በአፍ ያመኑትን ሃይማኖት በሥራ መካድ ፣ የመሰከሩለትን እውነት መልሶ መጣል ፈተና ነው ። ውጤትን እያሰቡ ማገልገል ፣ ምድራዊ ዋጋን እየሻቱ በእግዚአብሔር ቤት መመላለስ ፈተና ነው ። እየበሉ መራብ ፣ እየጠጡ መጠማት ፣ ተቀብሎ እንዳልተቀበለ ማጉረምረም ፣ ያለውን ከጎደለው አለማወቅ ፈተና ነው ። ለእውነት አንቀላፍቶ ለስሜት ታማኝ መሆን ፈተና ነው ። መልካሙን ሰው አጠልሽቶ ማየት ፣ ንጹሑን ወገን መጠራጠር ፣ በጎ ንግግርን በክፉ መተርጎም ፈተና ነው ። ሰውን በጉልበት መልካም አደርጋለሁ ብሎ መነሣት ፣ ትላንት ባደረጉት መልካም ነገር መጸጸት ፈተና ነው ።
ስለማናውቃቸውና በመለኮት ፊት ስለማንከሰስባቸው ሰዎች አስተያየት ሲሰጡ መዋል ፣ ስለ ማንም በጎ መናገር አለመቻል ፈተና ነው ። በየደረሱበት መስገድ ፣ አምልኮን እየወደዱ የሚመለከውን አምላክ አለማወቅ ፈተና ነው ። እንዴት እኔ ይህን አደርጋለሁ ብሎ መመጻደቅ ፣ ለቁጭት እንጂ ለንስሐ አለመብቃት ፈተና ነው ።
እግዚአብሔር የከደነለትን የወንድምን ገመና ማውጣት ፣ በሌሎች ምሥጢር መሳለቅ ፣ በፍቅር ቀን ለጠብ ቀን ብሎ መረጃ መያዝ ፈተና ነው ። ባማረ ፊት የተቀበሉንን ፣ ክፉውን ቀን ያሻገሩንን ረዳቶች መርሳት ፣ መመሪያን ትቶ መሪን መከተል ፣ ማምለክን ፈልጎ እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመፈለግ ፈተና ነው ። ይሙትም ይዳንም ሲባል ማጨብጨብ ፣ ለሕሊና ትቶ ለሆድ ማደር ፈተና ነው ። ሰውዬው የኮራበትን ክፋት አለማመን ፣ ዝንጀሮን አቆነጃለሁ ብሎ ቀለም መጨረስ ፈተና ነው ።
ጊዜ ተሰጥቶት ጊዜ መጠበቅ ፣ የቀበሩትን ቂም ቆፍሮ ማውጣት ፣ ለአምላክ የሚሰጠውን ፍቅር ለሰው መስጠት ፈተና ነው ። ራሱን የሰጠንን አምላክ እያመለክን ፣ ገንዘባችንን ለአሥራትና ለመባ መሰሰት ፈተና ነው ። ባልጋበዙን በሰው ጉዳይ መግባት ፣ የታገሡን ላይ ሌላ ጭነት መጨመር ፣ የተኰነነውን ኃጢአት ጽድቅ ለማድረግ መታገል ፈተና ነው ። የራስን ችግር አጉልቶ የሌላውን ረሀብ አሳንሶ ማየት ፣ በመጣው ነገር መማርን ጥሎ ማማረር ፈተና ነው ።
ራስን መምራት ከሥልጣን በላይ መሆኑን ዘንግቶ ሥልጣን መሻት ፣ ክፉ ሳይመጣብን ወደ ክፉ መሄድ ፣ እግዚአብሔር ያድነኛል ብሎ በበሽታ መጫወት ፈተና ነው ። በገነት መሰቃየት ፣ በምቾት መጨነቅ ፣ ከመልካም ሰውና ከመልካሙ ነገር እንከን መፈለግ ፣ ባሌ የማይመታኝ ስለማይወደኝ ነው ፣ ሚስቴ የማትሰድበኝ ስለማትቀናብኝ ነው ብሎ ፣ ጦር አውርድ ጸሎት መያዝ ፈተና ነው ። ጭር ሲል አልወድም ብሎ ነገር ማለኳኮስ ፣ በሚዋደዱ መካከል ጠብ መዝራት ፈተና ነው ። ሲሄድ የሚኖረውን ሰው አትሂድብኝ ብሎ ማልቀስ ፣ የወደደንን አምላክ ትቶ በጠሉን መደነቅ ፈተና ነው ። ያለፉትን ሰዎች ላሉት ሰዎች ማማት ፣ በማይመጣው ትላንት ላይ ማቀድ ፈተና ነው ።
አቤቱ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ! በምን እየተፈተንን እንደሆነ እንኳ አናውቅምና ከፈተና አድነን !!!
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሐምሌ 17 ቀን 2015 ዓ.ም