መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (11)

የትምህርቱ ርዕስ | ዐርፍ ዘንድ ተወኝ (11)

“አቤቱ ፥ ፍጻሜዬን አስታውቀኝ ፥ የዘመኔ ቍጥሮች ምን ያህል እንደ ሆኑ ፥ እኔ ምን ያህል ወደ ኋላ እንደምቀር አውቅ ዘንድ ።” (መዝ. 38 ፡ 4) ።

“በሉ እናንተም ሂዱ እኛም ወደዚያው ነን ፣
ወትሮም መንገደኛ ፊትና ኋላ ነው ፤”

ዛሬ የሞተው ሰው ይኑር ብንል አንድ ቀን መሞቱ አይቀርም ። ሞት የማይቀር የሰው ዕጣ ነው ። የሰው ልጅ አእምሮው ለሞት ስለተሸነፈ ለበሽታ መድኃኒት ሲፈልግ ፣ ለሞት ግን መድኃኒት ለመፈለግ አልተነሣም ። ሁሉን ያስተካከለ ሚዛን ሞት መሆኑን እናያለን ። የድሀውን ሞት ባለጠጋው ፣ የምስኪኑን ሞት ንጉሥ ይሞታል ። የመቃብር ስፍራዎችን ስንጎበኝ ከእኛ የተሻሉ ኃያላንና ጠቢባን መቃብር ውስጥ እንዳሉ እናረጋግጣለን ። ነጭ ይለብሱ የነበሩ ሽቅርቅሮችን ስናስብ ዛሬ አፈር/ጭቃ ውስጥ ተኝተዋል ። መሬትን ለመርገጥ ይጸየፉ የነበሩ ዛሬ ድንጋይ ተጭኗቸዋል ። ቤታቸውን አያምኑት የነበሩ ዛሬ ሁሉን ትተው ላይመለሱ ባዶ እጃቸውን ከቤታቸው ወጥተዋል ። በሕይወት ዘመናቸው ይጨነቁለት የነበረው ነገር ፣ እኔ ከሌለው ይህ ነገር ምን ይሆናል ? ከሌለሁ እገሌም ቆሞ አይሄድም ሲሉ የነበሩ እነርሱ ሞቱ እንጂ ሕይወት እየቀጠለ ነው ። በሽታዬን አይስማ ቀድሞኝ ይሞታል ብለው ሲታክቱ የነበሩ ሞታቸው ተሰምቶም ነገሮች እየቀጠሉ ነው ። እርግጥ ነው ከሞተ ጋር የሞተ አላየንም ። ሁሉም የራሱን ምጽአት ወይም ዕለተ ሞቱን ይጠብቃል።

የሕንዱ የነጻነት መሪ የነበሩት ማኅተማ ጋንዲ፡- “ተስፋ መቍረጥ ሲሰማኝ በታሪክ ሁሉ ምንጊዜም የፍቅር መንገድ ማሸነፉን አስባለሁ ። ጨካኞችና ነፍሰ ገዳዮች ነበሩ ፤ ለጊዜው የማይደፈሩ መስለው ይታያሉ ። ሆኖም በመጨረሻ ሁልጊዜም ይወድቃሉ ። አስታውሱ !! ሁልጊዜ!!” ብለዋል ። ሶቅራጥስም፡- “በዚህች ምድር ሁሉም ነገር ያልፋልና ስታገኝ ከልክ በላይ አትደሰት ፣ ስታጣም አብዝተህ አትከፋ” ብሏል። መጽሐፍ ቅዱስ በእያንዳንዱ ክፍል ይህን ያረጋግጥልናል ። የዘፍጥረት መጽሐፍ ሁሉም ነገር ጅማሬ እንዳለውና ወደ ተጻፈለት ግብ እንደሚጓዝ ይነግረናል ። የዘጸአት መጽሐፍ ኃያላን ሰጥመው ድሆች እንደሚሻገሩ ያወሳል ። የዘሌዋውያን መጽሐፍ በሚያልፍ ዕድሜ የማያልፈውን እግዚአብሔር ስለማገልገል ይተርካል ። የዘኁልቍ መጽሐፍ በእግዚአብሔር የታወቅን ፣ የራስ ጸጉራችንም የተቆጠረ መሆኑን ይተነትናል ። የዘዳግም መጽሐፍ እኛ ስናልፍ ትውልድ እንደሚቀጥል ይገልጻል። የኢያሱ መጽሐፍ ሁሉም ነገር በጊዜው ፍጻሜ እንደሚያገኝ ያስተነትናል ። የመሳፍንት መጽሐፍ ሁሉም መሪ የሆነበት አገር እንደሚፈርስ ያትታል ።

የሩት መጽሐፍ ለሚያልፍ ችግር የማያልፍ ሕይወትን ማጣት እንደማይገባ ያስረግጣል ። የሳሙኤል መጽሐፍ አህያ ፈላጊ ሳኦልን ፣ እረኛውን ዳዊት ያከበረውን እግዚአብሔር በመግለጥ ትልልቆች ሁሉ የጀመሩት ከትንሽ መሆኑን ያብራራል ። የነገሥት መጽሐፍ አገርን የሚመራ እግዚአብሔር መሆኑን ይገልጣል ። የዜና መዋዕል መጽሐፍ ስለ አገርና ስለቤተ ክርስቲያን ደግ ደጉን ብቻ ማሰብ እንደሚገባ ያትታል ። የዕዝራ መጽሐፍ እግዚአብሔር ከሰጠን ስጦታዎቻችን አንዱ ደራስያን/መጽሐፍ የሚጽፉ መሆናቸውን ያስተምራል ። የነህምያ መጽሐፍ አገር ፈርሶ በለማ ከተማ ቢኖሩም ልብ እንደማያርፍ ይገልጻል ። የአስቴር መጽሐፍ እኔ የማስፈልገው ለማን ነው ? የሚለውን ጥያቄ ያነሣል ። የኢዮብ መጽሐፍ የተዋረደው ሁሉ የከበረ እንደነበር ይናገራል ። የዳዊት መዝሙር እግዚአብሔርን በሕይወት ውጣ ውረድ ሁሉ መጠጋት እንደሚገባ ያስረግጣል ። የምሳሌ መጽሐፍ ከሰው ጋር መኖር መቻል ትልቅ ጥበብ መሆኑን ይገልጻል ። መጽሐፈ መክብብ ደስታም ኀዘንም ሁሉም ያልፋል ፣ የአሁኑ የመጨረሻ አይደለም ይለናል ። የሶቅራጥስ አሳብም ከዚህ ከመክብብ መጽሐፍ ይቀዳል ።

ብዙ ሰው የሚናገረው ነገ አንደበቱ እንደሚታሰር ሆኖ አይደለም ። ብዙ ሰው የሚሮጠው ነገ እንደሚቆም ዘንግቶ ነው ። ብዙ ሰው የሚጨነቀው ሞት የሚባል ጥሪ እንዳለ ረስቶ ነው ። ሰው ሞት እንዳለ እያሰበ ቢራመድ አይደናቀፍም ። ትልቁ ሞኝነት ወዳጅን እየቀበሩ እኔ አልሞትም ብሎ ማሰብ ነው ። ልጅን እየቀበሩ ገና ግፍ የሚሠሩ ወላጆች መኖራቸው ይገርማል ። ሞቱን የሚያስብ ትልቅ ጠቢብ ነው። የቀረን ዘመን በጣም አጭር ነው ። የምንዘገየው ለጥቂት ቀን ነው ። ስለዚህ አንደበታችንን መጠበቅ አለብን ። ዘግይቶ የተፈታው አንደበት ቀድሞ ይዘጋልና ለአንደበታችን ጠንቃቃ መሆን ይገባናል ። ነቢዩ በየቀኑ ካለው ተናግሮ አናጋሪ ማረፍ ስለፈለገ “ጥቂት ተወኝ” ብሎ ለመነ ።

“እኔ መንገደኛ ተሸኝቶ አዳሪ ፣
ምን ክፉ አናገረኝ እንግዲህ ከቀሪ ፤

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 30 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም