መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 6

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 6

5- ጸልይ

ስታገኝም ጸልይ ፣ ባለህ ነገር ትረካለህ ። ስታጣም ጸልይ ተስፋን ይዘህ ትነሣለህ ። ስትስቅ ጸልይ ፣ ሳቅህን እውነተኛ ያደርግልሃል ። ስታለቅስም ጸልይ ፣ ከኀዘን ሸለቆ ያወጣሃል ። ስትወድድ ጸልይ ፣ ያረፈደው ፍቅር ያመሽልሃል ። ስትቀየምም ጸልይ ፣ ልብህን ያጥብልሃል ። በአገርህ ስትሆን ጸልይ ፣ ከወገን ጠላት ይጋርድሃል ፤ በሰው አገር ስትሆንም ጸልይ ፣ ባዕዱን ዘመድ ያደርግልሃል ። ስታሸንፍ ጸልይ ፣ ጋሻህ እግዚአብሔር ይሆናል ። ስትሸነፍም ጸልይ የእንደገና ዕድል ይሰጥሃል ። ስትደፍር ጸልይ ፣ መለኮት ድጋፍ ይሆንሃል ። ስትፈራ ጸልይ ፣ እምነትን ይሰጥሃል ። ሲሳካልህ ጸልይ ፣ የመኸር ደስታ ታገኛለህ ። ሳይሳካም ጸልይ ፣ ፈቃደ እግዚአብሔር ልብህን ያሳርፈዋል ። አስታመህ ሲድንልህ ጸልይ ፣ ፈውስ የእግዚአብሔር ገንዘብ ናትና ። አስታመህ ሲሞትብህም ጸልይ ፣ ሞት ዕረፍት ነውና ። ደግ ንጉሥ ሲነሣ ጸልይ ፣ ደግ ሰው ዘመኑ አጭር ነውና ። ክፉ ንጉሥ ሲነሣም ጸልይ ፣ ለቅጣት ይላካልና ። ስትቀደስ ጸልይ ፣ ከኃጢአት የሚያድን ኢየሱስ ነውና ። ስትቆሽሽም ጸልይ ፣ በደሙ ያጥብሃልና ። ደም በባሕርይው ያቆሽሻል ። የእግዚእ ኢየሱስ ደም ግን አምላካዊ ደም ነውና ያነጻል ። ደም ሲያዩት ያስደነግጣል ፣ የአማኑኤል ደም ግን መሢሐዊ ደም ነውና የተዘጋውን በር ይከፍታል ።

ተደርጎልህ እንደሆነ የምታመሰግነው በጸሎት ነው ። የሌሎች ጉዳት አስጨንቆህ ከሆነ የምትማልደው በጸሎት ነው ። ኃጢአትህ ከብዶህ ከሆነ ንስሐ የምትገባው በጸሎት ነው ። አጥተህ ከሆነ የምትለምነው በጸሎት ነው ። ጸሎት ለንጉሥ አቤት ማለት ነው ። ጸሎት ለዳኛ ይግባኝ ማለት ነው ። ጸሎት ለሰጪው ጌታ እጅን መዘርጋት ነው ። ጸሎት ለወዳጅ የፍቅር መልእክት መላክ ነው ። ጸሎት ለተዋጊው ጀግና መንገድ መልቀቅ ነው ። ጸሎት ለቤትህ ራስ ጉድለትህን ነግረህ መተኛት ነው ። ጸሎት ምግበ ሥጋ ፣ ምግበ ነፍስን የምንጠይቅበት ነው ። ጸሎት ወደ ሰማይ መደወያ ቍጥር ነው ። ጸሎት የሃይማኖት መሣሪያ ነው ። ጸሎት ሀልወተ እግዚአብሔርን የምንመሰክርበት ነው ።

ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ መጸለይ ነው ። ስለዚህ አፍ ከልብ ሆነህ ፣ ስፍራና ጊዜ ለይተህ በማለዳና በምሽት ጸልይ ። ከበረታህ በሃያ አራት ሰዓት ሰባት ጊዜ ጸልይ ። ከቤትህ ስትወጣ የመንገድ ጸሎት ፣ ስትመገብ የማዕድ ጸሎት አትርሳ ። ወደ ወዳጅህ ቤት ስትሄድ ፣ ደግሞም ስልክ ስትደውል ጸልይ ። የእግርህ ኮቴ እንዲናፍቀው ያደርጋል ። ወደ ሥራ ስትገባና ሥራህን ስትጀምር ጸልይ ። ሐኪም ሆነህ እንደሆነ ሳትጸልይ በሽተኛ አትንካ ። እውቀቱን የሰጡህ ፈረንጆች ቀዶ ጥገና ከማድረጋቸው በፊት ተንበርክከው ይጸልያሉ ፣ “አንተም በእምነትህ ጸልይ” ብለው በሽተኛውን ይጠይቃሉ ። የአገሬ ሐኪም ሬሳ የምታመርተው ስለማትጸልይ ነው። ሠራተኞችህ ሊጋጩህ ሲፈልጉ ዘወር ብለህ ጸልይ ፣ ሚስትህ ለግጭት ስትፈልግህ በልብህ ጸልይ ። በማለዳ አፍህን በጸሎት ሳታሟሽ ከሚስትህም ጋር ቢሆን አትነጋገር ። ላንተ ማንጋት አልረሳምና በማለዳ ተነሥተህ አመስግን ። ታርፍ ዘንድ ላንተ ማስመሸት አልረሳምና ሲመሽ ጸልይ ። በመንገድ ስትሄድ ፣ ብቻህን ስትሆን ፣ ወደ መታጠቢያ ሄት ስትገባ ፣ ገላህን ስትታጠብ ጸልይ ። ከጸሎት ሁሉ አውራው “እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ – አቤቱ ክርስቶስ ሆይ ማረን” የሚለው ነው ። ያለማቋረጥ ይህን ጸሎት ጸልይ ። ፈተናና ትግሉ ሲበዛ መዝሙር 22ን እግዚአብሔር እረኛዬ ነው የሚለውን ደጋግመህ ጸልይ ። ደግሞም ጸሎተ ማርያምን ታዐብዮ ነፍስዬን- ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች የሚለውን ደጋግመህ ጸልይ (ሉቃ. 1፡47-55)። የመቍጠሪያ ጸሎት እጅግ ጠቃሚ ነው ። ከመዝሙረ ዳዊትም በጸሎትህ ደባልቅበት ። የልብህን ሙቀት ለጌታህ አፍስስለት ።

የግል ጸሎት ፣ የቤተሰብ ጸሎት ፣ የማኅበር ጸሎት እንዳለ አስታውስ ። የአጋንንት ፍላጻ ሲበዛ መዝሙር 90ን ደጋግመህ ጸልይ ። “በልዑል መጠጊያ የሚኖር…” የሚለውን ማለቴ ነው ። አባቶችህ ስታገኝ ጸሎት ተቀበል ። አንተም ትባረካለህ ፣ እነርሱንም ታተጋለህ ። በማለዳ ጸሎትህ ላይ ውኃ በብርጭቆ አድርገህ ጸልይ ። ራስህንና ቤተሰብህን በተባረከው ውኃ ቀድስ ። ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ስላገኘህም ጸልይ ። የሚፈልጉትን የማያውቁና የሚፈልጉትን ያጡ በዓለም ላይ አሉ ። የሚያድናቸው ጸሎት ብቻ ነው ። ወደ ወዳጅህ ቤት ስትገባ ሳትቀመጥ ጸሎት አድርሱ ። ወደ ቤተ ክርስቲያን ስትገባ ሳትቀመጥ ጸሎት አድርስ ። ወደ ጉባዔ ስትሄድ በቃሉ እንዲናገርህ ጸሎት አድርስ ። በታላቅ መከራ ውስጥ ስትሆን ዝም ብለህ ጸልይ ። ጌታ በመስቀል ላይ ሆኖ ጸልዮአልና ። ጸሎት ለሥጋዊ ጤና ፣ ለአእምሮ መታደስ ፣ ለመንፈስ እረፍት ወሳኝ ነውና ጸልይ ። እባክህ ጸልይ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 21 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም