የትምህርቱ ርዕስ | የማያስወቅስ ክፉ ስም

“…ቀራጩ ማቴዎስም፥…” ማቴ. 10፡3 ።

ብዙ ሰው የኋላ ታሪኩን ለመደበቅ ከራሱ ጋር ትግል ውስጥ ይገባል ። ሀብቱ ከድህነት የጀመረ ሳይሆን በወርቅ ምንጣፍ ላይ እንደ ተወለደ ለማስረዳት ይሞክራል ። ሥልጣኑ ከሎሌነት የጀመረ ሳይሆን በማኅፀን የተቀባ መሆኑን ለመግለጽ ይዳዳዋል ። ቅድስናው በስርየት የጀመረ እንደሆነ ፣ ይቅር የተባለ ኃጢአተኛ መሆኑን ከመግለጥ የእናቴን ጡት ያልጠባሁ ፍጹም ፣ መምህር ያላስተማረኝ አማኒ ነኝ ለማለት ሩብ ጉዳይ ይቀረዋል ። በርግጥ በሀብት ላይ የተወለዱ ፣ አልጋ ወራሽ ተብለው በማለዳው የተሰየሙ ፣ በጠዋቱም ወደ እግዚአብሔር ቤት የገቡ ጥቂት ሰዎችን መጥራት እንችል ይሆናል ። የብዙኃኑ ሕይወት ግን ተራራ መውጣት ፣ ሸለቆ መውረድ ያለበት ነው ። ሰው ኖርኩ ካለም ሁሉንም የሕይወት ክፍል ቢያይ ታሪክ አለው ይባላል ።

ያለ ትላንት ዛሬ የለችም እንደሚባለው ዛሬ በዓሉ ከሆነ ዋዜማው አድካሚ ነበር ። ዛሬ የክብር ልብስ ቢለብሱም ዋዜማው ግን የጭስ የጠጣ ጨርቅ ነበረው ። ዛሬ ገንዘብ ቢነሰንሱም ትላንት ግን የሌሎችን ድጋፍ ይፈልጉ ነበር ። የዛሬው ቅላት የትላንት ጥቁረት ውጤት ነው ። እንደ ጌታ የሚበሉ እንደ ባሪያ የሠሩ ናቸውና ። አንድ ቀን የሚባለው ሃያ አራቱ ሰዓት ቀዳሚው አሥራ ሁለት ሰዓት ጨለማ ያለበት ነው ። ደስታን ከደስታ ቦታ ቢፈልጉ አትገኝም ። ደስታ የምትገኘው ኀዘንን ሲሻገሩ ነው ። በጥንተ ተፈጥሮ ሌሊት ይቀድማል ፣ ቀኑ ይከተላል ። ብርሃኑ ጨለማ አለው ። ጨለማውም ብርሃን አለው ። ሰው በዛሬው ሁነት ይገመግመን ፣ እንዲህ የኖርን ይመስለው ይሆናል ። የመጣበትን የሚያውቀው ግን የባለቤቱ አእምሮ ብቻ ነው ። ሸለቆውን ካልወጡ ተራራውን ማግኘት አይቻልም ። ጨለማ የብርሃን ዋዜማ መሆኑን ብዙ ሰው አያስተውልም ።

ትላንት በኃጢአት አብረውን የደከሙትን መጸየፍ ፣ በራሳችን እንደ ወጣን አድርገን በአደባባይ እኒያን መውቀስ የግብዝ አእምሮ ተግባር ነው ። የቻልነው ባስቻለን ጌታ እንጂ የሚችል ሥጋ ስለተሸከምን አይደለም ። መጣር ጥሩ ነው ፣ ከእኛ ይልቅ የጣሩ ግን ዛሬም ተራራ እየገፉ ነው ። የምንቆርሰው እንጀራ የረሀብ ዘመንን ያስተናገደ ፣ የምናዝዝበት እልቅናም የመገፋት ዋዜማ ያለበት ነው ። የእስራኤል ልጆች በየዓመቱ ከግብጽ የወጡበትን በዓለ ፋሲካ ሲያከብሩ በጉን ከመራራ ቅጠል ጋር እንዲበሉ ታዝዘው ነበር ። መራራውን ዘመናቸውን በማሰብ ለተጎዱት እንዲያዝኑ የሚያሳስብ ነበር ።

መጽሐፍ ቅዱስ የመጽናናት መጽሐፍ ነው ። ኃጢአተኞችን ባለ ተስፋ የሚያደርግ ፣ እኔንም ይቅር ይለኛል ብሎ ወደ እግዚአብሔር የሚያንደረድር መጽሐፍ ነው ። ስለ ዳኑ ኃጢአተኞች ፣ ስለነጹ ለምፃሞች ፣ ስለከበሩ ድሆች ፣ ስለጸኑ ሸምበቆዎች የሚናገር መጽሐፍ ነው ። አገልጋዮች የብርታት ታሪካችንን ብቻ ስለምንናገር “እኔማ ዋጋ የለኝም” ብለው ምእመናን ተስፋ እንዲቆርጡ እናደርጋለን ። ብርታታችን ድካም ነበረው ። ሕይወታችን ሁለት ገጽ የሚኖረው እግዚአብሔርን ስናገኝ ብቻ ነው ። ከዳተኛው ጴጥሮስ ሰባኪ ፣ አሳዳጁ ጳውሎስ የቤተ ክርስቲያን ማኅቶት የሆኑት ታሪክን በሚቀይረው እግዚአብሔር ነው ። ድካማቸው የተጻፈልን ለወቀሳ ለከሰሳ ሳይሆን እኔ አልድንም ለሚሉ ኃጢአተኞች ተስፋ እንዲሆን ነው ።

በቅዱስ መጽሐፍ ላይ በቀድሞ ስማቸው የሚጠሩ የእግዚአብሔር ምርጦች አሉ ። ስሙ ክፉ ነው ፣ የተጠቀሰው ግን ጌጥ ሆኖ ነው ። የዛሬውን ትልቅ ሹም “ሌባው እገሌ” እያልን በቀድሞ ታሪኩ ብንጠራው በአንገታችን ከረባት ሳይሆን ሰይፍ አንጠልጥለን መሆን አለበት ። የቀድሞ ፋይሉን ሊያጠፋ ደፋ ቀና የማይል ሹም ጥቂት ነው ። መጽሐፍ ቅዱስ በቀድሞ ስማቸው የሚጠራቸው ፣ ስማቸው የአሁን ሕይወታቸው ሳይሆን የቀድሞ ታሪካቸው በመሆኑ ነው ። ለመውቀስ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ምሕረት ለማግነን የቀረበ ስም ነው ። ለማሳነስ ሳይሆን ለአናሳዎች ሞራል ለመስጠት ያልተሰረዘ ስም ነው ። ሰው በቀደመ ስሙ ሲጠራ ፣ ራሱ በሚያፍርበት የቀደመ ግብሩ ሲሰየም ይከፋዋል ። በቀጥታ ራሱን “ቀራጩ ማቴዎስ” ያለው ግን ወንጌላዊው ነው ። ስሙ ክፉ ነው ፣ የማያስወቅስ ክፉ ስም ነው ። ጌታን ሲከተልም ድግስ ደግሶ ነው ። የቁም ተዝካሩን አውጥቶ ጌታን ተከተለ ይላሉ አባቶች ። ማቴ. 9፡10።

ማቴዎስ ራሱን ቀራጭ ብሎ ሲጠራ ያለው በሮማ ግዛት ነውና የከዳ ሠራተኛ መባልን ደፍሮ ነው ፣ ቀራጭን በሚጸየፉት አይሁዳውያንም ዘንድ የታሪኩን መለወጥ ሊያበስር ፈልጎ ነው ። ቀራጭ ማለት ለዚያ ዘመን አስተሳሰብ ባንዳ ፣ ከወገን እየበላ ወደ ጠላት የሚውጥ ማለት ነው ። ቅዱሱ መጽሐፍ ሐዋርያውን “ቀራጩ ማቴዎስ” ይለዋል ። ይቅር የተባለ ኃጢአት ያልተሠራ ያህል ነው ። እግዚአብሔር የኃጢአተኛን ኃጢአት ይቅር ሲል ከበደሉ በፊት ከነበረው ንጽሕና በላይ በማክበር ነው ። ይቅር የተባልሁ ኃጢአተኛ ነኝ ለማለት ራሱን “ቀራጩ ማቴዎስም” እያለ ይጠራል ። እግዚአብሔር ይቅር ያለውን ማን ይከስሰዋል ? ልክ እንደዚሁ “ጋለሞታይቱ ረዓብ” ፣ “ለምጻሙ ስምዖን” በማለት በቀደመ ክፉ ስማቸው የተጠሩ አሉ ። (ዕብ. 11 ፡ 31 ፤ ማቴ 26 ፡ 6 ።) ስሙ ክፉ ነው ፣ ግን የማያስወቅስ ስም ነው ።

ይቅር ተብለሃልና በቀደመ ስምህ ቢጠሩህ ደስ ይበልህ ። በጥፋትህ ላይ የእግዚአብሔር ምሕረት ገኗልና የምሕረቱ አደባባይ ሆይ ሐሤት አድርግ ።

ዕለተ ብርሃን 11

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 19 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም