መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (33)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (33)

18. ስፖርት

ከሕይወት ሥነ ሥርዓቶች አንዱ ስፖርት ማዘውተር ነው ። ለታላቁ ሩጫ በዓመት አንድ ጊዜ መሮጥ ፣ ለፎቶ እንጂ ለጤና ምንም ጥቅም የለውም ። የሰውነት እንቅስቃሴ ዕለታዊ ግዳጅ ነው ። እጅ ለመሥራት ፣ እግር ለመራመድ እስከ ተሠራ ድረስ መሥራትና መንቀሳቀስ አስፈላጊ ነው ። አሊያ የሞት ጎረቤት ፣ የበሽታ ዳስ ሆኖ መኖር ነው ። “መቀመጥ ቆመጥ ነው” እንዲሉ ። ዘመናዊነት ከጎዳን ነገር አንዱ የስንፍና ሠራዊት ማብዛቱ ነው ። ከምግብ እንኳ የሚታኘክ አንፈልግም ። በፋብሪካ ተቀነባብሮ ፣ ልሞ ፣ በሚሳብ መልክ መውሰድ ነው ። ይህ ጥርስ ያላወጡ ፣ ምግብ ያለመዱ ሕፃናት ይወስዱት የነበረ ነው ። ተፈጥሮአዊ ሂደቱን ጠብቆ ምግብን መመገብ ብዙ ጥቅም አለው ። መዓዛውን ፣ ጣዕሙን እንድናውቅ ያደርገናል ። ጥርሳችን ጥንካሬ ያገኛል ። ምግብን የሚፈጀው የአካል ክፍልም እየመጣ ላለው የምግብ ዓይነት ዝግጅት ያደርጋል ። ከጠዋት እስከ ማታ ከመቀመጫቸው የማይነሡ የቢሮ ሠራተኞች አሉ ። ሻይ ቡና እዚያው ጠረጴዛቸው ላይ ይመጣላቸዋል ። በየተቋማቱ ሻይ ቡና በእግር ተጉዘው ከሚጠጡበት ቦታ መዘጋጀት አለበት ። አንድ ተቋም የሠራተኞቹን ጤና መጠበቁ ለራሱም ህልውና ወሳኝ ነው ። መንግሥት በከፍተኛ ሁኔታ ሆስፒታሎችን መገንባት ሥራው ነው ። መድኃኒት በውጭ ምንዛሪ ወደ አገር ያስገባል ። ዜጎችም ከአገር ወጥተው በውድ ገንዘብ ይታከማሉ ። በዚህም ውጤቱ አነስተኛ ነው ። የስፖርት ማዘውተሪያዎች በየሰፈሩ ቢገነቡና ጤናማ ማኅበረሰብ መገንባት ቢቻል የአገር ወጪ ይተርፍ ነበር ። ችግርን ከሥሩ መከላከል ውጤታማ ያደርጋል ።

በአገራችን የአንድ ትልቅ ቤተሰብ የልጆች አስተዳደግ የሚያሟላው አራት ነገሮች ነበሩ፡- ትምህርት ፣ ግብረ ገብ ፣ ስፖርትና የዜማ መሣሪያ ማወቅ ናቸው ። ትምህርት ስለ ራሱና ስለሚኖርበት ዓለም ግንዛቤ ይሰጠዋልሰ ። ግብረ ገብ ከራሱና ከሰዎች ጋር የሚኖርበት ትልቁ የመኖሪያ ፈቃድ ነው ። “የሰው አገሩ ምግባሩ” እንዲሉ ። ስፖርት ንቃቱን ፣ ጥንካሬውን የሚጠብቅበት ነው ። የዜማ ዕቃ ፈጣሪውን የሚያመሰግንበት ፣ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚያደርስበት ነው ። ይልቁንም ዕድሜ እየገፋ ሲመጣ ወዳጅ እያነሰ ይመጣልና የዜማ ዕቃ ጓደኛም ነው ። የሰውነት እንቅስቃሴ ከተሟላ አስተዳደግና አኗኗር የሚደመር ነው ። በዚህ ዘመን ስፖርት የሚመለከቱ ብዙ የዓለም ሕዝቦች አሉ ። እንደውም አንድ አባት እንዳሉኝ “ከእግዚአብሔር በላይ ኳስ ተከታይ አለው ።” ኳስ መመልከቱ ያን ያህል ስህተት አይደለም ። ከአምልተ እግዚአብሔር ፣ ከትዳራችን ፣ ከማኅበራዊ ግዳጃችን ከበለጠብን ግን አደገኛ ጣዖት ነው ። “የመጀመሪያውን ስብከት ለእኔ ስጡኝ ፣ የማንቸስተር ጨዋታ አለብኝ” ያለ ሰባኪ እንዳለ ሰምተናል ። እነዚህ የሚያስተምሩት በሥጋ በነፍስ ቢደነቁር አስደናቂ አይደለም ። ቤተ ክርስቲያን የሚቆጭላት አጥታ ቁማር መጫወቻ ከሆነች ቆይታለች ።

ስፖርት ማድነቅና ስፖርት መመልከት ለጤናችን ምንም የሚያደርገው አስተዋጽኦ የለም ። የሚደግፉት ቡድን በመሸነፉ ራሳቸውን ያጠፉ ወጣቶችን በቅርብ ጊዜ ሰምተናል ። የድሀን ቅብጠት የሀብታም አገር በጀት አይችለውም ። ለእውነቱ ካየነው በአገራችን መወራት ያለበት ሰው ስለ መሆን ፣ እንጀራ ስለ መብላት ፣ ስለ ንጽሕናን አጠባበቅ ነው ። የሚገርመው ስፖርት አድናቂዎች ጠጪዎች ናቸው ። የሰውነት ቅርጻቸው የተበላሸ ነው ። የሚደግፉት ቡድን ካሸነፈ በደስታ ይጠጣሉ ፣ ካላሸነፈ በንዴት ይጠጣሉ ። የስፖርት ደጋፊዎች ግብ መጠጥ መጠጣትና ለመጠጡ ምክንያት ማበጀት ነው ። የምናደንቃቸው ስፖርተኞች በብዙ ሚሊየን ዶላር የሚከፈላቸው ሲሆኑ ለእነርሱ ሥራቸው ነው ። እነርሱ ኢትዮጵያ የምትባል አገር መኖርዋን እንኳ አያውቁም ።

ስፖርት የምንሠራው ለተስተካከለ ቅርጽ ቢሆንም ፣ ቅርጻችንን ስናሳይ ለመዋል ግን አይደለም ። ይህ ራስን ማምለክ በመሆኑ በበሽታና በውድቀት ሳይቀጣ አይቀርም ። እዩኝ እዩኝ ያለ ገላ ደብቁኝ ደብቁኝ ይላል ይባላል ፤ ደግሞም እውነት ነው ። ይህ ሕግ ነው ፣ የገዛ አካላችንም ጣኦት ሆኖብን ላስመልክ ካልን በቍስል ይመታል ። ዛሬ ቅርጻቸውን አሳምረው ሀብታም ሴት የሚጠብቁ ድኩማን ወንዶች እያመረትን ነው ። ኤልያብ ተቀምጦ ዳዊት ለንግሥና የተመረጠው ቁመና መስፈርት ስለማይሆን ነው ። ቁመና እያዩ ሹመትና ማዕረግ የሚሰጡ አባቶች አሉ ። ይህ አዲስ አይደለም ነቢዩ ሳሙኤልም የተታለለበት ነው ። “እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፦ ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት ሰው ፊትን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል አለው።” (1ሳሙ. 16 ፡ 7) ። ቁመናን እያያችሁ ባል የምታስሱ እኅቶች ከተሰናዱ ሌቦች ራሳችሁን መጠበቅ አለባችሁ ። ሰው ስፖርት የሚሠራው ለራሱ ነው ። ስለዚህ እዩልኝ እያሉ ቪዲዮ መልቀቅ ምን የሚሉት ነገር ነው ? መጽሐፍ እያነበበ ቪድዮ የሚለቅ የለም ። የመጀመሪያው መጽሐፍን እንደ እርግጠኛ ጠላታችን ነው የምናየው ። ሁለተኛው መጽሐፍ የሚያነብ ሰው እዩልኝ ስሙልኝ የሚል ኑሮ የለውም ። ራስን የመሸጥ ግርግር ውስጥ ያለው ይህ ዘመን በድሀ ሕዝብ ፊት ቍርሳቸውን እየበሉ የሚለቅቁ ፣ መኖር ባቃተው ወገን ፊት እየተገላበጡ ከየጂሙ ፎቶ የሚሰድዱ ጨካኞችን ያፈራ ነው ።

አንተ ግን የሰውነት እንቅስቃሴ አድርግ ። ግድ ጂም መግባት አያስፈልግህም ፣ የራስህ ሰውነት የስፖርት መሥሪያም ነው ። ታክሲ ለመጠበቅ አንድ ሰዓት ከመቆም አንድ ሰዓት ተራምደህ እቤትህ ግባ ። በየጂሙ ያለው ወሬና የነጋዴዎች ትውውቅ ፣ ለመቼ ቀን እንደሆነ ባይታወቅም የሰቡ ጎረምሶች የሚታዩበት ነው ። ሌላው ይሥራልኝ ብለህ የተውከው ተግባርህ በራሱ ስፖርት ነው ። ከተፈጠርንበት ሥሪት እየራቅን ስለሆነ ታላቅ የጤናና የሥነ ልቡና ጉዳት ውስጥ ገብተናል ። አንተ ግን በየቀኑ ቢያንስ ለአንድ ሰዓት ያህል የእግር ጉዞ አድርግ ። ከመኝታህ ከመነሣትህ በፊትና በተነሣህ ጊዜ መንጠራራት ፣ ሰውነትህን ማፍታታት አትርሳ ። የትንፋሽ ስፖርት ብቻ ሳይሆን የጥንካሬ ስፖርቶችንም ልመድ ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 17 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም