የትምህርቱ ርዕስ | የመጣል ስሜት

እንኳን የሚናገር ሰው የምትናገር ወፍ የሚናፍቀን አንዳንድ ጊዜ አለ ። ሁሉም የረሳን ፣ ሁሉም ደጁን የዘጋብን ፣ ሁሉም ከልቡ ያራቀን መስሎ ይሰማናል ። ናዳ ሊያወርዱብን ብዙ እጆች ድንጋይ የያዙ መስሎ ያሸማቅቀናል ። ጦርነት በሌለበት በውስጣችን ሽብር ይፈጠራል ። ማለዳው ሠርክ የሆነ ፣ ቀኑ የመሸ ፣ ነግቶ ያልነጋ ይመስለናል ። ድንገት ከእንቅልፋችን ስንነሣ ፣ ለሥራ ስንዘጋጅ ፣ የቀኑን ተግባር ስናቅድ የሕይወት ጦርነት ይጀምረናል ። አንተ እኮ የተጣልህ ነህ ፣ የምትለፋው ለማን ነው ? የሚል ሙግት ይቋቋመናል ። የመጣል ስሜት ከዚህ በኋላ የሚፈልገኝ የለም ፣ ብፈልገውም እኔን ዋጋ የሚሰጠኝ ማንም የለም የሚል ሹክሹክታ አለው ። ድንገት ብስጩ ያደርገናል ። የሁሉም ነገር መፍትሔ ሞት ብቻ መስሎ ይሰማናል ። ሰማዩ ለበረከት ሳይሆን እኛን ለመጫን የተዘረጋ ጥቁር ጥላ ይሆንብናል ። ሰማይ ድሮ ሩቅ ነበር ፣ ዛሬ ግን አናታችን ላይ እንደ እንቅብ ሊከደንብን የቀረበ ዓይነት ስሜት ውስጥ ይከተናል ። የሚፈልገኝ ፣ የማስፈልገውም የለም ፣ እኔ ባልኖር ማንን አጎዳለሁ ? የሚለው የሌጣነት ስሜት ከብርቱ ጥዝጣዜ ጋር ይመጣብናል ። ሰው የሚኖርለት ነገር ሲጠፋው መኖር እየጠፋው ይመጣል ። ትልልቅ እቅዶች ፣ ከሳምንታት ፣ ከዕለታት በፊት የነበሩ ራእዮች ድንገት ይሰወሩብናል ። አዎ አንተ የተጣልህ ነህ ። ዛሬ ብቻ ሳይሆን ከልጅነትህ የተረሳህ ነህ የሚል የግድ ነዋሪነት ስሜት ይጋፋናል ።

ስልኮች ሲደወሉ አናነሣም ፣ በተቃራኒው የሚደውልልኝ የለም የሚል ብሶት የወለደው ልቅሶ ይተናነቀናል ። ሰው ማግኘት አንፈልግም ፣ ሰው አይፈልገኝም እንላለን ። ሰዎች ሊረዱንና ሊያግዙን ወደ እኛ ሲመጡ እንሸሻቸዋለን ። ሰው ከመድኃኒቱ ያጣላዋልና መፍትሔአችን ላይ በር እንቆልፋለን ። ለመጸለይ አቅም የለንም ፣ ጸሎቴ አይሰማም የሚል ስሜትም ከቦናል ። ደግሞ መጸለይ አልቻልኩም የሚል ጸጸት ውስጥ እንገባለን ። ከፍተኛ የሆነ የስሜት መዘበራረቅ ይገጥመናል ። ሞትን እንመኛለን ፣ መልሶ ትንሽ ሕመም ሲሰማን እንፈራለን ። ምነው ኒውክለር በተተኮሰ ፣ አንዱ ሟች አንዱ አልቃሽ የሌለበት ፍርድ በመጣ እንላለን ፣ ወዲያውም ፊኛ ሲፈነዳ ልባችን ትር ትላለች ። ሰዎች እንዳያውቁብኝ እንላለን ፣ መልሰን በሬዲዮ ለዓለም ስሜቴን በገለጥሁ እንላለን ። ፍርሃትና ድፍረት ሜዳ አድርገው ይታገሉብናል ። ያ እልኸኝነታችን ይከዳናል ፣ ጉብዝናችን ትቶን ይሄዳል ፣ የወገባችን መታጠቂያ ይላላል ፣ ለመሮጥ አቅም እንዳይኖረን የጫማችን ማዘቢያ ይፈታል ። ልባችን ሲደልቅ ጎረቤት የሚሰማ ይመስለናል ። የሕልሙ ዓለም አለቅህ ብሎ በቁም ቅዠት ውስጥ ይከተናል ። ፀሐይ ቢወጣም ሕይወት ዳምና ትታየናለች ። የጨው ውኃ እንደ ጠጣ ምክር ፣ መዝሙር ፣ ማጽናኛ አይጠቅመንም ፣ አያረካንም ። ማደንዘዣው እንደ ለቀቀው ታማሚ መልሰን ከብዙ ምክር በኋላ እናቃስታለን ።

ሰማዩ ጥቁር ፣ ምድሩ እሾህ ፣ ዙሪያው ይሰቀል ባይ ፣ ሜዳው የሚሳለቅብን መስሎ ይሰማናል ። እስከ ዛሬ የምናውቃቸው ክፉዎች በፊት ለፊታችን ይመጡብናል ። እነርሱ ምንም ሆነው አያውቁም ፣ እኛ ግን የሕማም ሰው ነን ብለን ለራሳችን እንነግረዋለን ። ድንገት ታክሲ ውስጥ አብሮን የተቀመጠውን “ይቅር በለኝ” ብለን ያልበደልነውንና የማናውቀውን ሰው ይቅርታ ለመጠየቅ ይዳዳናል ። ሰማይና ምድር የተቀየሙ ሲመስለን ይህ ዝቅታ ይጫጫነናል ። የጠበቅነው ያ ጥሩ ቀን እየሸሸ ነው ። ከሰማይ የተጣለ ወደ ጥልቁ ሲወረወር ሰማይ ጥሎኝ እየጠፋ ነው ብሎ ያስባል ። እውነቱ ግን እርሱ ከሰማይ እየራቀ ነው ። ሰማይ በስፍራው ነው ፣ እርሱ ወደ ጥልቅ እየወረደ ነው ። አለመኖር በጣም ይሰማናል ። የንብረት ኑዛዜ ለማድረግ እንከጅላለን ። ግን ለማን እንናዘዛለን ። እኛ እኮ የተተውን ሰዎች ነን ። እኛ ከሌለን ያለን ነገር እንደ ፍጥርጥሩ ይውጣ ። ድርሻችን መሞት ነው ። ሌላውም የራሱን ድርሻ ይወጣ ። ከቀናት በፊት ታላቅ ስኬት ነበረን ፣ መልሶ ታላቅ ውድቀት ይመጣብናል ። አዎ የመጣል ስሜት ከባድ ነው ። ይህ ሁሉ ግን ስሜት ነው ፣ አዎ ስሜት ነው ። በንኖ የሚጠፋ ። አባረን ብንይዘው የአረፋ ኳስ የሆነው ስሜት ነው ። እውነቱ ግን “አልጥልህም ከቶም አልተውህም” ያለው የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ነው (ዕብ. 13 ፡ 5) ።

ድምፅ ይሰማል ። ከሰማይ የሚንቆረቆር ዜማ ያለው የሚመስል መልእክት እየመጣ ነው ። ይህን ድምፅ ማንም እንዲያቋርጥብን አንፈልግም ። ሰዎች ለእኛ ቃል ያጠራቸው ፣ ያጽናናቸው ያቆሰሉን ፣ የጠበቅናቸው የከዱን ነንና አዎ ይህን ድምፅ ምንም እንዳይጋፋን እንፈልጋለን ። ያለን ተስፋ አንድ ነው ፣ እርሱም ከሰማይ ነው ። ተመስገን ድምፁ ተሰማ ። እኛ እየተናገርን ቢሆንም “የእኔን ድምፅ ስሙና እናንተ ትቀጥላላችሁ” በሚል ማባበል መጣ ።

“አሁን የማዕበል ጊዜ ነው ፣ የጸናውን ዓምድ እኔን ክርስቶስን ያዙ ። ሞገድ የማይበረታታበት መርከብ ትፈልጋላችሁ እኔ ኢየሱስ ነኝ ፣ በእምነት ተሳፈሩብኝ ። ሰዎች የራሳቸው ችግር አላቸውና ከችግር እንዲያወጡአችሁ አትከጅሉ ። ግን የሰው ድምፅ በራሱ መድኃኒት ነው ። በሩን ከፍታችሁ ውጡ ፣ ፀሐይ እያበራ ነው ፤ ምድር አሁንም ሰፊ ፣ ሰማይም ከፍ ያለ ነው ። ያላችሁን ከሌላችሁ ነገር አትተምኑ ። ካላችሁና ከሌላችሁም ፣ ከጉድለትም ከሙላትም በላይ እኔ አማኑኤል አለሁላችሁ ።”

ኡፍ ተመስገን ! ይህ ድምፅህ ያስገምግም ፣ እንደ መብረቅ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ ያብራ ። በአንድ ጊዜ ለወገን ይሰማ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 22 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም