መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ/9

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ/9

ነቢዩ ኤልሳዕ አንድ ጊዜ ታላቁን ነቢይ ሙሴን ፣ ሌላ ጊዜም መምህሩን ነቢዩ ኤልያስን እያየ ንግግሩን ቀጠለ፡-

“ኢያሪኮ ደማቅ ከተማ ነበረች ። በኢያሪኮ ሰማይ ፀሐይ አይጠልቅም ነበር ። እግዚአብሔር ፀሐይን ሲያጠልቅ ሰዎች መቅረዝ አብርተው ይቀመጡ ነበር ። ውድ የሆኑ የሙት ባሕር ቅባቶች ሴቶች ያችን ከተማ እንዳይለቁ አድርገዋል ። ንጹሕ መታጠቢያ ቤትና ቅባት ብዙዎችን የከተማይቱ እስረኛ አድርገዋል ። ኢያሪኮን ለመጎብኘት የሄዱ በዚያው ነዋሪ ሁነው ይቀራሉ ። በኢያሪኮ ሕይወት የሚለካው በልብስ እንጂ በልብ አልነበረም ። በቂ ጥበቃ ያለባት ከተማ ፣ ሰዎች ማንንም ላለመንካት የሚጠነቀቁባት ምድር ናት ። ፍርሃትና የልብ ሁከት ግን ሰውን ብረር ብረር ያሰኘው ነበር ። በኢያሪኮ መቃብሮች የተጌጡና በአበባ የተንቆጠቆጡ ነበሩ ። እዚያ መኖር ብቻ ሳይሆን መሞትን ያስመኛሉ ። የመቃብር ስፍራዎች ቢያምሩም ሕይወት የለባቸውም ። በኢያሪኮም ውበት አለ ፣ ሕይወት ግን የለም ። መቃብሮች ተጠጋግተው ቢቀመጡም ፣ አንዱ ባንዱ ላይ ቢነባበርም አያወሩም ። በሰለጠነችው ከተማም ጎረቤት ሰላም አይባባልም ። ሰው ለሰው ተፈራርቶ ላለመነካካት ተጠንቅቆ ይኖራል ። የገንዘብ አምልኮም ስስትን እየዘራ “ምን እሰጣለሁ?” ሳይሆን “ምን እቀበላለሁ?” የሚል ሒሳባዊ ዓለም ፈጥሮ ነበር ። ከተሞች ሲሰለጥኑ ብልጠት እንደ ጽድቅ ይታያል ።”

“የጥይት ድምፅ ባይሰማም የሰለጠነ ከተማ ነዋሪ ውስጡ የተረጋጋ አይደለም ። በኢያሪኮ ባርነት ይወገዛል ። የእጅ ስንሰለት ያጠለቁ ባሮች አይታዩም ። ሕይወት ግን በዚያ ከተማ ግብ የሌላት እሽክርክሪት ነበረች ። ሳምንት ሙሉ የባከኑ ሰንበት ላይ በሙት ባሕር ዳርቻ ተዘርረው ፀሐይ ይሞቃሉ ። የልብ ቃጠሎን በበረሃው ቃጠሎ ሚዛናዊ ለማድረግ ይጥራሉ ። ከተማይቱ ውስጥ ያለው ባርነት አእምሮአዊ ነው ። መንፈሳዊ ቅኝ ግዛት በርክቶ ነበር ። የከተማይቱ ስም የጨረቃ ከተማ የሚል ትርጉም አለው ። በዚያች አገር የሚወራው ስለ ጨረቃ ነው ። የሰማይ ጎረቤት ስለመሆን ነው ። ሌሎች ዓለማትን ስለማግኘት ነው ። የረገጡትን ምድር አክፍተውት ሌላ ምድር ይናፍቁ ነበር ።”

“ነጻ መሆንና ነጻነት ልዩነት አለው ። የዚያች ስልጡን ከተማ ነዋሪዎች ነጻ ነኝ ይላሉ ። ነጻነት ግን አልነበራቸውም ። እንደ ልባቸው መሪያቸውን መሳደብ ይችላሉ ፣ መንካት ግን አይችሉም ። የማስተንፈሻ ጫካዎች ተዘጋጅቶላቸው እንደ ልባቸው ይቃወማሉ ። በተዘዋዋሪ ግን የመንግሥታቸው ተንቀሳቃሽ ማሽን ናቸው ። ማንም የእኔን ፍላጎት እንዲወስን አልፈልግም የሚል ድምፅ ከተማይቱን አጣቧታል ። ቃለ እግዚአብሔር መስበክ የሰውን ነጻ ፈቃድ መጫን እንደሆነ ይታሰብ ነበር ። በዚህ ምክንያት ከተማይቱ ስብከትን ለማገድ ታቅዳለች ። ሴቶች ዕርቃናቸውን ይሄዳሉ ። ሙቀቱን ምክንያት አድርገው ይራቆታሉ ። የሚነሰንሱት ሽቱም መልካም መዓዛ በመውደድ ሳይሆን ሌላውን ለመሳብና ልዩ አትኵሮት ለማግኘት ነው ። በሰለጠነ ከተማ ተፈጥሮን የማይቀበል ትውልድ ይፈላል ። ወንድ ሁኖ ሴት መሆንን ፣ ሴት ሁኖም ወንድ መምሰልን ይሻሉ።”

“ኢያሪኮ ጎዳናዋ ሰፊ ነው ። ያለ ድንበር ከልካይ ብዙ ንግዶች ይመጣባታል ። መብራት አይታጣባትም ። ቅባት በቀላሉ ይገኝባታል ። የመዝናኛ ስፍራዎች በብዛት ያሉባት ውብ ከተማ ናት ። ነገር ግን ውኃዋ መራራ ፣ ምድሪቱን የምትጨነግፍ ነበረች ። የሰለጠኑ ከተሞች ዘመናዊ ትምህርት አላቸው ። የኖረውን እሴት ግን ይጥላሉ ። ዘመናዊነት ዓለም ዛሬ ጀመረች የሚል ትላንትን የሚንቅ ነው ። በሰለጠኑ ከተሞች መኖር የማይፈልጉ ወላጆች ፣ ለልጆቻቸው ግን ይመኛሉ ። ልጆች ግን ሕይወት መራራ እንደምትሆንባቸው ፣ ከምግባርም እንደሚጨነግፉ አያስተውሉም ። ምድር ከመልካም ነገር ፣ ከጥሩ ትውልድ በምትጨነግፍበት ከተማ መኖር ተጨማሪ ፈተና ቢኖረውም እንደ ሎጥ መቀደስ ይቻላል ። አዳም በገነት ረከሰ ፣ ሎጥ በሰዶም ተቀደሰ ። አንድ ራሱን ቢያድንም ሚስቱንና ልጆቹን ግን ከስሯል ። በሰለጠኑ ከተሞች ትዳር ትግል አለው ። ቢሆንም የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን በእሳትም በውኃም አክብሮ መያዝ ይገባል ። ልጆች እናውቃለን ብለው ይጠፋሉ ። ልጅ ይሮጣል ፣ ሽማግሌ ግን መንገድ ያውቃል ። በትዕግሥትና በጸሎት ልጆችን ማትረፍ ይገባል ። የተጸለየበት ልጅ ወጥቶ አይቀርምና ።”

“እግዚአብሔርን ለማምለክ ምቹ ከተማ ሳይሆን ምቹ ልብ ያስፈልጋል ።”

ነቢዩ ኤልሳዕ በምድር ላይ በሰፊ ትምህርቱ ሳይሆን በብዙ ተአምራቱ የሚታወቅ ነው ። አሁን ግን ሰፊ ትምህርት መስጠቱ ገረመኝ ። ይህን ሁሉ በተናገረ ጊዜ ሰማይ ለእኛ መልእክቱን ዛሬም እንደ ቀጠለ አስተዋልሁ ። ምድርን ለማየት ሰማያውያን ዓይናቸው በቂ ነው ። እኛ ሰማይን የምናየው ግን በእምነት ነው ። በእምነት ነገሥታትንና መከራን ብቻ ሳይሆን ምቾትንም ድል እንድንነሣ ተመኘሁ ። ዛሬም ለእኔ ቃል ያላለቀበትን እግዚአብሔርን አመሰገንሁ ።

ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/9

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ግንቦት 21 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም