መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የመጠመቁ ምሥጢር

የትምህርቱ ርዕስ | የመጠመቁ ምሥጢር

እንኳን ለ2016ዓ.ም. የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በሰላም አደረሳችሁ!

ጌታችን ለሦስት ዓመት አገልግሎት ሠላሳ ዓመት ተሰወረ ። ሙሴ ለአርባ ዓመት አገልግሎት ሰማንያ ዓመት ተዘጋጀ ። በዚህም ምክንያት የ430 ዘመን የባርነት ሸክም እንዲቃለል እግዚአብሔር ተጠቀመበት ። ዝግጅቱ ከሰፋ ውጤቱ ብዙ ይሆናል ። ዝግጅቱ ካነሰ ውጤቱም አናሳ ይሆናል ። ጌታችን ለእኛ አርአያ ለመሆን ሠላሳ ዓመት ተሰወረ ፤ ሦስት ዓመት አገለገለ ። የጌታችን ጥምቀት የመገለጥ ዘመን ነው ። ዘመኑም ዘመነ አስተርእዮ ይባላል ። በርግጥ መላው ዘመነ ሥጋዌ ዘመነ አስተርእዮ ቢሆንም ሠላሳ ዓመት ተሰውሮ የነበረው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅነቱን የገለጠው በጥምቀት ነውና አስተርእዮ ይባላል ። አዳም የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ሁኖ ተፈጥሮ ፣ ልጅነቱን አጎሳቍሏልና ክርስቶስ በሠላሳ ዓመቱ ልጅነት የምታሰጠውን ጥምቀት ሊመሠርት መጣ ። አምላክ ሲያዝዝ ልዩ ነገር እንዳለ ማሰብ ግድ ይላል ። ጥምቀት ግን ራሱ ባለቤቱ አርአያ የሆነበት ነውና ትልቅ ምሥጢር ነው ። ጥምቀት በመልእክተኛ ፣ በነቢይ በሐዋርያ ሳይሆን በክርስቶስ መመሥረቱ ታላቅ ጥቅም እንዳለው ያሳያል ። መጽሐፍ “አንተ ልጄ ነህ” እንዲል በጥምቀት በርነት የሚመጡትን “አንቺ ልጄ ነሽ” “አንተ ልጄ ነህ” ብሎ እግዚአብሔር የሚቀበልበት የምሥጢራት መግቢያ ነው ።

ጌታችን መጠመቁ ብዙ ነገሮችን ያሳየናል ። ጥምቀታችንን መባረኩን ፣ እስከ ምጽአት የሚቀጥለውን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ማስጀመሩን ያሳያል ። ባለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት ብዙ ነገሮች ቆመው ወድቀዋል ፣ ተጀምረው ቀርተዋል ። ጥምቀት ግን አሁንም ብዙዎች የእግዚአብሔር ልጆች የሚሆኑበት ምሥጢር ነው ።

የጌታችን ጥምቀት ትሕትናን ያሳያል ። ሰው ሁሉ የሚጠመቀው ፣ የሚባረከው በሚበልጠው ካህን ነው ። ጌታችን ግን በሚያንሰው አገልጋዩ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ ። ይህም የሚበልጡንን ብቻ ሳይሆን የሚያንሱንን ማክበር እንዳለብን የሚያስረዳ ነው ። የጌታችን ጥምቀት ንስሐን እንደሚያከብር የሚያሳይ ነው ። በዮሐንስ ዘንድ እየተናዘዙ ሊጠመቁ የመጡ ብዙ ሰልፈኞች ነበሩ ። ኃጢአት የሌለበት ክርስቶስ በኃጢአተኞች ሰልፍ መካከል ቆመ ። ንስሐን የሚወድድ መሆኑን ገለጠ ። በበረት የተወለደው ፣ በዓመፀኞች ከተማ በናዝሬት አድጎ ናዝራዊ ኢየሱስ የተባለው አሁን ደግሞ በኃጢአተኞች ሰልፍ መካከል ቆመ ። እርሱ ኃጢአትን እየጠላ ፣ ኃጢአተኞችን የሚወድድ አምላክ ነው ። እኛ ደግሞ በተቃራኒው ኃጢአትን እየወደድን ፣ ኃጢአተኞችን የምንጠላ ነን!

የጥምቀቱን በረከት ያሳድርብን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 11 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም