የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 
መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (23)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (23)

13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ሸ)

15. የማይወሩ ነገሮችን ለይ

አፋችን በተፈጥሮው መክፈቻ ብቻ ሳይሆን መዝጊያ ተበጅቶለታል ። ጥርስን የሚያህል የብረት አጥር ፣ ከንፈርን የሚያህል የሚሞቅ ምንጣፍ ተደርጎለታል ። ንግግርን ጨዋና ልከኛ ለማድረግ መንፈሳዊነት ፣ ጨዋ አስተዳደግ እጅግ ወሳኝ ነው ። አንዳንድ ሰዎች ዕድሜአቸው ቀላል አይደለም ፣ ነገር ግን የሚያወሩትን ነገር ማጥለል አይችሉም ። ዕድሜ አይለውጥም የሚባለው ለዚህ ነው ። ልጆችን ስናሳድግ የቱ እንደሚወራ ፣ የቱ የት ቦታ እንደሚነገር ፣ የቱ ፍጹም እንደማይወራ ማሳወቅ አለብን ። ይህ የአስተዳደግና የመንፈሳዊነት ክፍተት ዛሬ በጉልህ እየታየ ነው ። እኛ ኢትዮጵያውያን የተደበቀውን ማንነታችንን ማኅበራዊ መገናኛ እያወጣው ነው ። ሊነገሩ የማይገባቸው ነገሮች ብዙ ናቸው ። ጥቂቱን ማየት ብንችል መልካም ነው ።

ለሰዎች ያደረግነውን ውለታ ማውራት ፍጹም አይገባም ። ለራሳቸው ለሰዎቹ ይህን አድርጌልህ ነበር ማለት አስፈላጊ አይደለም ። ሰው በጠባዩ የሰጠውን አይረሳምና የዛሬ ሠላሳ ዓመት እንዲህ አድርጌልህ ነበር እያለ ሲያወራ ራሱን ያቀላል ። ሰዎች ውለታቸውን የሚያወሩት በተለያየ መንገድ ነው ። ውለታቸውን ለራሱ ለዋሉለት ሰው የሚናገሩት የመጀመሪያው ያ ሰው እንደ ጠላቸው ሲያስቡ ነው ። ሁለተኛው ከዚያ ሰው ጋር ያላቸው ግንኙነት መጨረሻ ላይ ሲደርስ ነው ። ሦስተኛው “ሰው በክፉ ይስለኛል እንጂ እኔ ቸር ነኝ” ለማለት ነው ። ሰውዬውን ለማገዝ ያደረግነውን ነገር ሰውዬውን ለማሳቀቅ ማዋል ፣ በማንኪያ ሰጥቶ በአካፋ መውሰድ ነው ። ሥጋውን ጠግኖ ነፍሱን ማፍረስ ነው ። ስጦታችን ልብንም ሥጋንም የሚጠግን መሆን አለበት ። በዚህ ዓለም ላይ ይዘን የመጣነውና ይዘን የምንሄደው ምንም ነገር የለም ። የሰጠነው የእኛ ያልሆነውን ሀብተ ሥላሴ የሆነውን ነው ። ደግሞም አንድ ቀን ትተነው ስንሄድ ተዝካራችንን እያወጡ ወስኪ ይራጩበታል ። ከመዝራት ይልቅ ገንዘባችንን ይበትኑታል ።

የማይወራ ነገር ሰዎች የነገሩን ምሥጢር ነው ። ምሥጢርን መሸከም የማይችል ሰው ጠባየ ቀላል የሆነ ሰው ነው ። ጓደኛ ለጓደኛው ልክ እንደ ንስሐ አባት ምሥጢሩን ሊደብቅለት ይገባል ። ምሥጢሩን የነገረን ሰው በምድር ላይ ከሚያከብሩን ሰዎች ቀዳሚው ነው ። የሰውን ምሥጢር ማውጣት ራስን ማዋረድ ነው ። “እገሌ ወሬ አያድርለትም/አያድርላትም” መባል ትልቅ ስድብ ነው ። ይልቁንም ሁለት ሆነን የሠራነውን ነገር ስንጣላ ማውጣት ተገቢ አይደለም ። ስንፋቀር ሌላውን ሰው ሸሽተን ነበር ። አሁን ስንጣላ ግን የዕድር ጡሩንባ ማስነፋት ፣ ስሙልኝ ማለት ተገቢ አይደለም ። ሰዎች ለሰርጋቸው ድምፁ በማይሰማ ወረቀት ይልካሉ ። ልቅሶአቸውን ግን በጡሩንባ ያስለፍፋሉ ። ዛሬ በአደባባይ የምንሰማው የትዳር ምሥጢር ፣ የባከነው የቤት ገመና የማኅበረሰቡን ውድቀት የሚያሳይ ነው ።

የአገር ምሥጢርን ማውጣት በአንገት ላይ ሰይፍ አንጠልጥሎ እንደ መዞር ነው ። በራሽያ ፣ በእንግሊዝ የተደበቁ የአሜሪካንን ምሥጢርን ያወጡ ሰዎች እንዳሉ እናውቃለን ። የአገር ምሥጢርን ያወጡ ሰዎች ምሥጢሩን ካወጡ ቀን ጀምሮ ሞት ጥላ ሁኖ ይከተላቸዋል ። ምሥጢር ከጠበቅነው ይጠብቀናል ። ካባከነው አሳዳጃችን ይሆናል ። ከዚሁ ጋር የግላችንንም የቤታችንንም ምሥጢር ለማይችል ሰው መንገር ጥፋቱ የእኛ ነው ። ለመንፈሳዊ አባት ግን የማይነገር ምሥጢር ያለ አይመስለኝም ። ሰይጣን ለመንፈሳዊ አባት ድብቅ እንድንሆን በማድረግ ለትልቅ ውድቀት ይዳርገናል ። አባቶች፡- “ሞኝ ለጠበቃው ምሥጢር ይሸሽጋል” እንዲሉ ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም