መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (20)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (20)

13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ሠ)

9. ቋንቋ አትቀላቅል

ቋንቋ በባቢሎን ርግማን ፣ በበዓለ ሃምሳ በረከት ሆኗል ። ብዙ ቋንቋ ማወቅ በጣም ጠቃሚ ነው ። በቋንቋ ውስጥ የሰው ልጅ ባሕል ፣ ፍልስፍና ፣ ታሪክ ፣ ቅኔና የተፈጥሮ ውበት አለ ። ቋንቋ ወደ ብቃት ሲሄድ ሥዕላዊ እየሆነ ይመጣልና ተፈጥሮ የዚህ ሥዕል ቡሩሽና ቀለም ነው ። ቋንቋ ወንዝ ስለሚያሻግር ብቻ ሳይሆን ጠቃሚ ስለሆነም ፣ አእምሮንም ስለሚያሰፋ ማወቅ ወሳኝ ነው ። የሰው ልጅ እስከ ሰባት ዓመት ዕድሜው ብዙ ቋንቋ የማወቅ ዕድል አለው ። ልጆችን የአራትና የአምስት ቋንቋ ባለቤት ማድረግ ይቻላል ። ቋንቋ ፍላጎት ፣ በድፍረት መናገርና ብዙ ማውራት ፣ ብዙ ማዳመጥ ካለ በቀላሉ እየታወቀ ይመጣል ። ቋንቋ ራሱን የቻለ እውቀት በመሆኑ አማርኛ ስለምንናገር አማርኛ እናውቃለን ማለት ላይሆን ይችላል ። የቋንቋውን ግሡን ፣ ሥሩን ፣ ሰዋስዉን ፣ ከፍና ዝቅ ፣ ጠበቅና ላላ የሚለውን ድምፁን መለየት አስፈላጊ ነው ። ቋንቋ በማንበብና በመጻፍ ሲዳብር የበለጠ የዝምታ ንግግር እየሆነ ይመጣል ። ማንበብና መጻፍ በዝምታ ያለ ፍንዳታ ነው ። የቋንቋ ብቃቱ ማንበብና መጻፍ ከሆነ የመናገር መጨረሻው ዝምታ ነው ማለት ነው ።

አያሌ ቀጣፊዎች ብዙ ቋንቋ የማወቅ ጥማት አላቸው ። ቅጥፈት ዓለምን የሚያጠብብ ፣ በሁሉ ቦታ ስደተኛ የሚያደርግ ነውና እነዚህ ሰዎች ብዙ ቋንቋ ያጠናሉ ። ብዙ ቋንቋ መሰብሰብ በውስጡ እውቀትንና ፍልስፍናን ማዳበር ካልተቻለ ልብን ቀውላላ ያደርጋል ። አንድን ነገር በደንብ ተረድቶ ያንን ማብሰል ፣ የበሰለውን ለትውልድ ምግብ አድርጎ ማቅረብ የሰው ልጅ ክብሩ ነው ። አዎ ብዙ ቋንቋ ብታውቅም ስትናገር አትቀላቅል ። በፍርድ ቤት የቆመ ተጠያቂ ቋንቋ እየቀላቀለ ቢናገር የፍርድ ሂደቱን እንደማሳት ስለሚቆጠር አንዱን መምረጥ ፣ ወይም አስተርጓሚ ማቆም አለበት ። የእያንዳንዱ ቀን ውሎአችን ጥንቃቄ የሞላበት ሊሆን ይገባዋል ። በአንድ ሰከንድ ስህተት መላው ዕድሜ ሊታጣ ይችላል ። ይልቁንም ያውቃል እንዲባል አንድ ሰባኪ ቋንቋ እየቀላቀለ ማስተማር አይገባውም ። ዓላማው ሰዎችን ስለ እግዚአብሔር ለማሳወቅ እንጂ ስለ ሕዝቦች ቋንቋ ለማስጠናት አይደለምና ሰባኪ ቋንቋ መቀላቀል አይገባውም ። በእግዚአብሔር ቤትም ዲያቆን ፣ ቀሲስ ፣ ብፁዕ አባታችን ከመባል የበለጠ ማዕረግ የለምና ዶክተር ፣ ኢንጂነር እገሌ እየተባለ መድረኩን ባያጣብብ ፣ አልተማሩም የሚባሉት ላይ የመብረቅ ሸክም ባይሆን መልካም ነው ። በሰለጠነውም ዓለም የትምህርት መጠሪያዎች የስም ማሳመሪያ አይሆኑም ። እኛ አገር ሥራውን ፈጽሞ ወደ አገሩ የተመለሰውን ሳይቀር “አምባሳደር እገሌ” እያልን እንጠራለን ። የስም ጥማታችን ወደር የለውም ።

ስም የሚያበዙ ሰዎች ሥራ የላቸውም ። ሰው ስሙና ልብሱ ካልቀለለው ሥራ መሥራት አይችልም ። የእግዚአብሔር አደባባይ የእኛ የሕይወት ታሪክ መንገሪያ አይደለም ። “መልከ ጥፉ በስሙ ይደግፉ” እንዲሉ ብዙ ሥራ ስለሌለን ስም ማብዛት ሥራ መስሎናል ። እኛ ረጅሙን መወዳደስ በምናቀርብበት ቅጽበት አንድ ምእመን በተኩላ እየተነጠቀ ነው ። በየትም ዓለም አገልጋዮች ሠርተው ያሠራሉ ። ሠርተው ይደነቃሉ ። በእኛ አገር ግን ሥራ ጥለን ወሬን ገንዘብ አድርገን ፣ ድሀ ባስገባችው በስእለት ገንዘብ እንወዳደራለን ። የዚህ ውጤቱን እያየነው ነው ። በቶሎ ካልነቃን ላይድን እንቆስላለን ። አልጀሪያ ወይም ሂፖ የቅዱስ አውግስጢኖስ መንበር ነበረች ፣ ዛሬ የክርስትና ምልክት የላትም ። ቱኒዚያ የጥንትዋ ካርቴጅ ብዙ ቀኖና የተሠራባት የክርስቲያን አገር ነበረች ። ዛሬ የለችም ። ሊቢያ ወይም ቀሬና ብዙ ጳጳሳት ያስተዳደርዋት ትልቅ የክርስቲያን መዲና ነበረች ዛሬ የለችም ። የኑቢያ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ ህልውና የነበራት ቤተ ክርስቲያን ነበረች ። ዛሬ የለችም ። ግብጽም ክርስትና የተስፋፋባት አገር ነበረች ። ዛሬ ክርስቲያን ተሸማቆ የሚኖርባት ፣ ከአገሩ ሕዝብ ቍጥርም ጥቂት ክርስቲያን ያለባት አገር ሆናለች ። የአገሬ ካህን በጊዜ ንቃ ። ለማልቀስም ዕድል ላይገኝ ይችላል ። እረኛ ይጠብቃል እንጂ ተኩላን ሲረግም አይውልም ።

አዎ ንግግርህ ክብር እንዲኖረው ፣ ካንተ የሚበልጥ ጸጋና እውቀት ያለው እንዲያደንቀው ቋንቋ አትቀላቅል ። “ይህን አማርኛ ጌታ ይገሥጸው” ያለ ፓስተር ሰምቻለሁ ። እንደ እርሱ አነጋገር የሚገልጥለት እንግሊዝኛ ነው ። “አባቱን አያውቅ አያቱን ናፈቀ” የሚባለው እንዲህ ላለው ነው ።
ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 30 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም