መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ ክፍል 5

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ ክፍል 5

ታላቁ ነቢይ ሙሴ ንግግሩን ቀጠለ፡-

“ታጋይ መሆን ፣ ለወገን ጥቅም መቆም ፣ ስለ ነጻነት ነጻነትን ማጣት ፣ ስለ እስረኞች መታሰር በሕይወት ላይ ክብር ነው ። በታጋይ ስም የምንታገለው ለራሳችን ዝና ነው ወይ ? ብለን ልባችንን መጠየቅ ያስፈልጋል ። የጤና እክላቸውን ላለመስማት ታጋይ የሚሆኑ አያሌ ናቸው ። በውጫዊ ዓይናቸው ስለ ድሆች መገፋት እያለቀሱ በውስጣዊ ዓይናቸው ግን ስለ ኑሮና ስለ ትዳራቸው የሚያለቅሱ ዛሬ በዝተዋል ። ጭር ሲል ጭንቀት የሚጀምራቸው ፣ ውጫዊ ጦርነትን በመክፈት ምስኪኖችን የሚያስጨርሱ ቤት ይቍጠራቸው ። ለማይራሩለት ድሀ የአሳብ ዳቦ እየቆረሱ ፣ እኔ ብገዛችሁ ማር አዘንብላችሁ ነበር እያሉ በምኞት የሚቸሩ ብዙዎች ናቸው ። የጀብደኝነት ስሜት የተጠናወታቸው ፣ ዝናቸውን በረሀብተኛ ሬሳ ላይ የሚገነቡ ፣ መነዳት ጠባዩ የሆነውን ወገን በምላስ የሚነዱ ፣ “በአልጋ ሞተ ከመባል ገድሎ ሞተ መባል ለታሪክም ጥሩ ነው” እያሉ ለአንድ ማንነታቸው ሺህዎችን የሚገብሩ ፣ ግላዊ ጠባቸውን ብሔራዊ የሚያደርጉ ፣ የሰውን ስስ ብልት እየነካኩ ፣ የዘር ዕድር እያቋቋሙ ትውልድን የሚቀብሩ በዚህም ለብዙዎች መሞት ምክንያት የሚሆኑ ፣ ዋናው ተዋናይ አይሞትምና ሰው ሁሉ ሲሞት እነርሱ ግን መውጫውን አዘጋጅተው የሚተርፉ ብዙ ናቸው ። ምድር እነዚህን እንደምትሸከም ብታውቅ ኖሮ አትፍጠረኝ ብላ አምላኳን ትለምን ነበር ።

እኔ ለእስራኤል ሕዝብ እቆረቆር ነበር ። የቤተ መንግሥት ኑሮዬ ፣ የወገኖቼን ጭንቅ አላስረሳኝም ነበር። የግል ድህነቴን ለመበቀል የታገልኩ አልነበርኩም ። ንግሥናን አስቀምጬ ፣ አልጋ ወራሽነትን ንቄ ፣ ከቤተ መንግሥት ይልቅ ምድረ በዳን መርጬ ነበር ። ስለ ድሆች በእውነት የሚቆረቆር የተባረከ ነው !

መታገል መልካም ነው ። መከራ የመረረውን ሕዝብ ቢታገሉለት ነጻ ልውጣ ይላል ። መከራን እንደ ሰርግ የሚኖር ሕዝብ ግን ቢታገሉለት መልሶ ይታገላል ። የገዛ ሌባውን የደበቀ የትኛውም ፖሊስ አያወጣለትም ። ራሱን ለመከራ የጻፈ ሕዝብ ፣ በሬ ካራጁ እንዲውል ገዳዮቹን እያቀፈ ፣ የኖሩለትን ይገድላል ። ለማንና ለምን ነው የምቆረቆረው ? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል ። ራሳችን ሕዝብ መስሎ የሚሰማን ጊዜ ጥቂት አይደለም ። የዓለም ሕዝብ ስንት ነው ቢባል ውስጣችን አንድ ነው ። እርሱም እኔ ነኝ ማለቱ የማይቀር ነው ። እያልን የማንኖረው እውነት አለ ፣ ሳንል የምንኖረው ራስ ወዳድነት አለ ። ተራ ምርምርና ፣ የሥነ ልቡና ብልጠት ሳይሆን ራስን ለማየት ጥልቅ የሆነው ቃለ እግዚአብሔር ያስፈልገናል ። እኔ የማስፈልገው ለማን ነው ? ብሎ መጠየቅ መታደል ነው ። በቦታችን ሠራተኛ ፣ ያለ ቦታችን ተመልካች ነን ። በቦታችን ታዳጊ ፣ ያለ ቦታችን አጥፊ ነን ። እኔ ልቤ ለእስራኤል ይቀና ነበር ። ቅንዓቴ ግን ሥጋዊ ስለ ነበር ነፍሰ ገዳይ አደረገኝ ። በሥጋዊ ቅንዓትና ያለ ጊዜው በመውጣት ለአርባ ዓመት ስደት ተዳረግሁኝ ። ወገኖቼም ደስ አልተሰኙብኝም ። ላቀልላቸው ያሰብኩት ቀንበር የበለጠ ጸናባቸው ። መንፈሳዊነት የጎደለው ቅንዓት ራስንም ሌላውንም አያድንም ። ሚስቴ ኢትዮጵያዊት እንደመሆንዋ እንዲህ ብላ ትተርት ነበር ። “የእንጨት ምንቸት ራሱ አይድን ፣ ሌላውን አያድን” ትል ነበር ። ከእንጨት የተሠራ ድስት ራሱም በእሳት ይበላል ። የሚጠብቀውንም ወገን አብስሎ አያበላም ። የወንድነት ቅንዓት የእንጨት ምንቸት ነው ።

እግዚአብሔር ስለ ወገን ሸክም ሲሰጣችሁ እኔ የተላክሁት ለማን ነው ? ማለት አለባችሁ ። እዚህ ፊት ለፊቴ የማያችሁ የጌታዬ የክርስቶስ ሐዋርያት አላችሁ ። ቶማስ ለሕንድ ፣ እንድርያስ ለግሪክ ፣ ጳውሎስ ለሮም ተልካችኋል ። ሀገረ ስብከታችሁን በመለየታችሁ ወንጌልን ለዓለም አደረሳችሁ ። ደግሞም በምድር ላሉት ተተኪዎቻችን ደግሜ የምናገረው የምትሰብኩት ፣ የምትሮጡት ለማን ነው? በርግጥ ለወገናችሁ ነው ? ወይስ ለግል ኑሮአችሁ ነው ? የራሳችሁ ሎሌዎች ከመሆን ፣ በሰማያዊ ዓላማ ምድራዊ ኑሮአችሁን ከማሞቅ አምላከ እስራኤል ይጠብቃችሁ ። እኔ ለቀናት ከፈርዖን ጋር ታገልሁ ። ለአርባ ዓመት ግን ነጻ ከወጣው እስራኤል ጋር ታግያለሁ ። በማያምኑ ከመፈተን በሚያምኑ መፈተን ፣ በውሻ ከመነከስ በበግ መነከስ ሕመሙ ከፍ ያለ ነው ። እግዚአብሔር ግን በካህንም በምእመንም አይለካም ። ያመናችሁትን ካወቃችሁ በየጣቢያው “ወራጅ አለ” እያላችሁ አትጮኹም ። አሁንም በእግዚአብሔር የምታምኑ አገልጋዮች በርቱ ፣ ልባችሁም ይጽና ። በብዙ ሕዝብ የምታምኑ ሰባኪዎች ታዝናላችሁ ፣ ልባችሁም ይቆስላል ። ምርጫው የእናንተ ነው ፤ እግዚአብሔር የተገኘበት ትንሽ ጉባዔ የለምና በሙላትም በጉድለትም ደስ ይበላችሁ !

የአንበሳ ቆዳ አልብሰው ሲያሞግሱአችሁ ደስ እንዳላችሁ ፣ የውሻ ቆዳ አልብሰው ሲያኮስሱአችሁም ደስ ይበላችሁ ። ሆሳዕና ሲሉአችሁ በልኩ ከተደሰታችሁ ፣ ይሰቀል ሲሉአችሁም ትታገሣላችሁ ። አይዟችሁ ዓርብ እሁድ ፣ ስቅለትም ትንሣኤ አለው ። በበረከት ተባረኩ !

የነቢያት ጉባዔ/5

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሚያዝያ 11 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም