መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ (2)

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ (2)

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

የሮም መንገዶች ጭርታ ነግሦባቸዋል ። ኔሮን ቄሣር ቤተ መንግሥቱን ለመሥራት ብሎ የሮምን ከተማ ከግማሽ በላይ በእሳት አጋይቶት ነበር ። የዘመናት ጥበብ ፣ አስደናቂ ኪነ ሕንፃዎች ፣ አብያተ ጣዖታት ፣ አብያተ መንግሥታት ወደሙ ። “የኔሮን እሳት” ተብሎ የሚጠራው ይህን ውድመት ንጉሡ ተራራ ላይ ሁኖ በደስታ ይመለከት ነበር ። ኋላ ላይ የመጣው ሰውን እያቃጠሉ መደሰት በዚህ የጀመረ ነበር ። ያቺ ውብ ከተማ ፣ እንደ ቆንጆ አሮጊት ውበትዋ በሩቅ የሚፈለግ መናገሻ ዛሬ በቁሟ ተለብልባ ነበር ። በዓለማችን ላይ ያለች ሰፊ ኩሽና ሆነች ፣ በጭስ ጠቆረች ። እሳት በልቶ በቃኝ ማለት ይቸገራልና ሺህ ዓመታት ከሰልና አመድ ሁነው ፣ ታሪክ እያለ እንደሌለ ሁና ነበር ። ፍላጎት ድንበር ፣ ቅምጥልነትም ልክ ሲያጣ ከተማ ምድጃ ፣ አእላፋትም ማገዶ ይሆናሉ ። ኔሮን የግል ችግሩ ዓለምን አስቸግሮ ነበር ። ከኢየሩሳሌም እስከ ቍስጥንጥንያ ፤ ከአንጾኪያ እስከ ሮም መንግሥቱ እየተናወጠ ነበር ። ሞቶም ያዝዝ ፣ አብዶም ይገዛ ነበር ። እልፍኝ ለመሥራት ከተማን አቃጠለ ፣ እርሱ ለመኖር ብዙዎችን አሳዘነ ። የጭምትነቱ ዘመን ለዐሥር ዓመታት ነበረ ። የማይረካው ፍላጎቱ መወራጨትን ፣ ወሰን አልባነቱም ጨካኝነትን አመጣበት ።

በሮም መቃጠል ምክንያት ሕዝቡ ሊበላው ተነሣ ። የሕዝቡን ቍጣ ለማብረድ የነበረው አንድ መንገድ ክርስቲያኖችን ጭዳ ማድረግ ነበር ። የሮምን ከተማ ያቃጠሉት ክርስቲያኖች ናቸው ብሎ ለሕዝቡ ጠላት ፈጠረላቸው ። አምባገነን ነውና ጠላት ካልፈጠረ የሚኖር አይመስለውም ነበር ። ሕዝቡም እብደቱን ቢያውቀውም ስማው ተብሎ የተፈረደበት ያህል ምክንያቱን ተቀበለው ። ሕዝቡ ጋ ሲደርስም ሁለት ዓይነት መልክ ፈጠረ ። አንደኛው ቡድን ክርስቲያኖች አቃጠሉት ሲል ፤ ሁለተኛው ደግሞ ክርስቲያኖች ባሕላችንንና አማልክቶቻችንን በማሳዘናቸው ከተማዋ በአማልክት ቍጣ ፈረሰች ማለት ጀመረ ። አርእስተ ዜናውን ከሰጡት ብዙኃኑ ወገን ዝርዝር ዜናውን ያስተነትነዋል ። እርካታ ያጣ አባወራ ልጆቹን እያስራበ ሁለት ትዳር ይመሠርታል ። እርካታ ያጣ ካህን በሐሰተኛ ትንቢትና ፈውስ ሕዝብን አስከፍሎ ያሳብደዋል ። እርካታ ያጣ መኰንንም ሁሉም አልቆ እኔ ልኑር ያሰኘዋል ።

አንዳንዴ ሕዝብ እንደ መስኖ ውኃ ወደ ቀየሱት ይፈስሳል ። ስለዚህ ከኔሮን ጋር በመግደል ተባባሪ ሆነ ። ሮም ስደርስ ይህ ሁሉ ጥላ አጥልቶባት ነበር ። ጳውሎስ ያዘዘኝን የብራና መጻሕፍት በጀርባዬ ተሸክሜ በጎዳና ላይ ብቻዬን እሄዳለሁ (2ጢሞ. 4 ፡ 13) ። ቀጥሎ የሚሰማኝ የራሴው የእግር ኮቴ ብቻ ነው ። ጸጥታው ምቾት የወለደው ሳይሆን ፍርሃት ያመጣው ነበር ። ሁለት ዓይነት ጸጥታ አለ ። የልብ ጽሞና ያለበት የአካባቢ ጸጥታ የመጀመሪያው ሲሆን ፤ የሰው ረሀብ የወለደው ፣ ወገን ወገኑን ፈርቶ እቤቱ የሚቀመጥበት ፣ የተሸበረ ልብ የሚወልደው የአካባቢ ጸጥታ ሁለተኛው ነው ። ሰላማዊ የሆነ ጸጥታ ለጸሎት ይረዳል ። ጎዳናውን ሁሉ ከጌታ ጋር እያወሩ ለመሄድ ከጸሎት እልፍኝ በላይ ይረዳል ። ክርስቲያን በመልካሙ ጊዜ ከመጸለይ ፣ በክፉውም ጊዜ ተግቶ ከመጸለይ ውጭ ሌላ አማራጭ የለውም ። የመግደል ድፍረት ባይኖረውም ፣ የመሞት አቅም ግን አለው ። ሮም ውበትዋ አሮጌነትዋ ነበር ። አሮጌነት ሁሉ ማስጠላት ፣ አዲስነት ሁሉ ማማርም አይደለም ። ኔሮን ግን የእሳት እራት አደረጋት ። እሳት ቢበላም ሆድ ስለሌለው በቃኝ አይልም ።

ዋርካ ምን ያፈራል ? ብለው ሳይጠይቁ ፣
ዋንዛ ምን ያፈራል ? ብለው ሳይጠይቁ ፣
ሾላ ምን ያፈራል ? ብለው ሳይጠይቁ ፤
ቆርጠው ፣ ቆርጠው ጣሉት እነ ጣዕም አያውቁ ።

የሮም ሕዝብም ንጉሡን ቢጠላውም ክርስቲያኖችን በማሳደድ ግን ተባበረው ። የሰማው ምክንያት ባያሳምንም እመን ተብሎ የተፈረደበት ያህል ወንጌላውያንን ለማጥፋት ዘመተ ። እኔ ሮም ስደርስ ሁሉም የፈራበት ጊዜ ነበር ። ንጉሡ በሠራዊት መሐል ሁኖ ፈርቷል ። ሕዝቡ ባለ አገር ቢሆንም አገር ያመለጠው ያህል ፈርቷል ። ክርስቲያኖችም ወደ ካታኮምፕ ዋሻ ገብተዋል ። ጳውሎስ ግን ለክርስቶስ የሚሞትበትን ቀን እንደሚሞሸርበት ቀን ይናፍቀው ነበር ። ያለ ጌታ ከመኖር በጌታ መሞት ደስተኛ ያደርጋልና ።

ይህን ሁሉ እያሰብሁ ሐዋርያው ጳውሎስ የተከራየው ቤት ደጃፍ ላይ ደረስሁ ። “ማነው ?” ሲለኝ እኔም “ጢሞቴዎስ ነኝ” አልኩት ። በልቤ ያለውን ሁሉ ለማውራት ጓጉቻለሁ ። ከመጣሁበት መንገድ ፣ በሩ እስኪከፈት ያለው ደቂቃ ራቀብኝ ። ይሁና ! ሰው ሲገኝ እናወራዋለና !

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 2

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 14 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም