮች የማያውቁትን መንገድ ሲጠቁሙት እሺ ብሎ ይሄዳል ። ደፋር አላዋቂ ፈሪ አላዋቂዎችን ይመራል ። መንገድ የጠፋው ሰው እርሱ ብቻ አላዋቂ ሰዎች ሁሉ አዋቂ እንደሆኑ ይገምታል ። ሰዎች ለሰዓታት መንገድ ሊጠፋቸው ይችላል ። እስራኤላውያን ግን በምድረ በዳ ለዐርባ ዓመታት ያህል መንገዱ ጠፍቷቸዋል ። ባመኑ ሰዓት መንገዱ ወለል ብሎ ይታያቸዋል ፣ ጠላትም ወዶ ሳይሆን ተሸንፎ ጎዳናውን ይለቅላቸዋል ። ከእምነት ጎድለው በማየት ሲመላለሱ ግን መልሰው የበረሃ አዙሪት ውስጥ ይገባሉ ። ዙሪያውን ቢያዩት ከአድማሱ ጋር የተጋጠመ የአሸዋ ክምር ነው ። ምድረ በዳው ለምልክት የሚሆን አንድ ዛፍ እንኳ አልነበረውም ። የሚመጡትን ለመጠየቅ እንዳይቻል በዚያ መንገድ ማንም አይሄድም ነበር ። ያላቸው ብቸኛው መንገድ እግዚአብሔርን መስማት ነው ። እርሱ በግብጽ ምድር ደመላሽ ፣ በቀይ ባሕር መርከብ ፣ በምድረ በዳ ጓደኛ ፣ በጉዞው መሪ ፣ በበረሃው ጥላ ፣ በቃጠሎው እርካታ ነበረ ። እስራኤልን በበረሃ የመራ ዛሬም በበረሃው ዓለም ይመራናል ።

ብዙ ሰው መንገድ ጠፍቶታል ብንል ማጋነን አይሆንም ። መንገዱን ባገኝ ብሎ ሃይማኖት ይቀይራል ፣ እምነትን በፍልስፍና ይለውጣል ። ጽድቅን በኃጢአት ይተካል ። መድረሻውን ሳያውቅ የሚጓዝ ብዙ ነው ። ብቻ አለመቆም ነው እያለ ሲጓዝ የሚኖር ብዙ አለ ። ፎቅ ላይ የወጣ ወደ ላይ ቢሄድም ወደ ታች ሁለቱም ጉዞ ነው ። ስለሄድን እየደረስን አይደለም ። አለመቆም መሄድ ቢሆንም ግብ ግን ሊሆን አይችልም ። እየተረጋጋን ያለነው ባለመቆም ነው ። ቁልቁል እየወረድን ነው ። ስላልቆምን እየተጓዝን ይመስለናል ። መባዘን ፣ መቦዘን ፣ ሥራ መፍታት ፣ ትርጉም የሌለው ድካም ውስጥ መውደቅ የብዙዎች ኑሮ ነው ። ራስን በማሰቃየት መርካት ፣ ሁሉንም ነገር በጭንቅ ለማግኘት መሞከር ፣ ከአንዱ ሃይማኖት ወደ አንዱ መሰደድ ፣ መምህርን በመምህር መለወጥ ፣ አዋቂ ጠንቋይ መፈለግ ብዙዎችን መንፈሳዊ ዘማ ያደረገ ነው ። አልተቀመጡ ፣ አልቆሙ ፤ አልተራመዱ ፣ ወይ አልደረሱ ብዙዎች በመንቀዋለል ሽቅብና ቁልቁል ይላሉ ። እስከ ዛሬ የሄዱበት የኃጢአት መንገድ እረፍት እንደሌለው ቢገባቸውም ወይ ከቃለ እግዚአብሔር አሊያም ከኪሣራቸው መማር አልቻሉም ። መንገድ ሲጠፋ የሚከፈለው ዋጋ ብዙ ነው ። ከተጠሩበት ዘመን አንጻር አስተማሪ መሆን ሲችሉ ዛሬም መንገዱን ያላገኙ አያሌ ናቸው ። መንገዱን አለማግኘት ፈሪ ፣ ተጨናቂ ፣ ሁልጊዜ በጥያቄ ውስጥ ነዋሪ ያደርጋል ። መኖርም መሞትም ሊያስፈራ ይችላል ።

ጌታችን ወዳለበት የሚያደርሰውን መንገድ እንፈልጋለን ። እርሱ የነፍስ ጥማት ነውና የማይፈልገው ሰው የለም ። ያለ እርሱም እፎይ ማለት የማይቻል ነው ። ሩጫ ምንም መልካም ቢሆን የሚሸለመው የጀመረው ሳይሆን የፈጸመው ነው ። ብዙዎች ይጀምራሉ ፣ ግን መፈጸም አይችሉም ። መንገዱም ክርስቶስ ግቡም ክርስቶስ መሆኑን ማወቅ ፣ እርሱ አስጀማሪና አስፈጻሚ አልፋና ዖሜጋ መሆኑን መረዳት ልብን የሚያስደስት ነው ። በየትም ዓለም መንገድ የጠፋውን ሰው መንገደኛ ሁሉ ይራራለታል ። በአንዳንድ አገር ቆመው በትክክል ያመለክታሉ ፣ በሌላ አገር ትንሽ አብረው ተጉዘው በዚህ በኩል ሂድ ይላሉ ። ከሁሉ የሚያረካው ፣ ልብን ከፍርሃት ነጻ የሚያወጣው እኔም ወደዚያው ነኝ አብረን እንሄዳለን የሚል ወዳጅ ከተገኘ ነው ። በእውነት ሁላችንም የጽዮን መንገደኞች ነን ። አብረን ብንጓዝ ስጋት ይቀንሳል ፣ አብረው ሲጓዙ ሽፍታም ፣ ቀማኛም አያሰጋም ፣ አብረው ሲጓዙ ሳቁ ጨዋታው መንገድ ያጋምሳል ፣ አብረው ሲጓዙ ስንቅ ይቃመሱ ።

ያለ መንገድ መድረስ የለም ። ያለ ክርስቶስም ሰማይን መውረስ አይቻልም ። ምሥጢረ ጥምቀትና ምሥጢረ ቍርባን መሠረቱ ምሥጢረ ሥጋዌ ነው ። የምሥጢረ ሥጋዌ መሠረትም ምሥጢረ ሥላሴ ነው ። ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ሰው ሆኖ በአንድ አካልና ባሕርይ ተገልጦ በመስቀል ላይ ሞቶ መንገዱን ከፍቶልናል ። እርሱ መንገድ ነው ፣ ወደ ዘላለማዊ አባቱ ያደርሳል፤ ወደ ሕይወት እልፍኝ ያስገባል ። እርሱን ወልድ ዋሕድ ብሎ ማመን የዘላለም ሕይወት ያሰጣል ። ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት የተወለደውና ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም ያለ አባት የተወለደው አንድ ክርስቶስ ብሎ ማመን እርሱ የመጨረሻው እውነት ፣ የሚያድነው ሕይወት ነው ። ያለ ክርስቶስ እውነትን ማወቅ ፣ ያለ ክርስቶስ በሕይወት መኖር አይቻልም ። የደመ ነፍስ ሕይወትን እንስሳትም እየኖሩት ነውና በዚያ የሚመካ ካለ እንደ እንስሳ ኖሮ ማለፍ ይችላል ፤ ክርስቶስ ግን ዘላለማዊ ሕይወትን ይሰጣል ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 24 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም