የትምህርቱ ርዕስ | የጸና ግንብ

 “የእግዚአብሔር ስም የጸና ግምብ ነው ጻድቅ ወደ እርሱ ሮጦ ከፍ ከፍ ይላል።” ምሳሌ 18፡10
በህልውና የተገኘ ነገር ሁሉ ስም አለው ። እያንዳንዱ የሰው ልጅም ከሌላው ተለይቶ የሚታወቅበት የመጠሪያ ስም አለው ። ስም የህልውና መግለጫ ፣ ስም የአካል መታወቂያ ፣ ስም የግብር ማሳያ ነው ። የተጸውዖ ፣ የመዐርግ ፣ የሙያ ፣ የመንፈሳዊ ደረጃ መግለጫ የሆኑ ስሞች አሉ ። እነዚህ ሁሉ ስሞች ግን ከጊዜ በኋላ የተሰየሙና በጊዜ ውስጥም የሚያበቁ ይሆናሉ ። መነሻና መድረሻ የሌለው ዘላለማዊ ስም ያለው እግዚአብሔር ብቻ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ያሉት ስሞች ከመለያነት ባሻገር የማማጸን አቅማቸው ዝቅተኛ ነው ። ስምም ከስም አይበልጥም ። የእግዚአብሔር ስም ግን የሚያስጠጋ ስም ነው ። ከስሞች ሁሉ በላይ የሆነው ስምም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው ። ፊልጵ. 2፡9-10 ።
በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ግንቦች አሉ ። አንዳንድ ግምቦች ከጊዜ ብዛት የተነሣ በእርጅና ምክንያት ሰው ላይ በመውደቅ አደጋ ያደርሳሉ ። የሰሊሆም ግንብ ተደርምሶ አሥራ ስምንት ሰዎች እንደ ሞቱ ጌታችን አስታውሷል ። ሉቃ. 13፡4 ። አንድ ግንብ ግን የማይፈርስ ነው ፤ እርሱም የእግዚአብሔር ስም ነው ። ግንብ መሠረቱ የጸና ወደ ላይ ከፍ ያለ ነው ። ሰውና አራዊት የሚያሳድዳቸው ሰዎች ሮጠው ፣ ሮጠው ግንቡ ላይ ከወጡ ጠላታቸው ታች ሁኖ ይጮኻል እንጂ አያገኛቸውም ። እነርሱም በሩጫ የምትመታውን ልባቸውን ማስተካከል ፣ ትንፋሻቸውን ማደስ ይጀምራሉ እንጂ ከሥር ሁኖ የሚጮኸው ጠላት አያሰጋቸውም ። የእግዚአብሔር ስም ሮጠን ከፍ የምንልበት የጸና ግንብ ነው ። የምንሮጠውም በጸሎት ነው ። የምንሮጠውም ቃሉን በማሰስ ነው ። የምንሮጠውም ስሙን በመጥራት ነው ።
ጠቢቡ ሰሎሞን ይህን ሲገልጥ አባቱ ዳዊት የነገረውን በማስታወስ ይመስላል ። ዳዊት ከንጉሥ ሳኦል እስከ ልጁ አቤሴሎም ሁሉም ያሳደደው ፣ አማካሪዎችና ካህናት ያደሙበት ሰው ነው ። የንጉሥ ጠላት ፣ የልጅ ባላጋራ ፣ የአማካሪ አሳዳሚ ፣ የካህን አዋራጅ ሊሸከሙት የሚከብድ የመከራ ቋጥኝ ነው ። ዳዊት ሮጦ ሮጦ ከፍ ያለው በጸናው በእግዚአብሔር ስም ነው ።
በዚህ ክፍል ላይ ይሮጣል የተባለው ጻድቅ ነው ። ጻድቅ መሆን ማለት ከዓለም መገፋት ፣ በወዳጅና በልጅ ሳይቀር መከዳት ነው ። መገፋት የለም አልተባለም ፣ የሚያስጠጋ ግን አለ ። መሰደድ የለም አልተባለም ፣ የሚያስጠልል ግን አለ ። መታመም የለም አልተባለም ፣ የሚፈውስ ግን አለ ። መሮጥ የለም አልተባለም ፣ ከፍ የሚያደርግ ግን አለ ። መሮጥ ለውድድር ካልሆነ ክብር ላለው ሰው ብዙም አያሳርፍም ። የሚያሯሩጡ ቀኖች ግን አሉ ። በዚህ ሰዓት ወደ ዘመድ ፣ ወደ ባለሥልጣን ፣ ተስፋ ወደ ሰጡን ሰዎች ከመሮጥ ወደ እግዚአብሔር ስም መሮጥ ዋጋ አለው ። የእግዚአብሔር ስም የጸና ግንብ ነው ። የተሳፈሩበትንም ከፍ ያደርጋል ። አባራሪውና ተባራሪው ቅድም በምድር ላይ እኩል ነበሩ ። ተባራሪው ግን ግንቡ ላይ ሲወጣ አባራሪው ታች ፣ ተባራሪው ከላይ ሆኑ ። አባራሪው ግንቡን መምታቱ አይቀርም ። ግንቡ ካልጸና ይፈርስና ተባራሪው ተጨፍልቆ ይሞታል ። የጸና ግንብ ከሆነ ግን አባራሪው ጠላት አፍሮ ይቀራል ። የእግዚአብሔር ስም የጸና ግንብ ነው ። ኅሊና ፣ ሰዎችና ሰይጣን ሲያባርሩን ወደዚህ ስም እንሩጥ ። ውጤቱ ከፍ ማለት ነው ።
“ያንተን ስም ሰምቶ ሞት ይደንግጥ ፤ ቀላያትም ይሰንጠቁ ጠላትም ይረገጥ ። የጥፋት መንፈስም ይንቀጥቀጥ፤ ከይሲም ይወገድ፤ አለማመንም ይራቅ ። ወንጀለኛ ይቸገር ቊጣ ጸጥ ይበል ፤ ቅናት ጥቅም አያግኝ ፤ ኃጢአትን የሚያዘወትር ይገሠጽ ። ወርቅን የሚወዱ ይነቀሉ ፤ ድካም ይወገድ ፤ ሐሰተኛ ይጣል፤ መርዝ ያላቸው የፍጥረት ወገን ሁሉ ይበተን።” /ቅዳሴ እግዚእ – የጌታ ቅዳሴ ቊ. 53 ።
ከሰማያት በላይ ከፍ ያልከው ፣ አሳብህም ከውቅያኖስ ይልቅ የጠለቀው ፣ ብልሃትህ የማይደረስበት ጌታዬ እግዚአብሔር ሆይ አመሰግንሃለሁ ። እያንዳንዱ ቀን የራሱ የሆነ አባራሪ አለው ። የተለያዩ አባራሪዎች አሉ ፣ እኔ ግን ያው እኔ ነኝ ። እባክህን በመስቀልህ ማማ ላይ አሳፍረኝ ። ጠላቴን ከታች ሳየው እርሱ ወደ እኔ በማንጋጠጥ ይድከም ። ወደ ጸና ስምም ልጠጋና ቁርጥ ፣ ቁርጥ የምትለው እስትንፋሴ እንደገና መጓዝ ትጀምር ። የሚመታው ልቤ ፣ በፍርሃት የሚርደው ማንነቴ ይጠንክር ። ኃይሌን ብታመን ወደ አንተ አልመጣም ። ምንም የለኝምና እግዚአብሔር ሆይ አስጠጋኝ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለት መና /ክፍል 1/
ተጻፈ አዲስ አበባ
ዲአመ ሚያዝያ 30 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም