መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ድባቴ – ድብርት – መደንዘዝ

የትምህርቱ ርዕስ | ድባቴ – ድብርት – መደንዘዝ

የሰው ልጆች ከታላላቅ ችግሮችና ውጣ ውረዶች በኋላ ከሚገጥሟቸው የሥነ ልቡና ጉዳቶች አንዱ ድባቴ ወይም ድንዛዜ ነው ። ድባቴ ችግር ስለመጣ የሚሰማን ስሜት ሳይሆን የነበሩት ችግሮች ጥለውብን የሚያልፉት የድንዛዜ ስሜት ነው ። ድባቴ ከኀዘንና ከልቅሶ ዘመን በኋላ የሚመጣ ስሜት በመሆኑ ማንም ሰው በቀላሉ ሊገነዘበው አይችልም ። መከራው ድምፅ ያለው ሲሆን ድባቴ ግን ድምፅ የለሽ ነው ። መከራው ብዙ ወዳጆችን ሊሰበስብና ሊበትንብን ሲችል ድባቴ ግን ብቻችንን የምናልፍበት የሕይወት ቀጠና ነው ። ሰዎች ብቻ ሳይሆን እኛ ራሳችንም ሳይቀር ይህን ስሜት ላንለየው እንችላለን ። ቀድሞ የምናደርገውን ነገር ዛሬ ማድረግ አለመቻላችን ፣ ፊት ያስደስቱን የነበሩ ነገሮች አሁን የማያስደስቱን መሆናቸው ፣ ፍቅርና ደግነትም ሕይወት ሳይሆን ሥራ እየሆኑብን ሲመጡ ምን ሆኛለሁ ብለን በስሱ ልንጠይቅ እንችላለን ። ይህ ግን ድባቴ ሊሆን ይችላል ። ድባቴ በተለያየ መንገድ ሊመጣ ይችላል ። ድባቴ ከጎርፍ በኋላ ያለ ትንሽ ፈሳሽ ፣ ከዶፍ በኋላ ያለ ካፊያ ልንለው እንችላለን ። ድባቴ ከቊስል በኋላ ያለ ጠባሳ ሲሆን ጠባሳው ግን የሚወጥር ስሜት አለው ።
ድባቴ የተለያዩ መነሻዎች ሊኖሩት ይችላሉ ። ትዳራቸውን እስከ ሞት ድረስ አስበውት እስከ መፋታት የሆነባቸው ሰዎች ድንገት ድባቴ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ ። የፍርድ ቤት ክርክር ላይ ንዴት እንጂ ድባቴ የለም ። ሁሉም ነገር አብቅቶ ቁጭ ስንል ድባቴ ሊጀምር ይችላል ። በጣም የሚወዱት ልጅ በአደጋ ሕይወቱ ማለፉ ወደ ድባቴ ሊከት ይችላል ። ኋላ የመጣ ልጅ ቀድሞ መሄዱ ብቻ ሳይሆን ማኅበረሰቡ ይህን አደጋ እንዴት ያለ ትርጉም ይሰጠዋል ብለን ማሰብ ስንጀምር ድባቴ ሊቆጣጠረን ይችላል ። በመውለድ ሰዓት የሚመጣ ድባቴ ሊኖር ይችላል ። ይበልጥ ብቸኝነት በሚያጠቃው በፈረንጅ አገር ይህ ስሜት ሊጫጫን ይችላል ። በአገራችን ወላድን ከበብ ፣ ከበብ ማድረግ በረጅም ጉዞ ውስጥ የደረሱበት ትልቅ እውቀት ነው ። መውለድ ደስታ ቢሆንም ሊያስከትለው የሚችለው ድባቴም ይኖራል ። ከእስር የተፈቱ ሰዎች ይህ ችግር ሊገጥማቸው ይችላል ። ከዓለሙ ጋር እኩል መጓዝ ሲያቅታቸውና መገለሉ የማያባራ ፈተና እየሆነ ሲመጣባቸው ራሳቸውን በዚህ ስሜት ውስጥ ሊያገኙት ይችላሉ ። ወዳጆቻቸው በተለያየ ምክንያት ከአጠገባቸው የራቁአቸው ሰዎችም አስበው ፣ አስበው ሲደክማቸው ድባቴ ውስጥ ይገባሉ ። የኑሮን እውነት አለመቀበል ለድባቴ ያጋልጣል ። የውስጣቸውን ገልጠው ለመናገር የማይፈልጉና መሸነፍ የሚመስላቸው ሰዎችም ድባቴ ያጠቃቸዋል ። ትልቅ ሕክምናና የዕድሜ ማራዘሚያ ውስጥን መግለጥ መሆኑን የሚያውቁ ጥቂቶች ናቸው ። አስቸጋሪ ጉዞ ያለውን ትዳራቸውን ተሸክመው የሚኖሩ ሰዎች ከዚህ በኋላ ዝም ማለት ነው ያለብኝ ብለው መቻል የሚመስል መቃጠል ውስጥ ሲገቡ ወደ ድባቴ ይገባሉ ። ከረሀብ ዘመን በኋላ የሚመጣው የማግኘት ዘመንም የራሱ ድባቴ አለው ። ሁሉንም ነገር ያደርግና “ታዲያ ምንድነው ትርጉሙ ? ” ብሎ ሲያስብ ድባቴ ውስጥ ይገባል ። ሱስ የለመዱ ሰዎች ሱሱ የቀረ ሲመስላቸው የሚሰማቸው የመደበት ስሜት አለ ።
ትኩስ መከራዎች ንዴትን ፍርሃትን ፣ መፍትሔ ፍለጋን ሲወስዱ ድባቴ ግን ትዕግሥት የሚመስል መደንዘዝና አጉል ድፍረትን ወይም ፍርሃን የተሸከመ ነው ። መከረኞች የመውጫውን መንገድ ሲፈልጉ በድባቴ ውስጥ ያሉ ሰዎች ነገሮች እንዲተረማመሱ ይፈልጋሉ ። ሁከትና መደበላለቅን የሚፈልጉ ሰዎች የዚህ ስሜት ተጠቂዎች ናቸው ። ሰዎች በዚህ ስሜት ውስጥ እንዳሉ ለማወቅ ከፍተኛ የድካም ስሜት ውስጥ ይገባሉ ። ስለ ሞቱ ሰዎች ከማዘን ተገላገሉ ብለው ያስባሉ ። በአደባባይ የሚታዩ ከሆነ መታየትን እየጠሉ ይመጣሉ ። ቀላል የነበሩ ተግባሮችን አሁን ለመከወን አቅም ያጣሉ ። በይሉኝታ ፍቅርንና አክብሮትን ቢሰጡም ይህ ግን ለእነርሱ ትልቅና የግድ የሆነ ሥራ ነው ። ደስተኝነት ማጣት ፣ ሁሉንም ነገር ሰዎች ያድርጉልኝ ብሎ በውክልና መኖር ፣ ገለልተኝነት ማብዛት አንዱ ምልክት ሊሆን ይችላል ።
በድባቴ ውስጥ ያሉ ሰዎች ሊያስቡት የሚገባ ነገር አለ ። ያለፉት ቀኖች ላይስተካከሉ ይችላሉ ፣ የተሻለ ተግባር ግን ከትላንት ይልቅ ነገ ላይ አለ ። ያለፈውን በአስተማሪነቱ እንጂ በሕያውነቱ መጠቀም አንችልም ። በጸሎት ሁሉን ለእግዚአብሔር መግለጥ ትልቅ መንፈሳዊ ፈውስ ያመጣል ። ወደ አማካሪዎች ሂዶ በፍጹም ግልጥነት ማውራት ይጠቅማል ። በይበልጥ የሃይማኖት አባቶች በጸሎትና በመንፈሳዊ ምክር ስለሚያግዙ ይጠቅማሉ ። ቆየት ያሉና ነጻነት የሚሰጡን ወዳጆችን ማግኘትም የተሻለ መፍትሔ ያመጣል ። ማንበብና የሰውነት እንቅስቃሴ ወይም ስፖርት መሥራት አንዱና አስፈላጊ ነገር ነው ። ያለፉትን ዘመናት በይቅርታ መዝጋትና ነገን በአዲስነት መጠበቅ ትልቅ መፍትሔ ነው ። የድባቴ ስሜት ከእምነት ማነስ የመጣ ስሜት ነው በሚል ራስን መውቀስ ከንቱ ነገር ነው ። በተወሰነ ሰው ላይ ብቻ ሳይሆን አብዛኛው የሰው ልጅ የሚያልፍበት መስመር መሆኑንም መረዳት መልካም ነው ። ብዙ ሰዎች እንዲህ ያለውን ስሜት ተቀብሎ ወደ አማካሪ ዘንድ መሄድ የውድቀት ያህል ያዩታል ። የጨጓራቸውን መታመም እየተቀበሉ ከጨጓራቸው ይልቅ ትልቅ ሥራ ያለበትን አእምሮአቸውን ሊረዱት አለመቻላቸው ይገርማል ።
የድባቴ ዘመን ሲያበቃ ድንገት ብርሃን ይበራል ። ምንድነው የያዘኝ ? በማለት ፈጥኖ ወደ ሥራው ይቀላቀላል ። ድባቴ የዘላለም ዕጣ ወይም የአምላክ ቅጣት አይደለም ። ወዳጆች ሆይ ይህም ያልፋል ።
እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በዚህ ውስጥ ለሚያልፉ ወገኖች ሁሉ የድል ብርሃንን ያብራ ። አሜን ።
ዲአመ
ነሐሴ 24 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም