መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት ( 45 )

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት ( 45 )

አዎንታዊ ሥነ ሥርዓት ይኑርህ /2

ሰዎች “ሥነ ሥርዓት ይኑርህ” ብለው ከተናገሩ ቍጣ ላይ እንዳሉ ግልጽ ነው ። “ሥነ ሥርዓት ይኑርህ” ሲሉም እንዳታጠፋ እያሉ ሳይሆን በጥፋትህ እንዳትቀጥል እያሉ ነው ። ስለዚህ ሥነ ሥርዓት አንደኛ አለማጥፋት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በጥፋት አለመቀጠል ነው ። “ካፈርኩ አይመልሰኝ” የሕይወት ሥነ ሥርዓት አይደለም ። መርዝ መጠጣት የጀመረ ሰው ካፈርኩ አይመልሰኝ ካለ ቀጥሎ ሟች ነው ። ሲጨርሱት ክብርና ሕይወት ያለው መልካም ነገር ብቻ ነው። የአገራችን ሰው ጨርሶ ነው የሚኖረው ። ጨርሶ የሚኖር ሰው መማር ፣ መጸጸት ፣ መመለስ ፣ ይቅርታ መጠየቅ አይፈልግም ። ይቅርታ ከምንጠይቅና አንድ ሚሊየን ሰው ከሚያልቅ ብንባል አንድ ሚሊየን ይለቅ የምንል ነን ። ሥርዓተ መንግሥት ብለን እንናገራለን ፣ የመንግሥት ሥርዓት ፣ መንግሥታዊ ሥልጣን ፣ አሁን እየገዛ ያለ ሕግና መሪ ማለት ነው ። ሥርዓት ሥልጣንን ያመለክታል ማለት ነው ። ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ ተብሎ ክስ ሲቀርብ ስንሰማ መንግሥቱን ፣ ሕገ መንግሥቱን ማለት ነው ። ሥርዓት ሥልጣን ነው ። ሥርዓት ያለውን ሰው በቤታችን በሕይወታችን ላይ ሙሉ መብትና አደራ እንሰጠዋለን ። ሥርዓት ለሹመት የሚያሳጭ ፣ ለምሥጢር ተፈላጊ የሚያደርግ ነው ። ሥልጣን ያላቸው ፣ እውቀት ያላቸው ፣ ሀብት ያላቸው ሰዎች ሥርዓት የላቸውም ተብለው ይናቃሉ ፣ ይፈራሉ ። ሥርዓት ያለው ሰው ከበላይ ሁኖ የሚያዝዝ እግዚአብሔርና የሕሊና ሕግ ያሉት ነው ። ሥርዓት ያለው ሰው እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰውን የሚያፍር ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ብቻውን እንዳለ ሰው ቤቱን ፣ መንደሩን ፣ አገሩን አያዝበትም ። የጋራ ዓለም ነውና ። ሥርዓት ሌላውን ማክበር ነው ። ክብርን የምንፈልግ ከሆነ ማክበር አለብን ። የዘሩትን ማጨድ ክብርን የሚመለከትም ሊሆን ይችላል ።

“ማክበር መከበር ነው ፣
መወደድ ነው መውደድ ፣
ላዋርድ ካሉማ ይመጣል መዋረድ”

“በሥርዓት አድርገው” የሚል ምክር ከሰማን በተርታ አድርገው ማለት ነው ። የሚቀድመውንና የሚከተለውን ለይ ማለት ነው ። የሰው ዕድሜ የሚባክነው የሚከተለውን ቀዳሚ በማድረጉ ነው ፣ ለቀዳሚው ደግሞ ጊዜና አቅም ሲያጣ ያን ጊዜ መጨነቅ ይጀምራል ። አስፈላጊ ነገሮች ሁሉ አስቸኳይ አይደሉም ። አስፈላጊውንና አስቸኳዩን መለየት ያስፈልጋል ። ከሥራ በኋላ የሚያጫውተንን ነገር ሥራን ትተን ካደረግነው የሚኖርልን ሌላ ወገን አለ ማለት ነው ። ስልኮቻችንን ማየት ያለብን ከሥራ በኋላ ለጥቂት ጊዜ ነው ። ሙሉ ሕይወታችን እዚያ ላይ ከተጠመደ አእምሮአችን ጤነኛ ፣ ጉልበታችን አምራች መሆን አይችልም ። በሕይወታችን ተርታ ያስፈልገናል ። ሱሪ ሳንለብስ ጫማ ብናደርግ ከመፍጠን ይልቅ መዘግየትን እናመጣለን ። መቸኮል መዘግየት ነው የሚባለው ለዚህ ነው ። ለዛሬ አስፈላጊውና አስቸኳዩ ምንድነው ? ብለን መለየት ፣ ለማያስቸኩለው ነገር ቀጠሮ መስጠት ተገቢ ነው ። ሁሉንም ነገር ዛሬ ካልከወንሁ ማለት ሁሉንም ነገር አለማድረግን ያመጣል ። ለነገም ሥራ ማስቀመጥ አለብን ። ጥንቅቅ ያለ ቤት ፣ የተሟላ የትዳር እሴት ጨብጦ ስለ ማግባት ማሰብ የለብንም ። እያንዳንዱ ነገር በጊዜው ሲሟላ ብዙ ደስታ ለማየት በተርታ ማድረግ ይገባናል ። በድሀ ቤት ብዙ የልብ ሙቀትና ደስታ ያለው ከብዙ ልፋት በኋላ በር ሲቀየር የድል አድራጊነት ስሜት ይኖራል ። ሁሉንም ነገር ስለማሟላት ማሰብ አስፈላጊ አይደለም ። ነገ ላይ ምን ልንኖር ነው ? የአማዞን መሥራች ባለሀብት “ጭንቀት የሥራ ብዛት ሳይሆን መሥራት እየቻልን ያልሠራነው ነገር ነው” ብሏል ።

ዓለም ስትዋቀር በአንድ ቀን ጉዳይን ለመፈጸም ዕድል ያላት ሆና አይደለም ። እግዚአብሔር ከፈቀደ ነገም የእኛ ነው ። ሥራን በጊዜ መፈጸም መልካም ነው ። ሥራን ሁሉ ግን ዛሬ እፈጽማለሁ ማለት ራስን ለጭንቀት መዳረግ ነው ። ይልቁንም ልናደርጋቸው እየቻልን ያላደረግናቸው ነገሮች እንዳፈጠጠ አውሬ በየሰዓቱ ይታዩናል ። የሚገርመው ቆም ብለን እነዚህን ጥያቄዎቼን ልመልስ አንልም ። በማይረባ ነገር ጊዜአችን እየባከነ ለሚያስጨንቀን ነገር መፍትሔ አንፈልግም ። መርዳት እየቻልን የሞቱ ወላጆቻችን ፣ መጠየቅ እየቻልን ናፍቀው የቀሩ ወዳጆቻችን የሕይወት ቅሬታን ያመጡብናል ። ለሚወዱን ቅድሚያ መስጠት የሕይወት ሥነ ሥርዓት ነው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 15 ቀን 2ዐ17 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም