መግቢያ » ትረካ » ወለተ ኢያኢሮስ » ወለተ ኢያኢሮስ

የትምህርቱ ርዕስ | ወለተ ኢያኢሮስ

  

/ማር. 5፡21-43/

እግረ መንገድ የምናከናውናቸው ብዙ ተግባራት ያልተጠበቁና እንደ ተአምር የሚቆጠሩ ፣ “በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ” ተብለው ስያሜ የሚያገኙ ናቸው ። እግዚአብሔር ግን እግረ መንገድ በሚመስል የታቀደ ተግባር ይሠራል ፣ በአንድ ሰዓትም የብዙ ሰዎችን ጉዳይ ይፈጽማል ፣ የዘመናትን እንቆቅልሽ ይፈታል ። አንዱ ታሞ ሌላው ሞቶበት ቢሆንም ሳያወዳድር ለሁሉ ያዝናል ። እናቱ ለሞተችበትም እናቱ ገበያ ለሄደበትም ለሁሉም የአባትነቱን ድምፅ ያሰማል ። ሕመምን እፈውሳለሁ ፣ ሞት ይሳነኛል ሳይል በጌትነቱ ሁሉን ይገዛል ። ጸጋ ልዩ ልዩ ቢሆንም ባለ ጸጋውና አዳዩ ግን አንድ መንፈስ ቅዱስ ነው ። ጉዳይ ብዙ ቢሆንም ማኅተሙን የሚፈታው ግን አንድ ክርስቶስ ነው ። ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ልበ ሰፊነት ፣ ወደ አምላክ ይቅር ባይነት ፣ ወደ ጌታ ችሮታ የምንገባበት በር ነው ። ከልቡ የሚጸልይም ጠባብነት ፣ ምቀኝነትና ስስት ይርቁለታል ። ኢያኢሮስ ለሌላው ስትደርስ ለእኔ ዘገየህ ፣ በእኔ ጸሎት እነ እገሌ ተጠቅመው እኔ ባዶዬን ቀረሁ ፣ እኔ ሙት ተሸክሜ አንተ ግን ለበሽተኛ ትቆማለህ አላለም ። እኔ ናዳ ወርዶብኝ አንተ ግን ጠጠር ለመታው ታዝናለህ የሚል ልብ አልነበረውም  ። 

ኢያኢሮስ በአሮጌይቱ ድንኳን አዲሱን ወንጌል የሚያገለግል ነበር ። አሮጌይቱ ድንኳን ሰማይን የማታይ ፣ ከምድረ እስራኤል ውጭ አስፍታ የማትሄድ ፣ ወደ እኔ ኑ እንጂ ልምጣ የማትል ፣ ሙከራ እንጂ መፍትሔ የሌለባት ነበረች ። አዲሲቱ ወንጌል ግን ምድርን ትታ ሰማይ ሰማይ የምታይ ፣ ግዛቷን በዳርቻ በምድር ጥግ ያደረገች ፣ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ የሚል  አደራ የተቀበለች ፣ በአንዱ በግ ፍጥረት መጥገቡን ያበሰረች ናት ። ትንቢት ሳይሆን ፍጻሜ ፣ ሙከራ ሳይሆን መፍትሔ ያለባት የእግዚአብሔር ድንኳን ናት ። ኢያኢሮስ ወደ ክርስቶስ በራሱ ተነሣሽነት ለመምጣት ቀኑ ባይረዳውም በልጅ ሞት ግን መጥቷል ። ሰው በተለያየ ደወል ወደ ክርስቶስ ይመጣል ። ለልጅ ሕመም መጥተው ራሳቸው በነፍስ መሞታቸውን ያወቁ አያሌ ናቸው ። ሰው ሊያሳክሙ ሄደው የራሳቸውን የከፋ በሽታ የሚያገኙ ብዙ ናቸው ። ታክሜአለሁ ታከሙ የሚል ወንጌላዊ ነው ። እግዚአብሔር በመምጣታችን ደስ ይለዋል እንጂ “እንዴት ነው የመጡት ?” ብሎ አመጣጣችንን አያጠናም ። “እኔ ባጣ ቆየኝ ነኝ ወይ ?” አይልም ። “አልሳካ ሲላችሁ ነው የመጣችሁት” አይልም ። “ደስታችሁን ከዓለም ጋር ነስንሳችሁ የኀዘን አመዳችሁን እኔ ጋ ለመበተን መጣችሁ” አይልም ። እግዚአብሔር አልመጣም ስንል ይገሥጸናል ፣ ስንመጣ መንገድ አጋምሶ ይቀበለናል እንጂ አይታዘበንም ። 

እግዚአብሔር የወደቀውን ዛፍ አንሥቶ ባለ ፍሬ ያደርገዋል እንጂ በወደቀ ዛፍ ላይ ምሳር/መጥረቢያ አያበዛም ። 

ሲነጋ የነጋላቸው የታደሉ ናቸው ። ንጋትን ንጋት ፣ ደስታንም ደስታ አድርግልን ማለት ትልቅ ጸሎት ነው ። ኢያኢሮስ ነግቶ የጨለመበት በልጁ ሞት ነው ፤ የልጅ ደስታን ሳይጨርስ የልጅ ኀዘን የወደቀበት መከረኛ ነው ። ከሁሉ የሚከፋው በንጋት ውስጥ ያለው ጨለማ ፣ በደስታ ውስጥ ያለው ኀዘን ነው ። ሲነጋ የጨለመባቸው ፣ ሌሊትና ቀን አንድ የሆነባቸው ብዙ መከረኞች አሉ ። ጌታችን ሌሊቱን ሙሉ ሲገሰግስ አድሮ ማለዳ ደረሰ ። የዘመናትንና የዕለትን ልመና ለመፈጸም አለሁ አለ ። የዘመናት ችግረኞች የጌርጌሴኖኑ እብድና ደም ይፈስሳት የነበረችው ሴት ናቸው ፣ የዕለት ችግረኛ ወለተ ኢያኢሮስ ናት ። ቀን ሲደርስ አምባ ይፈርስ እንዲሉ ቀን ሲደርስም የዘመናት ጥያቄ መልስ ያገኛል ። 

ያ እብድ ዓመታት ያለፉት ፣ ይህች ሴትም አሥራ ሁለት ዓመት ደም ይፈስሳት የነበረች ናት ። የኢያኢሮስ ቤት የገባው የሞት አደጋ ግን ከባድ ነበረ ። ሕመምን ማስታመም ይቻላል ፣ ሞትን ማስታመም ግን አይቻልም ። የጠፋ ፋኖስን መለኮስ ይቻላል ፣ የጠለቀች ፀሐይን መመለስ ግን አይቻልም ። እግዚአብሔር የዘመናት ሕመምን ፣ የዕለት ሞትን ሊያስወግድ ገሰገሰ ። ሕመም የዘመናት ሲሆን ሞት ግን አንድ ቀን ነው ። ይህ ጌታ የጠራው ጸሎታቸው ብቻ ሳይሆን የሚጮኸው ጭንቀታቸውም ነው ። እግዚአብሔር ለለመኑት ቸር ነው ፤ ላልለመኑትም እስኪለምኑት ድረስ መንገድ የሚጠርግ ነው ። ፈውሱ ልዩ ልዩ ነው ። አንዳንዱን በሽታ በተግሣጽ ፣ አንዳንዱን በልብሱ ዘርፍ ፣ ሌላውንም በሥልጣን ቃል የሚናኘው ነው ። እብደት መገሠጽ አለበት ። ራስን ብቻ ማዳመጥ ፣ ሌላውን ዕረፍት መንሣት ያለበት ፣ ምቾትን ማምለክ ሌላው መርገጥ ፣ እኔ ልኑር ብዙዎች ቤዛ ይሆኑልኝ ማለት ፣ ራስን ገለልተኛና ጉዳተኛ ሌላውን ጠላት አድርጎ መመልከት … ይህ እብደት ነው መገሠጽ አለበት ። ድምፅ የሌለው የደም ዥረትም ድምፅ በሌለው የልብሱ ዘርፍ መቆም አለበት ። ሞትም ስለሌላው በሚማልዱ ይወገዳል ። እግዚአብሔር ምልጃን ይወዳል ። 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከበሽታ ብቻ ሳይሆን ከሞትም ያድናል ። 

የጌርጌሴኖኑ እብድ መጸለይ አይችልም ። ለመጸለይም አእምሮ ያስፈልጋል ። ደም ይፈስሳት የነበረችው ሴትም ድምፅ አላሰማችም ። መቃተትንም ጸሎት ብሎ የሚሰማ የኤልያስ አምላክ ሕያው ነው ። ወለተ ኢያኢሮስ/ የኢያኢሮስ ልጅም ለመጸለይ የማትችል ሙት ናት ። አባትዋ ግን ስለ እርስዋ ለመነላት ። መጸለይ የማይችለውንና ችግር እንዳለበት እንኳ የማያውቀውን እብድ ጌታ ተለመነው ። ስንት ምንጮች ሲደርቁ ደምዋ ያልቆመውን ሴት በልብሱ ዘርፍ ፈወሳት ። የሞተችውም በሚጸልይላት አባት ተነሣች ። ሰውዬው ባይናገርም መልኩ ይናገራል ። እግዚአብሔር አይቶም ይለመናል ። የሚገድለው ችግር ሳይገድላት ተንቀሳቃሽ ሬሳ ያደረጋትን ያቺን ሴት የደም ምንጭዋን አነጠፈላት ። “ደህና ሁኑ” ያለችውን ሟች “እንዴት አረፈዳችሁ ?” እንድትል አበቃት ። እርሱ ሲመጣ መለመን ፣ ፊቱን ሲያበራ ደጅ መጥናት መፍትሔ አለው ። 

እብዱ በጣም ይጮኻል ፣ ደም ይፈስሳት የነበረችው ሴት ወደ ውስጥ ትጮኻለች ። ወለተ ኢያኢሮስም ከብበው የሚጮኹላት ብዙ አልቃሾች ነበሩአት ። ለራሱ የሚጮኸውን ፣ ወደ ውስጥ የሚጮኸውንም ፣ ሌሎች የሚጮኹላቸውንም ሁሉንም በዓይነ ምሕረት አየ ። ያ ጌታ ዛሬም ይመልከተን ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

ኅዳር 27 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም